የዛሬ የሳምንቱን በታሪክ አምዳችን ከ85 ዓመታት በፊት የተፈጸመውን የአርበኞቻችን ድል መታሰቢያ፤ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ለአፍሪካና ለመላው ጥቁር ሕዝቦች ነጻ መውጣት የከፈሉትን መስዋዕትነትና ያደረጉትን ብርቱ ተጋድሎ ይመለከታል፤ የኛ የአፍሪካና የመላው የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ህያው ቅርስ የትውልዶች አሻራና መታሰቢያን ይዘክራል::
በለው በለው፣
አትለውም ወይ አትለውም ወይ፣
ለዚህ ላታላይ ትሰጋለህ ወይ፣
ኧረ በለው በለው!
አትለውም ወይ አትለውም ወይ፣
ጥቁር አንበሳ አይደለህም ወይ፣
አትለውም ወይ አትለውም ወይ፣
የአድዋ ጀግኖች ቅርስ አይደለህም ወይ?፣…. የሚሉት ወኔ ቀስቃሽ ስንኞች የጥቁር አንበሳ ማህበር ከሚያዜማቸው ግጥሞች ውስጥ ጥቂቶቹ ናቸው:: በእርግጥ የማንነት ታሪካችን ከአንበሳ ጋር የተዛመደ መሆኑን ነገራትን በማጣቀስ ይዘፈናል:: ጥቁር አንበሳ በኢትዮጵያ ነባራዊ ታሪክ ውስጥ ያለውን ጉልህ ሚና በዘፈን ስንኞቹ በቀጥታ የገለጹ እንደ አብዱኪያር ያሉ ባለውታዎቻችን ይጠቀሳሉ:: ለመሆኑ ጥቁር አንበሳ ማነው? ምንድነው?
የአምስት ዓመቱን የኢትዮጵያውያን የነፃነት ተጋድሎ በሙሉነትና በፅናት ከታገሉ ድርጅቶች ውስጥ ቀዳሚው “ጥቁር አንበሳ” የተሰኘው የወጣት አርበኞች ድርጅት ነው።
ተፈሪ ዓለሙ “ትዝታ ዘ አራዳ” በሚለው የሸገር ፕሮግራም ላይ እንዳስደመጠው፤ በዳግም ጣሊያን ወረራ ወቅት ሁሉም አገሩን ሊታደግ በዱር በገደሉ ሆኖ ወራሪውን በፈተነበት በዚያ ዘመን የሆለታ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የጦር ትምህርት ቤት ሰልጣኝ የጦር መኮንኖች ከወታደሮች ጋር መቀመጫቸውን ነቀምት ላይ አድርገው የመሰረቱት ድርጅት ነው፤ ጥቁር አንበሳ::
የፋሺስት ኢጣሊያ ጦር አገራችንን ከመውረሩ ቀደም ብሎ በየትምህርት ቤቱ የተመለመሉ ወጣቶች በሆለታ ገነት ተሰብስበው የጦር ትምህርት እንዲሰጣቸው ተደረገ:: እነዚህ የጦር ትምህርት ቤት ምልምሎች በወረራ ወቅት ታላቅ ተጋድሎ ፈጽመው ከፍተኛ መስዋዕትነትን ከፍለዋል::
እነዚህ የመጀመሪያዎቹ የገነት ጦር ትምህርት ቤት ወጣቶች ኋላ ጥቁር አንበሳ የሚል ስያሜ ይዘው የፋሺስት ኢጣሊያን ጦር ሲፋለሙ በአሰቃቂ ሁኔታ ተገለዋል፤ ቆስለዋል፤ ታስረዋል :: የእነዚህን ለጋ ወጣቶች ገድል ልንዘክር ወደናል :: የእዚያ ዘመን ወጣቶች ወኔና ተጋድሎ ለዛሬ ትውልድ ትልቅ ምሳሌ ሆኖ ተከትቧል::
የድርጅቱ አባላት በአብዛኛው ሆለታ ከተቋቋመው ከመጀመሪያው የኢትዮጵያ የጦር ትምህርት ቤት የተመረቁ ወጣት መኮንኖች ሲሆኑ፣ የድርጅቱን ፖለቲካዊ አመራር የያዙት እንግሊዝ አገር ተምረው የተመለሱ ወጣት ኢትዮጵያውያን ናቸው ። በአመራርነት ከንቲባ ገብሩ እና ይልማ ደሬሣን ጨምሮ ስመጥር የጦር መኮንኖች እና ሲቪሎች የነበሩ ሲሆን ወታደሮቹን በበላይነት ያሰለጥኑ የነበሩት ሌ/ኮ/በላይ ኃይለ አብ እንደነበሩ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ::
