ገጠመኙ ከጥቂት ዓመታት በፊት ነው፡፡ በምኖርበት አካባቢ የቤት እቃ መሸጫ ሱቅ ከፍታ ከምትሰራ ሄለን ደጉ ከምትባል ወጣት ጋር ተዋወቅን። ይህች ወጣት በሕጋዊ መንገድ ወደ ተባበሩት ዓረብ ኤምሬት ለሥራ ፍለጋ በመሄድ ሰርታ የተመለሰች ነበረች፡፡ የመጀመሪያ ጉዞዋን አድርጋ ሁለት ዓመት ያህል እንደሰራች አሰሪዎቿ የተወሰነ ጊዜ ያህል እረፍት ሰጥተዋት ወደ ኢትዮጵያ መጣች፡፡ እንደመጣች ግን ቤተሰቦቿ ወደሚገኙባት ሰንዳፋ ከተማ አላመራችም ነበር፡፡ እረፍቷን ጨርሳ እስክትሄድ ድረስም ከአዲስ አበባ ውልፍት አላለችም፡፡
ከተማ ውስጥም ስትዘዋወር በአግባቡ ተሸፋፍና ነበር። ነገር ግን ከውጭ ሀገር የተላከ በማስመሰል ዕቃ ለቤተሰቦቿ ልካ እንደነበረ ታስታውሳለች፡፡ ይህን ያደረገችበትን ምክንያት ስታብራራም ቤተሰቦቿ እና ዘመዶቿ ከሷ ብዙ ስለሚጠብቁ ሀገር ቤት ብትሔድ እያንዳንዱን በስጦታ ዕቃ እና በዶላር ማንበሽበሽ ባለመቻሏ ነበር፡፡ እናም እረፍቷን እስክትጨርስ ቤት ተከራይታ ወደ ተባበሩት አረብ ኢምሬት ተመለሰች፡፡
አሁንም ጠቅልላ ወደ ሀገሯ ብትመለስም ቤተሰቦቿ ጋር ያስገባኛል ብላ የምታስበውን ያህል ገንዘብ ስላልያዘች በያዘቻት ጥሪት የራሷን የእቃ መሸጫ ሱቅ ከፍታ እዛው እያደረች ኑሮዋን ተያይዛዋለች።
እንደ እሷ አይነት መጠነኛ ጥሪት ቋጥረው በሀገር ላይ ለመሥራት ቢያልሙም የዘመዶቻቸውን ፍላጎት ባለማሟላታቸው ብቻ ለዳግም ስደት የሚዳረጉ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በርካታ ናቸው፡፡ ከነዚህም አብዛኞቹ ሕጋዊ የጉዞ እና የሥራ ፈቃድ ሰነዶች ሳይኖሯቸው በሕገ ወጥነት በሰው ሀገር የኖሩ እና በብዙ የስደተኝነት ቀውስ ውስጥ እያለፉ ያሉ ናቸው።
ይህን ታሪክ እንድናስታውስ ያደረገን የእናቶችና ህፃናት ዘርፈ ብዙ የልማት ድርጅት ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር “ ከባቢዊያዊ የእድገት አጋርነት ፕሮግራም” በሚል ፕሮጀክት ስር ለ91 ኤርትራዊያን ስደተኞችና ኢትዮጵያዊያን የስደት ተመላሾች በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ሰልጣኞች ባስመረቀበት መርሃ ግብር ላይ መገኘታችን ነው።
በእንጨት ሙያ እና በምግብ ዝግጅት አስተምሮ ካስመረቃቸው መካከልም 46 ሴቶች ነበሩ። ታዲያ ከስደት ተመላሽ የሆኑት ሴቶች ባሰቡት ልክ ኑራቸው ባለመቀየሩና ለከፋ ችግር በመጋለጣቸው “በሀገሬ ያገኘሁትን ልስራ” በማለት ከተመለሱ በኋላ ይሄንን የሰልጠና እድል ማግኘታቸውን ይናገራሉ።
ከሰልጣኞቹ መካከልም ጥቂቶቹን ስለ ህይወት ተሞክሯቸው ጠይቀናል። የቆንጆዎቹ መፍለቂያ ከሆነችው ወሎ የተገኘች የደሴ ልጅ ናት። የትምወርቅ አክሊል ትባላለች። ልጅነቷ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ልጅ የተገኘውን ከእህት ከወንድሞቿ ጋር እየተካፈለች እየተማረች ነበር የምትኖረው። ልክ ስምንተኛ ክፍል እንደ ደረሰች ነበር የጎረቤት ልጆች አረብ ሀገር ሄደው የቤተሰቦቻቸውን ህይወት ሲቀይሩ በመመልከት ለዚህ እድል ጥሩ አማራጭ ይኖራታል ብላ ወዳሰበቻት አዲስ አበባ የመጣችው። ለተወሰነ ጊዜ በአዲስ አበባ ኑሯቸውን ካደረጉት አክስቶቿ ቤት ከቆየች በኋላ ነበር ወደ ሱዳን ለስደት በመሄድ ሻይ ቡና በመሸጥ ኑሮዋን ለመግፋት መታገል የጀመረችው።
