የጋዜጠኛው ቅኝት አምዳችን ላይ በጉዟችን የገጠመንን ስናሳያችሁ፤ የታዘብነው ስናስቃኛችሁ ጥሩውን ስናወድስ የሚስተካከለውንና የሚታረመውን ስንጠቁም ቆይተናል። ዛሬ በዚሁ አምዳችን ላይ በማህበራዊ ድረ ገፆች ማለትም ፌስቡክ፣ዩቱዩብ፣ ኢንስትግራም፣ቴሌግራምና የመሳሰሉት ላይ እራሳቸውን እኔ የማህበረሰብ አንቂ ነኝ ብለው የሾሙት ማህበረሰብም በሚያሰራጩት የተለያየ መረጃ የሚከተላቸውና የሚሉትን የሚመለከታቸው የማህበረሰብ አንቂዎች ላይ ቅኝት አድረገን አንደሚከተለው ዓይተናቸዋል።
ዛሬ ቅኝታችን ምድር ላይ ሳይሆን ሳይበር ላይ ሆኗል። በሳይበሩ ዓለም እነማን ምን መልካም ነገር ላይ ዘወተሩ እነማንስ ያገኙትን መልካም አጋጣሚ ለእነሱ እኩይ ተግባር መፈፀሚያ አደረጉት የሚለውን ለመቃኘት ወደናል። በጋዜጠኛ ዓይን እንዲሁ የሚታለፉ ጉዳዮች የሉም። የማህበራዊ ድረ ገፆች እና የዘመኑ መገናኛዎች አሁናዊ ሁኔታም ዓይተን ይህን ቢያስተካክሉ መልካም ነው። አያያዛቸውም ለአገር ለህዝብ ብሎም ለራሳቸውም መልካም አይደለምና እርማቱን ይውሰዱ ያስባለን መነፅራችን ያስመለከተንን ህፀፆችን እንሆ ብለናል።
አገር ለመገንባት ዘርፈ ብዙ ተዋናዮች በጋራ የሚያደርጉት ጥረት ወሳኝ ነው። በተለይም የማህበረሰቡን ንቃተ ህሊና ከፍ ለማድረግና በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ያለውን ግንዛቤ ለማስፋት ብሎም ምክንያታዊነት ለማላበስ ምቹ ናቸው። ችግሩ ግን በሌላ መልኩ እልፍ ምክንያት አልባዎች ማፍሪያ በርካታ የተሳሳተ መረጃዎች ማቅረቢያ ሲሆኑ ነው።
እነዚህ ማህበራዊ ድረ ገፆች ከሁሉም መረጃ አውታሮች በፈጠነ መልኩ ሰዎች ጋር በተለያየ መልኩ መረጃዎች ያደርሳሉ። በቴክኖሎጂ ታግዘው በስርጭት እና አጠቃቀም ቀለው በብርሃን ፍጥነት ከአንዱ ወዳንዱ መረጃዎችን ያደርሳሉ። መልዕክት ይቀባበላሉ። ታዲያ በስርዓት ከተያዙና ትውልድና አገር በሚገነባ መልኩ ከተገለገልንበት ትልቅ አስተዋፅዖ የሚያበረክተው ይህ ዘርፍ፤ ስርዓት አልበኝነት ከተንሰራፋበት የሚያስከትለው አደጋ ቀላል የሚባል አይደለም።
ቦታ ተሁኖ በአንድ ጊዜ ዓለም ላይ ስለተፈጠረው ሁኔታ መከታተል እና እየሆነ ያለውን ማሳየት በሚቻልበት ዛሬ ግለሰቦች የየራሳቸው ሚዲያ ከፍተው ሃሳባቸው ያጋራሉ። ይጠቅማል ያሉትን ለሌሎች ያስተላልፋሉ። ከእነሱ ጋር የሚመሳሰል ሃሳብ ካላቸው ጋር አብረው ይሠራሉ። ታዲያ በዚህ ሁሉ የሃሳብ ዝውውር ውስጥ በተለይ የማህበረሰብ አንቂዎች መልካም ነገር ለሌሎች ማቅረብ ሲጠበቅባቸው የእነሱን በጎ ያልሆነ አመለካከት እና እሳቤ ሌላው ላይ ለመጫን ሲሞክሩ ማየት እነዚህ አንቂዎች እውን ህዝብን ማንቃት ነው ተግባራቸው? ብለን ብዙ እድንጠይቅ ያደርጉናል።
