በባለፈው ሳምንት የዚህ አምድ ዳሰሳዬ የመስቀል አደባባይ አራዳ ማዘጋጃ ቤት የእግረኞች መንገድ ግንባታን ማስቃኘት መጀመሬ ይታወሳል። በዚህም ከመስቀል አደባባይ በተለምዶ ኢምግሬሽን እየተባለ የሚጠራው አካባቢ /ጥቁር አንበሳ ትምህርት ቤትም የዋንኛው ጎዳና መጠሪያ ነው/ ድረስ የተካሄደውን የእግረኛ መንገድ ግንባታን አስቃኛችኋለሁ። በዚህም መልካም ገጽታው ይበርታ ብዬ የጎደለውና መስተካከል ይገባዋል ያልኩትንም አመላክታችኋለሁ። ዛሬ ደግሞ ሳምንት ካቆምኩበት ጥቁር አንበሳ ትምህርት ቤት ተነስቼ የአራዶቹ መንደር ፒያሳ ድረስ አስቃኛችኋለሁ።
ከጥቁር አንበሳ ትምህርት ቤት የመንገዱን ቀኝ ይዤ ወደ አዲስ አበባ መስተዳደር በእግሬ ባማረው ጎዳና ሽር ማለቴን ጀምሬያለሁ። በፊት ጠቦ ይጨንቅ የነበረው የቸርችል ጎዳና ግራና ቀኝ የእግረኛ መንገድ ሰፍቶና ተውቦ እባኮዎትን ይራመዱብኝ የሚል ይመስላል። አልፎ አልፎ ለእግረኞች ማረፊያ የሚሆኑ ወንበሮችም ተደርገውለታል። ለመንገዱ ውበት ያጎናጸፉ ዛፎችና አበቦች ተተክለዋል፤ ገና በለጋነት እድሜያቸው አካባቢውን የተለየ ገፅታ አላብሰውታል። ዛፎቹ ደግሞ ለአቅመ ዛፍ ሲደርሱ ከሌላ ቦታ ተነቅለው የመጡ ናቸው። ችግኝ አይደሉም።
እዚህም የእግረኛውን መንገድ ለማሰፋት እንዲቻል ተቋማት አጥራቸውን እፍርሰው ወደ ውስጣቸው ተሰብስበዋል። የጥቁር አንበሳና የሊሴ ገብረ ማሪያም ትምህርት ቤቶች የግንብ አጥሮች ተነስተዋል። የሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት አጥር በጥሩ ሁኔታ እየተገባ ነው። የጥቁር አንበሳው ግን መሬቱ እንዳይናድ ከተካሄደው ግንባታ ውጪ የትምህርት ቤቱ አጥር አልታጠረም። ለልማት የፈረሰ አካባቢ በታጠረበት መልኩ ነው አሁንም ድረስ የታጠረው። አጥሩ በአስቸኳይ መገንባት አለበት። ይህ ሁኔታ በአካባቢው ላይ ውበት ለማፍሰስ የተደረገውን ጥረት ለሰሞንም ቢሆን ማበላሸት የለበትም።
አጥሩ ብቻ አይደለም እይታዬን የረበሸው። የትምህርት ቤቱን የታችኛውን የግንብ አጥር ተጠግተው ዛሬም የጎዳና ተዳዳሪዎቹ የኢትዮጵያ ልጆች መጠለያ ያሉትን ሸራ ይሁን ፕላስቲክ ዘርግተው እየኖሩ ናቸው። የእነዚህ ዜጎች አኗኗር የውቡን መንገድ ውበት አፍዞታል፤ በልማቱ ከሄድነው ርቀት ትንሽም ቢሆን ወደሁዋላ የሚመለስ ችግር ስለመኖሩ የጎዳና ተዳዳሪዎቹ ህይወት ይጠቁማል።
