በዛሬው የወጋ ወጋ አምዳችን ጥሩ ስራዎችን አበረታትን፣ ለጥሩ ዋጋ ሊከፈለው እንደሚገባ አስገንዝበን ፣ ይህን ያላደረጉትን ወጋ ወጋ እናደርጋለን። በምንም ጉዳይ የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ይቻል ዘንድ የተሰራውን ማበረታታት አንድ ነገር ሆኖ፣ ሳያበረታቱ የተገኙት መንገዳቸው ትክክል እንዳልሆነ በማሳየት የማበረታት ባህል እንዲለምዱ ማድረግ ይገባል። አንድ ጉዳይ በወጋ ወጋ ስናነሳ አላማችን ሰዎች እንዲታረሙ ነው። የነገርን ሌላ መልክ ተገንዝበው፣ ለመልካም ነገር ጥሩ አተያይ እንዲኖራቸው ያደርጋል የሚል እምነት አለን።
ዛሬም አንድ ጉዳይ በማንሳት የማይጠቅሙ ነገሮችን ወጋ ወጋ እያረግን በመርፌያችን ለማከም ወደናል። ሰሞኑን በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ምርቃ ሚዲያዎችን አጨናንቆ ሰንብቷል። ግዙፍ ፕሮጀክቶች ፣ሌሎች ሰው ሰው የሚሸቱ እንዲሁም የመሰረተ ልማት ሲመረቁ በመገናኛ ብዙሃኑ ተመልክተናል። ፕሮጀከቶቹ በፌዴራል መንግስት፣ በክልሎች እንዲሁም በግሉ ዘርፍ ጭምር የተገነቡ ፕሮጀክቶች ናቸው።
በእርግጥ እንደ ታዳጊ አገር ህዝቡንና ሀገሪቱን የሚጠቅሙ ግዙፍና ሌሎች ፕሮጀክቶችን መገንባት ብሎም መጨረስ መቻል ትልቅ እምርታ ነው። በአገር ግንባታ ሂደት ውስጥ የሚጣሉ አሻራዎች በማንም ተሰሩ አልያም ማንም አቅዶ አሻራውን አሳረፈባቸው ውጤቱ የአገር ለውጥ ነውና በበጎነት መመልከትና ለዚያም የራስን በጎ ሚና መጫወት ይገባል።በጥረት የሰሩትን ማድነቅ በትጋት ለተለፋበት እውቅና መስጠት ደግሞ ከእኛ የሚጠበቅ የመልካም ስራ ክፍያ ነው።
ከዚህ በተፃራሪ ቆሞ የሰሩትን ማነተብ የጣሩትን ማንኳሰስ ተገቢ አለመሆኑ ላይ ነው ትኩረታችን። አንድ የሚያስማማን የጋራ ነጥብ ወይም ጉዳይ አለ፤ያም በጎና መልካም ነገር ለሁሉም ሁሌም መልካም ነው። በጎን መጥፎ ነው ብሎ ማሰብ አልያም ብርሀንን በጭለማ መስሎ ማቅረብ ግን ከትክክለኛነት መራቅ ነው። እንዴት አንድ ሰው ወይም አካል በአይኑ የተመለከተውን አልያም ቀርቦለት ያለን የተሻለ ነገር ለማጥላላት ይሞክራል?