እርግጥ እዚህ መድረክ ላይ ያለ ስስት ኢትዮጵያዊነትን የሚያነግሡ፣ አብሮ መኖርን የሚሰብኩ፣ እኩልነትና ፍትህ አገሪቱ ላይ ይሰፍን ዘንድ ሌተቀን የሚሠሩ መልካሞች ስንዘዋወር እንመለከታለን። በአንፃሩ ግን በማህበረሰቡ ዘንድ እጅግ የሚታወቁ የሚሉትና የሚለጥፉት ሁሉ ሌሎች ትክክል ናቸው ብለው የሚያምናቸው ግለሰቦች ከትክክለኝነት ብዙ የራቁ መረጃዎች እንካችሁ ሲሉ ይስተዋላሉ።
ወደላይና ወደታች እየተረተርን ማን ምን አለ በምንልበት ገፅ ላይ የምናገኘው መረጃ ሁሉ እውነት ነው ብለን ከተቀበልን፤ ማስረጃውን ያቀረቡት ግለሰቦች ዓላማቸው ምንድነው ብለን ካልመረመርን፤ በማንም በማንኛውም ጊዜና ወቅት ከኃላፊነት እና ከተጠያቂነት ስሜት በራቀ መልኩ እንኩ የምንባለውን ወደውስጣችን ካሰረፅን፤ ብሎም የተዛባውን መረጃ ይሁነኝ ብለን ከተቀበልን ስህተት ውስጥ መውደቃችን አይቀርም።
የማህበረሰብ አንቂ ነኝ ብሎ እራሱን የሰየመና በሌሎችም በተሳሳተ መረጃው በመታለል “አዎ ልክ ነህ” ተብሎ እውቅና የተሰጠው አንቂ ስለምን ያን አነቃዋለሁ ያለን ማህበረሰብ ከንቃት የሚለዝበው ተግባር መፈፀም ላይ ገባ። ግለሰቦችን አልያም ተቋማትን መዝለፍ፣ ያለ መረጃና ማስረጃ ማብጠልጠል፣ በሚዲያ ቀርቶ በድብቅ ሊነገሩ የማይገቡ መጥፎ ቃላትን እየተጠቀሙ የማህበረሰብን ባህል እና እምነት በሚፃረር መልኩ ለክፋት በማነሳሳት ተግባር ላይ ይገኛሉ።
ማህበራዊ አንቂዎች ለአገርና ህዝብ የሚጠቅም መልካም ነገሮችን በማንሳት ህዝብ እንዲወያይ በጉዳዮቹ ላይ ተነጋግሮ እንዲግባባ ማድረግ ዋንኛው ሥራቸው መሆን ይገባዋል። ነገር ግን ከዚህ በተለየ መልኩ ለህዝብ አለመግባባትና እርስ በርስ ግጭት መፈጠር ምክንያት የሚሆኑ ፅሑፎች በገፆቻቸው ላይ ያለ ሀፍረት አስፍረው ለፀብ ያነሳሳሉ።
እነዚህ ማህበራዊ ሚዲያን ተጠቅመው አካባቢያዊና አለማዊ ሁናቴን በቁጥጥር ውስጥ በማዋል ህዝብን በተሳሳተ ምልኩ በማነሳሳት የተዛባና ተጨባጭ ያልሆነ መረጃ በመስጠት እነሱ በስውር የሚፈልጉትን ዓላማ ያስፈፅማሉ። ማህበረሰቡ በማህበራዊ ሚዲያዎቹ ትክክለኛነትና እውነታ ላይ ያልተመሰረተ መረጃ በመታለል በግብታዊነት የተሳሳተ እንቅስቃሴና ጉዳት በሌሎች ላይ ለማድረስ ይነሳሳል።
