ኢትዮጵያዊያን በየዘመኑ የራሳቸው የሆነ የፋሽን ጥበብ ተከትለው ዘመኑ ያቀረበላቸውን መልክ ተላብሰው ቆይተዋል። በተለይ ዛሬ ላይ እጅግ ሰፍቶና እንዲህ በየቦታው ቴክኖሎጂ ያበረከታቸው የውበት መጠቀሚያዎች ከመፈጠራቸው በፊት አባት እናቶቻችን የራሳቸው የሆነ ልዩ የመዋቢያ መንገዶችን ፈጥረዋል።
ባሳለፍነው ሳምንት በዚሁ አምድ የሴት ኢትዮጵያዊያን የፀጉር አሰራር የተመለከተ ፅሁፍ ማቅረባችን ይታወሳል። ዛሬ ደግሞ ወደ ወንዶች ተሻግረን ከትናንት የፀጉር አሰራርና ፋሽን ዛሬ እስካለው ገፅታ ድረስ በአጭሩ ለመዳሰስ እንሞክራለን።
ኢትዮጵያዊያን አባቶች ፣ወጣቶችና ልጆች በየዘመናቱ በተለያየ መልኩ በፀጉር አያያዝና በየዘመኑ ፋሽን አምረው ታይተዋል፤ በዘመናቸው የውበት አክሊልን ደፍተዋል። በተለይም ከአልባሳትና ማጋጌጫቸው በላቀ ልክ እንደ ወይዛዝርትና እናቶች ሁሉ ኢትዮጵያውያን ጎበዛዝትና አባቶች የተለየ የፀጉር አሰራር ቁርጥና አንክብካቤ በየጊዜው ተጠቅመዋል።
ከኢትዮጵያዊያን በተለየ በዓለም ዙሪያ ወንዶች በየዘመናቱ የተለያየ አይነት የፀጉር አሰራርና አቆራረጥ ሂደቶችን አልፈዋል። እንዲህ እንደ ዛሬ በተለያዩ ቦታዎች ወንዶች ፀጉራቸውን የሚቆረጡበትና የሚንከባከቡበት ዘመን ላይ ከመደረሱ በፊት የፀጉር አሰራርና እንክብካቤ ጅማሮ የነበረው ቤተመንግስት ውስጥ በንጉሶችና በልዑሎች ዘንድ እንደነበር የታሪክ መዛግብት ያመላክታሉ። በተለይ የጥንት የሮማውያን ንጉሶች በፀጉር አያያዝና እንክብካቤ እንዲሁም ልዩ የሆነ አሰራር ከሌላው ተራው ህዝብ በተለየ ይታዩ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ። ቀስ በቀስም ይህ በንጉሳውያኑ ዘንድ የተለመደው የፀጉር አሰራር በተራው ህዝብ ዘንድ እየተለመደ መጣ።
ወንዶች ፀጉራቸውን በማስረዘም በተለያየ መልኩ በማስያዝ ይዋቡ ነበር። ከዚያ በፊት ወንዶች የተለያየ የፀጉር አስራር የሚከተሉ ሲሆን በተለይም በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የወንዶች ፀጉር ማስረዘም እንደ ነውር ይቆጠር ነበር። ይህ ፀጉርን የማስረዘም ነውርነትና አለመወደድ በ17ኛው ክፍለ ዘመን መልሶ እንደ አዲስ ተለምዶ ፋሽን ሆነ።
በተለይም ከ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጅማሮ አንስቶ ደግሞ አዲስ የአቆራረጥ ስልት ይተገበር ጀምር። በተለይም የእግር ኳስ ተጫዋቾችን የመርከብ ሰራተኞች በተለያየ የፀጉር አቆራረጥ ስልት ይታወቁ ነበር። እነዚህ የእግር ኳስ ተጫዋቾች ከአንዱ አገር ወደሌላው የሚጓጓዙት የመርከብ ሰራተኞች ሌላው ህዝብ እነሱን እየተመለከተ የሚሰሩትን የፀጉር ቁርጥና አሰራር እየተከተለ በራሱ ይተገብረው ጀመር።