ስራው ከድካም የዘለለ ምንም ትርፍ ባይሰጣትም ከአንድ ሁለት ይሻላል በማለት እዛው ካርቱም በስደት ካገኘችው ኢትዮጵያዊ ጋር በትዳር ተጣምራ የተሻለ ህይወት ለመምራት የሚያስችላቸውን ጥሪት ለማጠራቀም ቢተጉም ኑሮ ሞልቶ የማይሞላ ሆኖባቸው ለረጅም ጊዜ ተንገዳግደዋል።
ለአምስት ዓመታት ኑሮን ለማሸነፍ ከታገለች በኋላ በስደት ካገኘችው ትዳር ያፈራችውን አንድ ልጅ ይዛ ከሀገሯ የተለየ ምንም ማግኘት ስላልቻለች በኢትዮጵያ ኢምባሲ በኩል ወደ ሀገሬ መመለስ እፈልጋለሁ ብላ ባቀረበችው ጥያቄ መሰረት የይለፍ ወረቀት አግኝታ በመኪና ወደ ሀገሯ ተመለሰች።
እዚህ እንደመጣች ለዓመታት የተለየቻት ሀገሯን መልመድ ግድ ሆኖባት እየተንገላታች በያዟት ጥሪት ለባለቤቷ መንጃ ፍቃድ አውጥተው እሱ ወደ ስራ እንዲገባ ካደረጉ በኋላ ሌላ አማራጭን መመልከት ላይ እያሉ ነበር ስለስልጠናው የሰማቸው። ምግብ ቤት የመክፈት ሀሳብ ያላት ይች ወጣት አቅም ማጣት የከለከላትን እድል ስታገኝ አይኗን ሳታሽ በስልጠናው ተሳትፋለች።
ድርጅቱም የስራ እድል እንደሚያመቻችላቸው መስማቷን የምትናገረው የትምወርቅ ነገን በተስፋ እየተመለከተች በስደት ያሳለፈችውን እድሜ በቁጭት ወደኋላ መለስ ብላ ታያለች።
ህይወት በስደት ከባድ ነው። ሰው ተሰዶ ጥሪት ካልያዘ ለምን ይሰደዳል? በተቻለ መጠን ያቅሙን ያህል በሀገሩ ከሰራ ከሰው ሀገር የማይሻል ምንም የለም ትላለች።
አዲስ አበባ የካ ሚካኤል አካባቢ ተወልዳ ያደገችው ልዩወርቅ ለገሰም ሌላዋ ያነጋገርናት ሰልጣኝ ስትሆን እሷም የስደት ህይወትን ቀምሳ በቃኝ ብላ ወደ ሀገሯ የተመለሰች ሰልጣኝ ናት።
ወጣቷ በሱዳን አንድ ባለ ሀብት ቤት ተቀጥራ ትሰራ የነበረ ሲሆን በስደት ህይወት ብዙ የተለያዩ መከራዎችን ብታሳልፍም አብረን ወደ ጣልያን እንሻገራለን ካለችው የፍቅር ጓደኛዋ አንድ ሴት ልጅን አግኝታለች።
ልክ ማርገዟን እንዳወቀች ትሰራበት የነበረውን ቤት ለቃ በኢትዮጵያ ኢምባሲ በኩል በትራንስፖርት ሀገሯ እንደገባች የምትናገረው የትምወርቅ የልጇ አባት ተሳክቶለት ካሰበበት ጣሊያን መግባቱን ትናገራለች።
ትዳር እዛና እዚህ እንዲሆን የፈረደባት ስደትን የምትረግመው የትምወርቅ ገንዘብ አግኝታ መለወጥ ያሰበችው ወጣት ልጅ ይዛ በባዶ እጇ መመለሷ እዚህ የነበሩት ጓደኞቿ በማህበር ተደራጅተው የተወሰነ ጥሪት አግኝተው፤ ቤተሰብ አፍርተው ስትመለከት አራት የባከኑ ዓመታትን እንደሳለፈች ትናገራለች።
“አሁንም አልረፈደም” የምትለው የትምወርቅ በምግብ ስራ ስልጠና የእለት ጉርሷን የምታገኝበት የስራ መስክ ላይ በመሰማራት ስደት ያበረከተላትን ፀጋ ልጇን ማሳደግ እንደምታስብ ተናግራ ሌሎችም ወደ ውጭ ለመውጣት ከመጓጓታቸው በፊት ቆም ብለው እዚህ ያሉ አማራጮችን ማጤን የሚገባቸው መሆኑን ታስረዳለች።