የማህበሩ ዋነኛ አላማ በውጊያ ጠላትን መፈናፈኛ ማሳጣት፤ ለአገር መሞት ብሎም ወጣቶችን ለሀገራቸው ዘብ እንዲቆሙ መቀስቀስ ነው ። ጥቁር አንበሳ ድርጅት የራሱ እጅግ ጠንካራ መተዳደሪያ ደንቦች ነበሩት:: በክህደት ለተገኘ አባል ፍርዱ ሞት የሆነ። በተጨማሪም አባላቱ በጠላት እጅ ከሚወድቁ ይልቅ ሞትን እንዲመርጡ ሁሉ ይደነግጋል።
ኢትዮጵያውያን ወጣቶች የመሠረቱት የጥቁር አንበሳ ጦር በነቀምት አካባቢ የሰፈረ የኢጣሊያ ጦር አየር ኃይል ላይ ጥቃት ከፍቶ በእሳት ያወደመው ከ85 ዓመታት በፊት በዚህ ሳምንት ሰኔ 20 ቀን 1928 ዓ.ም ነበር።
የግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ 127ኛ ዓመት ልደት በዓል በተከበረበት ሥነ ሥርዓት ላይ ኮሎኔል ገብረእግዚአብሔር ‹‹በግርማዊነታቸው ዘመነ መንግሥት የዘመናዊ ጦር ኃይሎች አመሠራረትና አደረጃጀት›› በሚል ርዕስ አንድ ጽሑፍ አቅርበው ነበር። ታደሰ ገብረማርያም የተባሉ ጸሐፊ ይህን ጽሑፍ ጠቅሰው ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ እንደጻፉት፣ 148 ወጣቶችም ለዕጩ መኮንንነት ኮርስ ተመልምለው ጥር 21 ቀን 1927 ዓ.ም. ለሥልጠና ገነት ጦር ትምህርት ቤት እንዲገቡ ተደርጓል::
ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ ምልምሎቹን በታላቁ ቤተ መንግሥት ተቀብለው አሸኛኘት ባደረጉላቸው ወቅት ‹‹ቤት ያለምሰሶ ሊቆም ወይም ያለ ግድግዳ ከቁር ሊያድን እንደማይችል ሁሉ የጦር ኃይል የሌለው አገር ከአደጋ ሊሰወር አይችልም›› በማለት ዕጩ መኮንኖቹ የተጣለባቸው ኃላፊነት ከፍተኛ መሆኑን አስገነዘቧቸው። ሥልጠናው ግን ልዩ ልዩ እንቅፋቶች ስለተጋረጡበት በተያዘለት የጊዜ ሰንጠረዥ መሠረት አልተካሄደም።
ዋነኛው ጋሬጣ የፋሺስት ጣሊያን ጦር በደቡብ በኩል ድንበር ጥሶ ለመግባት መሰናዶ እያደረገ መሆኑንና በሰሜን በኩል ደግሞ መረብ ወንዝ ተጠግቶ መስፈሩ መታወቁ ነው። ሁለተኛው እንቅፋት መንግሥት ቤልጅግ ከሚገኘው ‹‹ፋብሪካ ናሲዮናል›› እንደ ረጃጅምና አጫጭር ጠመንጃዎች ፣ መትረየሶች፣ መድፎች፣ ብረት ለበስ የጦርና መጓጓዣ ተሽከርካሪዎች ያሉ ልዩ ልዩ ዓይነት የጦር መሣሪያዎችን ለመግዛት ያደረገው እንቅስቃሴ መክሸፉ ነው። ግዥው ያልተሳካውም እንግሊዝ፣ ፈረንሣይና ጣሊያን ማናቸውም የጦር መሣሪያ በቅኝ ግዛቶቻቸው አልፎ ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገባ ቀደም ብለው በ1922 ዓ.ም ማዕቀብ በመጣላቸው ነበር።
ኢትዮጵያ ግዢው ባይሳካላትም ከ40 ዓመት በላይ ዕድሜ ባለው አሮጌ የጦር መሣሪያ ወረራውን መከላከል የሚያስችል ዝግጅት አድርጋ ለዘጠኝ ወራት ያህል በሥልጠና ላይ የቆዩት ዕጩ መኮንኖች ሥልጠና አቋርጠው በመውጣት የጦሩን አመራር እንዲይዙ አደረገች።
ሁለት ሬጅመንት፣ የትምህርትና ሥልጠና መምሪያና ልዩ ልዩ ኪነታዊ ክፍሎች ያሉት አንድ ብርጌድ እንዲቋቋም ተደረገ። ብርጌዱም ‹‹ኃይለሥላሴ ብርጌድ›› የሚል ስያሜ ተሰጠው። የብርጌድ ኃይለሥላሴ ዋና አዛዥ ሌተናል ኮሎኔል ክፍሌ ነሲቡ፣ ዋና ኤታማዦር ሹም ሌተናል ኮሎኔል ነጋ ኃይለሥላሴ፣ የአንደኛ ሬጅመንት አዛዥ ሌተናል ኮሎኔል ከተማ በሻህ፣ የሁለተኛ ሬጅመንት አዛዥ ሌተናል ኮሎኔል በላይ ኃይለአብ እንዲሆኑ ሹመትና ኃላፊነት ተሰጣቸው። ስዊድናውያን አሠልጣኞች ደግሞ በአማካሪነት ተመደቡ።