እኛ ኢትዮጵያዊያን ጋ ጥንት በተለያዩ አካባቢዎች የነበረው እንደ አፍሮ ያለው የጸጉር አቆራረጥ በተለይም በ1950 በተለያየ ዓለም ወንዶች የሚዋቡበት ፋሽን ነበር። ከዚያ በፊት በተለይም በ1920ዎቹ አብዛኛዎቹ ወንዶች ፀጉራቸውን በመላጨትና ኮፊያ በማድረግ ይዋቡ ነበር። በተለይም በወቅቱ ይወጡ በነበሩ ፊልሞችና ሲኒማዎች ገፀባህሪያት ላይ የሚታዩ የፀጉር ማስረዘምና መልከ ብዙ ቁርጦች በብዙዎች ዘንድ እየተለመደ መጥቷል።
ወንዶች በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የፀጉር አሰራርና ፍሸና ልዩ የሆነ የእድገትና የመሻሻል ዘመን ሆነ። ለበዓላትና ለአዘቦት ቀን በልዩ ልዩ ወቅትና ቦታ ሁኔታው የሚፈቅደውና በዚያ ቦታ የተለመደ መልክና ቀለም ያለው የፀጉር አቆራረጥ ይከተሉ ጀመር።
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የወታደሮች የፀጉር አቆራረጥ ስልትም በብዙዎች ተተግብሯል። ይህም ፀጉር እጅግ በጣም አሳጥሮ እኩል በሆነ መልኩ የሚቆረጥበት ስልት ነበር። በተለይም በ1950 የፊልም ሰሪዎች የፀጉር አቆራረጥ ስልት በስፋት እንደ ፋሽን ተቆጥሮ በብዙዎች ተመርጦ ተተግብሯል። በተለይም በስፖርት በሙዚቃና በፊልም ኢንዱስትሪ ውስጥ ዝነኛ ሰዎች ምክንያት በስፋት አዳዲስ ፋሽን ይተዋወቅና ይተገበር ጀመር።
ወደኛ አገር ስንመለስ ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው የፀጉር አሰራር ዘመናትን ተሻግረዋል። ሹሩባቸውን ስናይ ማንነታቸውን ጎፈሬያቸውን ስንመለከት ዘመናቸውን ያስታውሰናል። የአርበኞች ጎፈሬ፣ የንጉሶች የፀጉር አሰራር፣ የወጣቶች ቁንጮ ፣የጎበዞች ሹሩቧ ኢትዮጵያዊያን እንደየወቅቱ ዘመኑን መስለው ተውበው የታዩበት ፋሽን ነበር። ጎፈሬ እኛ ዘንድ ብርቅ አልነበረም ፤መፈረዝም የተለመደና ሌሎች ጋር ተዟዙሮ ቆይቶ በአዲስ መልክ የተለመደ እንጂ ለዘመናት መዋቢያ እንደነበር ማሳያ መጥቀስ ይቻላል።
የአፋር ወጣቶች በአካባቢያቸው ያገኙትን ዕፅዋት ተጠቅመው ከተማ ላይ ፀጉር ከመፈረዛችን በፊት ከጥንት ጀምሮ አምረው ታይተውበታል፤ተውበው አጊጠውበታል። እዚህ ከተማ ውሎ አድሮ ከዚያ ተኮርጆ ፋሽን ሆኖ ይሄው ዛሬም ተሻግሯል።
አሁን ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች እና አባቶች ብሎም ልጆች የተለያየ የፀጉር ቁርጥ ፋሽንን ይከተላሉ። በዚያም ዘመናቸውን መስለው ከተለያየ አለባበስና ወቅት ጋር የሚሄድ ከራስ ቅልና ከፊታቸው ገፅታ ጋር የሚያምረውን ከፀጉር ስራ ባለሙያ ጋር ተማክረውና መርጠው ይሰራሉ። በዚያም አምረውና ደምቀው ይታያሉ።