መስተዳደሩ በፊት የጀመራቸውን የጎዳና ተዳዳሪዎችን መልሶ የማቋቋምና ምርታማ የማድረግ ስራ ዛሬ ከምን እንደደረሰ ባለውቅም ከተማዋ ላይ የሚታዩ የጎዳና ተዳዳሪዎች ቁጥር ግን ከበፊቱ እጅግ በርክቶ ይታያል። ይህ ደግሞ እየተሰሩ ያሉትን መልካም ስራዎች በመሸፈን የከተማዋን ገፅታ ለመቀየር በሚደረገው ጥረት ላይ ቀዝቃዛ ውሃ እንዳይቸልስበት ለጎዳና ተዳዳሪዎቹ መፍትሄ ለማስቀመጥ መሰራት ይኖርበታል።
ከእዚህ ውጪ ግን የቸርቸል ውበት በትክክልም በሚገባው መልኩ ተበጅቷል። ከተማ የመስራት አንዱ መገለጫ ነው። ከተሞች ኮንክሪትና መኪና ብቻ መሆን የለባቸውም። ክፍት ቦታዎች ሰፋፊ የመኪናና የእግረኛ መንገዶች ሊኖሯቸው ይገባል። የቸርችል ጎዳና የተሽከርካሪ መንገድ ፊትም ችግር የለበትም፤ አንጋፋ ውብ መንገድ ነው። ችግሩ የእግረኞች መንገድ ነበር፤ እሱም አሁን ተፈታ።
ከሊሴ ገብረ ማርያም ትምህርት ቤት ቀጥሎ ያለው የኢትዮ ቴሌኮም መስሪያ ቤት ያለበት ህንጻ እንዲሁም ከዚያ ትንሽ ከፍ ብሎ ያ ሆቴል አጥርም ለእግረኛ መንገድ ግንባታው በሚል ፈርሰው ይዞታቸው ወደ ህንጻቸው ተጠግቷል።
የህንፃዎቹን ገፅታና አሰራር ከመንገዱ አዲስነት ጋር እየለካሁ ወደ መስተዳድሩ ወይም አራዳ ህንጻ አካባቢ በእግር መጓዜን ቀጥያለሁ። ይህ አካባቢ በተለይ በስተቀኝ ያለው ሙሉ ለሙሉ ፈርሷል። ያለው አንድ ሆቴል ብቻ ነው። በስተግራ በኩል ግን ወደ ውስጥ እንዲገቡ ሲደረግ የሆነ አካላቸው ተቆርጦ ወደ ውስጥ አንዲገቡ የተደረጉ ቤቶች ይታያሉ።
አካባቢው የሬሳ ሳጥን መሸጫ ቤቶች በብዛት ይገኙበታል። ይህ የእግረኛ መንገድ እንዲህ ከመዋቡ በፊት እነዚህ የሬሳ ሳጥን መሸጫ ቤቶች ተርታውን ተሰድረው ይታዩ ነበር። ሁሌም በዚያ መንገድ ሳልፍ ምነው ለእነዚህ የሬሳ ሳጥን መሸጫዎች ሌላ ቦታ ቢፈለግላቸው እል ነበር፤ እዚህ ትልቅ ጎዳና ዳር ተደርድረው በሰው ተስፋ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ የሚቸልሱ አርጌ አያቸው ነበር። ስትሞቱና ሲሞቱባችሁ እነዚህን በመሳሰሉ ሳጥኖች ተሸሞንሞኑ፣ ሙቶቻችሁን አሽሞንሙኑ የሚሉ ነበር የሚመስለኝ። ምን ሆነሃል ሞትና ህይወት እኮ አይነጣጠሉም የሚሉ አይጠፉም። ቢሆንም በመልክ በመልኩ ማየት ይገባል እላለሁ።
በዚህ ውብ ሆኖ በተሰራው ጎዳና ዳር ላይ የተወሰኑት ባይኖሩም፣ ከመንገዱ በስተቀኝ በኩል ያሉት ዛሬም ሳጥኖቹን ደርድረው ይታያሉ። “መሬት መከተት አለ፤ የምር ሽር ብትን ማለት ነው እረፍ” የሚሉ ይመስላሉ። እንደው ህግ ነገር ወጥቶ ሰወር ሌላ ቦታ ቢፈለግላቸውና በዚህ ብዙ ተስፋ በሚያስንቅ ውብ ጎዳና ላይ ባይታዩ መልካም ነው።