እርግጥ ነው ሰላምን ሰባኪ፣ እውነትን መሰረት አድርገው አገር እንድትቀና ህዝብ እንዲለወጥና በኑሮው እንዲሻሻል የሚጥሩ፣ የእውነት የሚያነቁ ግለሰቦች ብሎም ተቋማት አሉ። የሚገርመው ግን ህዝብና ተከታያቸው ከልክ በላይ የተዛባና የተሳሳተ መረጃ የሚያቀብሉና የሚቀበሉት በዚህ ገፅ እጅጉን ንቁ ተሳታፊ ናቸው። ያለ ትክክለኛ ምክንያት ሃሳባቸውን አቅርበው ወደተሳሳተ መንገድ የሚጠቁሙ የሚከተላቸውና የሚያጅባቸው ቀላል አይደለም።
ሰሞኑን አገር ምድሩን ግራ የሚያጋቡ መረጃዎችን በመፈብረክ፤ ለጊዜውም ቢሆን ብዙዎችን ያስከተሉ እውነታነት የሌለው መረጃቸውን ለብዙዎች አዳርሰው አገርና ህዝብ በመንግሥት ላይ እምነት እንዳይኖረው እያደረጉ ያሉ ግለሰቦች ለዚህ ዋንኛ ማሳያዎች ናቸው። በተለይ የመከላከያ ሠራዊቱ ከትግራይ መውጣቱን ተከትሎ ለምንና እንዴት ስለ ምን ዓላማ የሚሉትን የጠራ መረጃ ሳይዙ የራሳቸውን መደምደሚያ በመስጠት ህዝብን ያደናገሩ ብዙዎችን ታዝበናል።
በእርግጥ ከመንግሥት በኩል ስለምን መከላከያው ከክልሉ እንደለቀቀ የወጣው መረጃ ማህበረሰቡ በተብራራ መልኩ አለመራዳቱና የተሻለ ግንዛቤ አለመያዙ እነዚህ የማህበራዊ ሚዲያ ዘማቾች ለጊዜውም ቢሆን ህዝቡን አደናግረውት ቆይተዋል። ዛሬም ከተሳሳተ ተግባርና ከእኩይ ዓላማቸው ሊታቀቡ አለመቻላቸው ሲታይ ምን ያህል ለአገርና ለህዝብ ለውጥ እንቅፋት መሆናቸው ማየት ማህበረሰብ አገርን ይመስላልና እጅጉን ንቁ ለአገር መከታና ጥላ የሆነ ትውልድ ይበረክት ዘንድ በዘመኑ እንደ አሸን የፈሉት የማህበራዊ ድረ ገፅ ተዋናዮች በጎ ሚናና በጎ ማንቃት ወሳኝ ነው። ተጨባጭ በሆነ መረጃ ላይ ተመስርተው ለህዝብና ለአገር ጠቀሜታቸው ተረጋግጠው የሚዘዋወሩ መረጃዎች መበርከታቸው ግድ ይላል።
ከስሜት እና ጊዜያዊ የግል ጥቅምን ችላ ብሎ የአገርና የህዝብ ደህንነትን መጠበቅ ዛሬ እዚህም እዚያም የሃሳብ መረጃን በማሯሯጥ ላይ ካሉ አንቂ ነኝ ባይ አለዛቢዎች ይጠበቃል። አገር በዜጎች መልካም አስተሳሰብ የምትቀና ናት። በተሳሳተ እሳቤና በክፋት አስተሳሰብ ደግሞ የምትለዝብ። የማህበረሰብ አንቂ ማህበራዊ ንቃት እንዲሰርፅና ለውጥ እንዲመጣ የሚጥር እንደመሆኑ በጎ አስተሳሰቦችን በስፋት የሚያቀብል ሰላም እንዲሰፍንና አንድነት እንዲጎለብት መትጋት ይጠበቅበታል።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሰኔ 26/2013