ጉዳዮችን አንስቶ በዚያ ጉዳይ ላይ ያለን የተሻለ አተያይ ወይም እሳቤ በወጉ ማቅረብ አልያም ያ ተግባር የተሳሳተና ሊታረም የሚገባው ነው ብሎ መጠቆም ችግር የለውም፤ ገንቢ ነው። የሚያስተዛዝበው ጥሩን ተመልክቶ አለማድነቅ ይባስ ብሎም ያንን ማጥላላት ነው። መስቀል አደባባይ ላይ በተሰራው ስራ ያልተደሰተ፤ የነበረውን የተሰላቸ ገጽታ መቀየር ያልወደደ፤ ለተጠቃሚው ምቹ ለአገር ገፅታ ግንባታ ለመዲናዋ ሌላ ድንቅ ውበት መሆኑን ያላመነ ግለሰብ ወይም አካል ኢትዮጵያን እወዳለሁ ሊል እንዴት ይቻለዋል።
የሸገር ፓርኮችን መሰራት የተቃወመ፤የአዳዲስ መናፈሻ ስፍራዎች መገንባት፣ የነባሮቹ ለተጠቃሚ ምቹ መደረግ ያልተመቸው፤የቸርቸር ጎዳና ማማር ለተጓዦች ምቹና ፅዱ መሆን ያላስደሰተው ኢትዮጵያዊ ስለዚህች አገር መልካም መሆን ቢያስብ ፣ስለ ህዝቡ ያገባኛል እያለ ቢሞግት ማን ሊሰማው ይችላል? መልካም የሰሩትን ማበረታት ቢያቅት እንዴት ዝም ማለት ያቅታል፤ የራስን በጎ ሚና አለመጫወትና በበጎው ተግባር አለመሳተፍ አንድ ችግር ሆኖ ፣ በልማቱ የተሳተፉትንና ያለሙትን ማንኳሰስ ምን አይነት በሽታ ነው?
የቀረበልንን ብሩህ ገፅታ ትተን አሻግረን ጭለማ መመልከት ካዘወተርን አመለካከታችን የጤነኛ አይሆንም። አንድ መልካም ስራ በመልካምነቱ አይቶ ለስራው ተገቢውን መልካም አተያይና አስተያየት መስጠት ጤነኛ ያሰኛል። በአገር ግንባታ ሂደት ውስጥ እንደ መገኘታችን በትጋትና በብዙ ጥረት ከስኬት ደርሰው ለምርቃ የበቁና በመጠናቀቅ ላይ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ማድነቅ፣ መጠናቀቃቸውን በጉጉት ለሚጠብቀውም የራሳችንን አስተዋፅኦ ማድረግ ሲገባን መንቀፍና አቃቂር እየፈለጉ የፕሮጀክቶቹ አስፈፃሚዎችን ማጥላላት አይገባም።
እኔ በሌላው አካል የሚተገበር አልያም የሚሰራን አገር ሊጠቅም የሚችል ነገርን በተሳሳተ እይታ ለመመልከት ምንስ ያህል ሞራል ሊኖረኝ ይችላል? ሀሳቤ ይህ ከሆነ የተሳሳተ መንገድ ላይ ነኝ ማለት ነው። በጎ ነገር በማንም ተተገበረ በማን በጎነቱን ካልመሰከርኩ የቆምኩበት ሚዛን ትክክለኛ መሆኑ ማመን ይከብዳል። መጀመሪያ ነገር እንደ አገር ለአገሬ መልካም ተመኝቼ ከራሴ አልፎ ለአገሬ የሚሆነውን በጎ ነገር ሁሉ ሊያስደስተኝ ይገባል።ያኔ ነው ሚዛኔ ትክክል የሚሆነው።ያ ነው እይታዬ ከራሴ አልፎ አገሬ ከግል ጥቅምና ፍላጎቴ ባየለ ለወገኔ ማለት የምጀምረው።
እንደ ዜጋ የራስን በጎ አሻራ ማኖር ሲገባ፤ለሌላው አቅዶ በትጋቱ እና በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ አልፎ የሰራውን በጎ ስራ አለማድነቅ ብሎም አለማመስገን ያስኮንናል። ይህ አተያይ በፍፁም ስህተት ላይ ይጥላልም። በጎን ነገር ተመልክቶ የዚያን ተግባር በጎነት ከመጥቀስ ይልቅ በሌላ አሉታዊ መልክ መመልከት ከበጎ እሳቤ የመነጨ አተያይ ሊሆን አይችልም።