ሆስፒታሎችና ሌሎች የጤና ተቋሞች እንዲሁም የቀብር ክልሎች ባሉበት አካባቢ ላይ ቦታ ቢፈልግላቸው ጥሩ ይመስለኛል። ሀሳብ ነው የሰጠሁት። ቦታውም ቢሆን ለሉላ ትልቅ ኢንቨስትመንት ሊውል የሚችል ነው።
ከዚህ አካባቢ አይኔን ነቅዬ ወደ ውበቱ ተመልሻለሁ። ከፍ ብዬ አደባባዩ መሀል ላይ በፊት በግሳንግስ ተሸፍኖ ብዙም የማይስብ የነበረው ታሪካዊው የአፄ ቴዎድሮስ የመቅደላ ታሪክ መታሰቢያ ሴፓስቶፖል ሀውልት ለአካባቢው ልዩ ግርማ አላብሶታል። በዚህ በልዩ ሁኔታ በተዋበው ጎዳና ላይ የዚህ ሀውልት መኖር ልዩነት ይፈጥራል። በዚያ መንገድ ሲመላለስ ያንን ያየ ምንነቱን ይጠይቃል፤ የሚያውቅም የኢትዮጵያዊያንን ታሪክ ያሳውቅበታል።
ሴፓስቶፖልን አልፎ የሚገኘው ዋናው መንገድ እንደ ታችኛው ሁሉ በግራና በቀኝ ተከፍሎ ለእግረኞችና ለመንገደኞች ምቹና ማራኪ ሆኖ ተሰናድቷል። መኪኖች ሽው እግረኞች ደግሞ ሽር ይሉበታል። አካባቢው ላይ በመንገዱ ግራና ቀኝ ታንፀው ለቦታው ድምቀትን ያላበሱት አዳዲስ ህንፃዎች የየራሳቸው መልክና ዲዛይን ያላቸው መሆኑን የተመለከተ በውበታቸው መገረሙ አይቀርም።
እነዚህ ህንጻዎች ከመገንባታቸው በፊት ይህ አካባቢ ከመንገዱ በስተቀር የሚከብድ ነበር። የተረሳም ይመስል ነበር ማለት ይቻላል። ገና ፒያሳን ሲለቁ ቁልቁል ያለው ቦታ እስከ ቴዎድሮስ አደባባይ ድረስ ያለው ስፍራ ፍዝ ነበር፤ ህንጻዎቹ አካባቢው የከተማ እንቅስቃሴ የሚታይበት እንዲሆን አርገውታል። የእግረኛው መንገድ መጨመር ደግሞ ይበልጥ ውብ አርጎታል።
ዋናው መንገድ ጨርሼ ፊት ለፊት ድሮ ቸርችል ቪው መዝናኛ የነበረው ቦታ ደርሻለሁ። ቸርችል ቪው የነበረበት ስፍራ ባማረ ዲዛይን የአንፊ ቲያትር መቀመጫዎችን የመሳሰሉ ደረጃዎችና መቀመጫዎች ውብ በሆነ መልኩ ተሰርተውበታል። የአዲስ አበባ ከተማም ስም በጉልህ ተቀርጾ ተተክሎበታል። ይህም ከርቀት ሲታይ ለአካባቢው ልዩ ውበት አልብሶታል።
የመስቀል አደባባይ ፒያሳ የእግረኞች መንገድንና ሌሎች ልማቶችን ታላቅ ስራ የሰራው የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር እንደጀመርከው ሌሎች የከተማዋን ገፅታዎች ይበልጥ ለማስዋብም መስራት ይኖርበታል። የአዲስ አበባ መስተዳድር አያያዝህ መልካም እና የሚደነቅ ነው፤ ጠንክር እላለሁ። አበቃሁ፤ ቸር ይግጠመን።
ተገኝ ብሩ
አዲስ ዘመን ሰኔ 12/2013