የፋሺስት ጣሊያን ጦር መስከረም 1928 ዓ.ም. በኦጋዴን፣ በደቡብና በሰሜን ወረራውን በይፋ መጀመሩን ተከትሎ መስከረም 25 ቀን 1928 ዓ.ም አዲግራትን ያዘ። ግርማዊነታቸውም ወደ ሰሜን ጦር ግምባር ዘምተው ጊዜያዊ ማዘዣ ጣቢያቸውን ደሴ ላይ አደረጉ። ብርጌድ ኃይለሥላሴም በፍጥነት ወደ ውጊያው ገብቶ ከክብር ዘበኛ ጦር ጋር እንዲሠለፍ ቢታዘዝም ማይጨው ላይ ተፈታ።
ጃንሆይ ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ የፋሺስት ጣሊያን ጦር ቀድሞ አደጋ እንዳያደርስ በማሰብ የብርጌድ ሁለተኛ ሬጅመንት ጣርማ በር ላይ የጠላትን ጉዞ እንዲገታ የተደረገ ሲሆን፣ አንደኛው ሬጅመንትም ሚያዝያ 25 ቀን 1928 ዓ.ም. አዲስ አበባ ገባ። ጃንሆይም የስዊድን መኮንኖችን አስጠርተው ስለመልካም ተግባራቸውና ዕርዳታቸው ካመሰገኗቸው በኋላ የቅጥር ውላቸው መሠረዙን ገልጸው አሰናበቷቸው። ከዚህ በኋላ ጃንሆይ ወደ ጂቡቲ ተጓዙ።
ብርጌዱም ወደ ሆለታ አቅንቶ ትግሉን እንደቀጠለ፣ በትግሉም በርካታ ሲቪሎች እየተቀላቀሉት ‹‹የጥቁር አንበሳ ጦር›› የሚል መጠሪያ ይዞ በጠላትም ላይ የሽምቅ ውጊያውን አፋፋመ። ሰኔ 20 ቀን 1928 ዓ.ም በነቀምት አካባቢ የሰፈረ የኢጣሊያ ጦር አየር ኃይል ላይ ጥቃት ከፍቶ በእሳት በማውደም ድል ተቀዳጁ። የጥቁር አንበሳ አርበኞች የፋሽስት ኢጣሊያን ጦር ሲፋለሙ በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድለዋል፤ ቆስለዋል፤ ታስረዋል እንዲሁም ግዞት ተግዘዋል።
ቢቢሲ ግንቦት 5 ቀን 2011 ዓ.ም ባቀረበው ዘገባ ‹‹ለታሪክ የተቀመጡትና በጥቁር አንበሳ አርበኞች ድባቅ ተመተው የወረዱት የጣሊያን አውሮፕላኖች ቅሪት እስካሁን አለ። የድሮ ቀለማቸው ወይም ሙሉ ቅርፃቸው ለቆና እንዳልነበሩ ቢሆኑም የድሉ ምልክት መሆናቸውን እንደቀጠሉ ነው። በተለይ “በምሥራቅ ወለጋ ላሉት የቦኒያ ሞሎ ነዋሪዎች ልዩ ትርጉም አለው” ሲል ወደ ወለጋ በማቅናት ያነሳቸውን በጥቁር አንበሳ አርበኞች ተመተው የወደቁ አውሮፕላኖች ስብርባሪ አካሎች የሚያሳዩ ፎቶግራፎች የያዘ ጽሑፍ በድረ ገጹ መለጠፉንም አዲስ ዘመን ጋዜጣ ከዚህ ቀደም አስፍሮታል::
በእርግጥ ኢትዮጵያውያን ካልነኳቸው በስተቀር በሌላው ላይ የማይደርሱ፣ ለነጻነታቸው ቀናዒ፣ ሠላማዊ፣ ጀግና የአኩሪ ቅርስና ታሪክ ባለቤት ሕዝቦች መሆናቸውን ታሪክ የመሰከረ ሀቅ ነው:: የነዚህ ጀግኖች አባቶቻችን አኩሪ ታሪክ ተከፋይና ወራሽ የሆንን እኛ ለዚህ ክብር ያበቁንን የባለውለታዎቻችንን ታሪክ ከፍ ማድረግ ተገቢውን ክብርም ልንቸራቸው ይገባል::
የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ፍቅርና ክብር ለዚህ ነጻነትና ክብር ላበቁን ጀግኖች አርበኞቻችን ሁሉ ይሆን ዘንድ ምኞቱን ይገልጻል::
አዲሱ ገረመው
አዲስ ዘመን ሰኔ 20/2013