ይህን በጎ ነገር የሰራው አካል ክፉ እንኳ ቢሆን ስራው ብቻም ሳይሆን ክፉም ጭምር መመስገን አለበት። በሀገራችን ‹‹አርጩሜም ገድ አለው›› የሚል አባባል አለ። ክፉ የተባለ ሃላፊ ጥሩ ጥሩ ነገሮች ሰርቶ ሲገኝ ይህ የሚባለው። አሁን ክፉ የለም፤ ኖሮ ቢሆን እንኳ ቢያንስ እሱ ያለበት ዘመን ጥሩ መሆኑን መመስከር ያስፈልጋል።
የሀሳባችን ሀያልነት ማሳያው ሌላውን መቃወም መሆኑን የምናምነው እስከ መቼ ነው? የምናቀርበው የተሻለ ሀሳብና ልንተገብር የምናቅደው ሌላ አሸናፊ የሚያደርገንና ተግብረነውም አሁን ካለው ይበልጥ አንፀባራቂ የሆነ ገፅታ መፍጠር እንደምንችል ለማስረዳት ዛሬ ላይ በትጋት ሰርተው በጥረታቸው ያሳኩትን መንቀፍ ሳይሆን አብረናቸው ቆመን ማበርታት ይገባል። በየትኛውም አካል የሚሰራ አገራዊ በጎ ተግባር በየትኛውም ዜጋ በእኩል ስሜት መረዳትና ለዚያ በጎ ተግባር እውቅና መስጠት ይገባል።
ከትላንት የተሻለ ዛሬ ያሳየኝን ሳላደንቅ ነገ ብሩህ አደርግልሀለሁ የሚለኝን መስማት ይከብደኛል። ዛሬን በትክክል አመላክቶኝ ለነገ የተሻለ ተስፋ የሚመግበኝ አተያዩ የተቃና አገሬና ህዝቧ የሚጠቀሙበትን ነጋቸውን ለማሳመር የሚተጋውን ማድነቅ፣ ከተቻለኝም ተሳታፊ ሆኜ በዚያ በጎ ተግባር ውስጥ የራሴን አሻራ ለማሳረፍ መጣር ይኖርብኛል።
ጉዳዮችን የምንለካበት የተሻለ መነፅር ማጥለቅ ይጠበቅብናል። በጎን ስራ ለራሳችን ስውር አላማ በሚሆን መልኩ ማንኳሰስ ዛሬ እንችል ይሆናል። ያ ተግባር ግን መነሻውም በጎነት የሚያተርፈውም መልካም ውጤት ነውና እውነት ይታዘበናል። አገራችን ብሎም ከተማችን ላይ እየተሰሩ ያሉ ትላልቅ በጎ ተግባራት ተግባሪያቸውንም አሳቢያቸውንም የሚያስመሰግን መሆኑን መካድ ይከብዳል።
በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ተጠናቀው የተመረቁ ሂደታቸው ተፋጥኖ ወደ ምርት የተሸጋገሩ ፕሮጀክቶች ዜና መስማታችን ያስደስታል። አንዳንዶች ግን በሰሙት መልካም ዜና አልተደሰቱም ፤የተሰራውን እያጥላሉ የተገነባውን እያንኳሰሱ ሀሳባቸውን በአደባባይ ሲገልጡ ሲታይ ለትዝብት ይዳርጋል። ለመልካም ስራ መልካም ያልሆነ አስተያየት ከየት የተለመደ ባህሪ፣ እንዴት ያደገ ልምድ እንደሆነ መገመት ያስቸግራል።
በመዲናችን አዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችና ከተማዋን የማደስ ሂደት በእርግጥም ያስደንቃል። አዲስ አበባ በመታደስ ላይ ያለች እድሳትዋም ተጀምሮ እየተፋጠነ መሆኑ በዚህም አንዳንድ ገፅታዎቿ ፈክተው ማየታችን እንደ ህዝብ ሊያስደስተን የሚገባ እውነት ነው።
እንደውም አንድ አስተያየት አለኝ፤ ለበጎ ነገር ተቺዎቹ። ንፁህና ውብ ተደርገው በተሰሩ ፓርኮች ፈታ እያላችሁ፣ ጎዳናዎች ላይ እየተንሸራሸራችሁ በጎ ያልሆነውን አስተሳሰባችሁን በበጎና ፅዱ በሆነ አመለካከት ቀይሩ ማለት እፈልጋለሁ። በጎ አለመስራት ባያስጠይቅ የተሰራን በጎ ተግባር አለማድነቅ አይከብድም? አበቃሁ ቸር ይግጠመን።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሰኔ 13/2013