“እንደ ዝምታ መካሪ እንደ ስደት ኑሮ አስተማሪ የለም” በማለት ስለስደት ህይወቷ ስጠይቃት ምላሽ መስጠት የጀመረችው ወጣት ሄለን ሞገስ፤ በአዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ተወልዳ ያደገችና ሌላዋ የዛሬ እንግዳችን ነች።
እስከ አስረኛ ክፍል ድረስ ከተማረች በኋላ ለመሰናዶ ትምህርት መግቢያ ውጤት እንዳላመጣች የተረዳችው ወጣት የተወሰነ ዓመት በአረብ ሀገር ሰርታ የራሷ የምትለውን ድርጅት ለመክፈት ባላት ህልም የተነሳ በህጋዊ መንገድ ወደ ኩዌት አቀናች። በቤት ሰራተኝነት የተቀጠረችው ይች ወጣት ቀንና ሌሊት ተሰርቶ የማያልቀው የአረብ ሀገር ስራ የወገብ በሽተኛ እንዳደረጋት ትናገራለች።
በወር የምታገኘውን ገንዘብ በሙሉ ለቤተሰቦቿ በመላክ እጇ ላይ ምንም ገንዘብ ባለመኖሩ እስኪሞላ ቆይ ዛሬ ቆይ ነገ ስትል ለአምስት ዓመታት በከባድ የስራ ጫና ውስጥ ሰውነቷ ላይ ያለው ስጋ አልቆ በአጥንቷ የምትሄድ ሲመስል አሁን በቃኝ በማለት የያዘቻትን ይዛ ወደ ሀገሯ ተመለሰች።
ለማገገም ከዓመት በላይ እንደ ፈጀባት የምትናገረው ሄለን ሰውነቷ ተመልሶ መንፈሷ ሲረጋጋ ትዳር ይዛ እንደ ልጅ ለማፍራት በቅታለች። አሁንም በምግብ ዝግጅት ሙያ ስልጥና የራሷን ትንሽ ምግብ ቤት ለመክፈት ማቀዷን የተናገረች ሲሆን “ብልጥ በሰው ሞኝ ከራሱ ይማራል” የሚባለው ነገር እንዳይደርስብን ምንም ካላተረፍነው ከኛ ህይወት በመማር ራሳችሁን አድኑ በማለት ላልደረሰባቸው፤ ግን ደግሞ ስደትን ላሰቡ ወገኖች ታሳስባለች።
ለአብነት ያህል እነሱን አነሳን እንጂ የሀገራቸው መሬት እየናፈቃቸው በበረሃ ወድቀው የቀሩ፤ ከነሙሉ አካላቸው ተሰደው አካል ጉዳተኛ ሆነው የተመለሱ፤ በአቅም በጉልበታችን ሰርተን እንለወጣለን ብለው ከሀገራቸው ከወጡ በኋላ ያሰቡትና የሚሆነው አልገናኝ ብሏቸው አእምሯቸውን የሳቱትን ቤት ይቁጠራቸው።
ግፍ አንገፍግፏቸው እራሳቸውን ከፎቅ ላይ የሚወረውሩ፤ ህጋዊ ባልሆነ መንገድ ሄደው በደረሱበት ሀገር ያልተገባ እንግልት ላይ ከሚወድቁት በላይ የባህር ሲሳይ የሆኑትም ቁጥራቸው ቀላል አይደለም። ወጣትነት ጉልበት ነው። እድሜው በራሱ የሞከሩትን የሚያሳኩበት ባይሳካ እንኳን ተጨማሪ ተስፋዎች የሚታዩበት ነው።
በአፍላ የወጣትነት እድሜ፤ ሮጠው የማይጠግቡትን ያህል ጉልበት ሀገር ላይ አፍሶ ሀገርን ከማሳደግ ባለፈ ለምን አቅማችንን ላብ ወዛችንን ላልተመጣጠነ ክፍያ እናፈሳለን? ለምን አፍላውን እድሜያችንን አጠቃላይ ማንነታችንን በ”ህጋዊ ባርነት” እናጣዋለን? የነገ ተስፋና ጸጋዎቻችንን በራሳቸን እጅ ከማጨለማችን በፊት የነገ ራዕያችንን እንዴት በሀገራችን ማሳካት እንደምንችል ለማሰብ ከራሳችን ጋር እንማከር እላለሁ።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሐምሌ 25/2013