የወንዶች የጸጉር ቁርጥ ምርጫ እንደ እድሜያቸው የተለያየ እንደሆነ የፀጉር ስራ ባለሙያዎች ይናገራሉ። በየጊዜው የሚለመዱ የፀጉር ቆረጣ ስልቶች ወይም ፋሽኖች በአብዛኛው በወጣቱ የሚተገበሩ ሲሆኑ እድሜያቸው ከፍ ያሉትና በአነስተኛ የእድሜ ደረጃ የሚገኙ ወንዶች የሚቆረጡት የፀጉር አይነት የተለመደና ብዙም ወጣ ያላለ መሆኑን ባለሙያዎቹ ያስረዳሉ።
ወጣት ሰለሞን አየለ ከአምስት ዓመታት በላይ በፀጉር ስራ ቆይቷል። በወንዶች ፀጉር ስራ ላይ ዓመታትን እንዳሳለፈ ባለሙያ ደንበኞቹ ወደፀጉር ማስተካከያ ሳሎኑ ሲመጡ የሚሰሩትን የፀጉር ቆረጣ ስልት ወይም እነሱ “ስታይል”ይሉታል ያማርጣቸዋል። በእርግጥ ደንበኞቹ ከሆኑ የሚወዱትና የሚያዘወትሩት ስለሚታወቅ በዚህ እንደማይቸገርና በቀጥታ የተለመደውን ቁርጥ እንደሚሰራ ያስረዳል።
እንደ ፀጉር ባለሙያው ገለፃ፤ የፀጉር አቆራረጥ ፋሽን እንደ ወቅትና ጊዜው ይለያያል። ክረምት ላይ አሳጥሮ መቁረጥ ይቀንሳል። ከዚህ ይልቅ ፀጉር ባለበት መንከባከብና ቅርፁን ማስተካከል ያዘወትራል። በአንፃሩ ደግሞ በጋ ላይ አጥሮና በተለያየ ቅርፅ መሰራት ተለምዷል። ይህም የብርድና የሙቀት ወቅት መሆኑ የፈጠረው ልዩነት ነው።
ዛሬ ላይ የፀጉር ማስተካከያ ቤቶች ተበራክተው ብዙዎች መተዳደሪያቸው ሆኗል። ሳሙኤል ከበደ ቄራ አካባቢ የራሱ የወንዶች የውበት ሳሎን ባለቤት ነው። ከሌሎች የሙያ አጋሮቹ ጋር ፀጉር ሲያስተካክል አግኝቼው ስለሚያስተካክለው የፀጉር ቁርጥና ስለስራው አወራሁት። በአብዛኛው በተለይም በወጣቶች የሚመረጠው “ፌድ” የሚባለው ሲሆን አይነቱም የተለያየ ነው። በተለይ “ሎ ፌድ” የሚባለው የፀጉር አሰራር አይነት በብዙዎች ይወደዳል።
እድሜያቸው ከ18 እስከ 30 ዓመት የሚደርስ ወጣቶች በአብዛኛው የፀጉር ፋሽን ተከታይ መሆናቸውን የሚገልፀው ሳሙኤል፣ የተለያዩ የፀጉር አቆራረጥ ሰልቶች መኖራቸውን ያስረዳል። የፀጉር ስልቶቹ ፓንክ(በወጣቶች የሚመረጥ)፣ፍሪዝ፣ዜሮ በአንድ ቁጥርና በሁለት ቁጥር በአጭርና መካከለኛ አጭር(የመቁረጫ ጥርስ ነው)አፍሮ፣ ጆንትራ ቮልታ፣ባላቶሊ የመሳሰሉት የፀጉር ስራ ባለሙያዎቹ ለብዙዎቹ በምርጫነት የሚሰሩት የፀጉር አቆራረጥ ስልቶች ናቸው። አሁን ላይ ከሌሎች የስራ ዘርፎች ጋር ሲነፃጸር የፀጉር ስራ እጅግ አዋጭና ለብዙዎች ገቢ ማግኛ መሆኑን በስራ ወቅት ካናገርናቸው ባለሙያዎች መረዳት ችለናል። አበቃሁ፤ ቸር ይግጠመን።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሰኔ 14/2013