ሀገራዊ ለውጡ በመጣበት ወቅት ልክ የዛሬ ሦስት ዓመት አካባቢ ሀገራችን ምን ያህል በፓለቲካ ፓርቲዎች እንደተጥለቀለች የምናስታውስ እናስታውሳለን።ያ ወቅት ሀገራችን የብሄሮች፣ ብሄረሰቦች ብዝሃነት መገለጫ ብቻ እንዳይደለች የታየበትም ነበር።የአመለካከት ብዝሃነት የተንፀባረቀባት ሀገር መሆን የጀመረችበት ወቅት ነበርና።ያ ሁሉ አመለካከት ተቻችሎ ማደሩ በርግጥም የሚያስደንቅ ነው፡፡
በውጭ ሀገር በስደት ላይ የሚገኙ ፓርቲዎች፣ አኩርፈው ጫካ የገቡ ፓርቲዎች ሁሉ መንግሥታዊ አቀባበል እየተደረገላቸው ሀገር ቤት የገቡበት፣ በእስሥር ላይ የነበሩ የፓለቲካ ፓርቲ አመራሮች እየተፈቱ ፓርቲዎቻቸውን ከእሥር የፈቱበት ወቅት ነበር።በሀገር ውስጥ ያሉት ፓርቲዎችም ይበልጥ የሚንቀሳቀሱበት ወቅት እንደመጣ በማሰብ በነጻነት መንቀሳቀስ የገቡበት ወቅትም ነበር፡፡
መንግሥት የፓለቲካ ምህዳሩ መስፋቱን ይፋ በማድረግ በሀገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት ሁሉም ርብርብ እንዲያደርግ በማሰብ ሁሉም ፓርቲዎች በነጻነት የመንግሥትን ህግ አክብረው በሀገሪቱ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አሻራቸውን እንዲያኖሩ የተቻለውን ሁሉ አድርጓል።የምርጫ ቦርድ በአዲስ ተዋቅሯል፤ የፓለቲካ ፓርቲዎችን አላሰራ ብሎ የነበረው የምርጫ ህግ እንዲሻሻል ተደርጓል። ፍርድ ቤቶች ነጻነታቸውን በሚጠብቅ መልኩ መስራት የሚያስችላቸው አደረጃጀት ተፈጥሯል።ሌሎች ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ አስፈላጊ የሆነ መደላድሎች ተፈጥረዋል፡፡
እነዚህ ላይ ተቁሞም ነው የዘንድሮው ምርጫ እየተካሄደ ያለው።በዚህ ምርጫ 47 የፓለቲካ ፓርቲዎች ተመዝግበው እየተዘጋጁ ናቸው።120 የግል ተወዳዳሪዎችም በምርጫው ይሳተፋሉ።እነዚህ ሁሉ የምርጫውን ዴሞክራሲያዊነት መገለጫ አድርጎ መውሰድ ይቻላል።
የፓለቲካ ፓርቲዎች ዝግጅታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል።አንጋፋ የፓለቲካ ፓርቲዎች ባለፉት ዓመታት የነበረባቸውን ክፍተት በመሙላት ለምርጫው ራሳቸውን አዘጋጅተው፣ የሚቀናጁት ተቀናጅተው ነው ወደ ምርጫው ሂደት የገቡት።በራሳችን ቆመን ምርጫውን እናሸንፋለን ያሉትም በራሳቸው መንገድ መጓዛቸውን ቀጥለዋል።አዳዲስ ፓርቲዎችንም ይህ ምርጫ አሣይቶናል።
የምርጫው ሂደት የሚራገፈውን እያራገፈ በምርጫው ዋዜማ ላይ ደርሷል።ልክ እንደ ባቡሩ።ባቡሩ ጉዞውን ቀጥሏል።የሚሳፈረው ተሳፍሯል፤ በየጣቢያው የሚወርደው እየወረደ ሌሎች ተሳፋሪዎችንም እያሣፈረ ጉዞውን ቀጥሎ አሁን ወደ ዋናው መዳረሻው እየተጠጋ ነው።
ለይስሙላ ውርውር ሲሉ የኖሩ ፓርቲዎች አሁን አይታዩም።ለነገሩ አንዳንዶቹ ያኔም እንዲያጅቡ የተፈጠሩ ነበሩ።በፓርቲዎች ምዝገባ ወቅት ሲያጭበረብር ተደርሶበት ከፓርቲነት የወጣ ፓርቲም እንዳለ ይታወቃል።ይህም ምርጫው በትክክለኛ ጎዳና ላይ መሆኑን ያመለክታል፡፡
አንዳንድ ፓርቲዎች ግን ይህን ታሪካዊ አጋጣሚ በራሳቸው ችግር አጥተውታል።እነሱ በምርጫው ተሳትፈው ቢሆን ኖሮ ምርጫው ምን ያህል ውብ ሊሆን ይችል እንደነበር አሁን ካለው ሁኔታ መረዳት ይቻላል፡፡
ሀገርን ለመምራት ሀሳቡ ያለው ፓርቲ በዚህ ወሳኝ የፓለቲካ ወቅት ውሃ የማያነሳ ምክንያት በማቅረብ ከምርጫ መውጣት አልነበረበትም።ግን ይህ ሆኗል።ፓርቲዎቹ ግራ ቀኝ ማየት ተስኗቸው የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታውን ጉዳይ ወደ ጎን ትተውታል።ለምርጫው መዘጋጀት ሲገባቸው በውስጥ ጉዳይ ሲርመጠመጡ ወርቅ ጊዜያቸውንና ዕድላቸውን ያመከኑም አሉ፡፡
በምርጫው ለመሳተፍ ተመዝግቦ የሚጎለውን መጠየቅ ሲችል በእሥር ላይ የሚገኙ አባሎቼ ካልተፈቱ በምርጫው አልሣተፍም ያለ ፓርቲ ታይቷል።ፓርቲው ይህን በማድረጉ ራሱንም፣ ደጋፊውንም፣ አባሎቹንም ጎድቷል።ይህን በማድረጉ በአባላቱ መጠየቅ የሚኖርበትም አለ።
አንጋፋ የሚባሉ የፓለቲካ ፓርቲዎች በተልካሻ ምክንያት ራሳቸውን ከምርጫ ማግለላቸው ሀገርንም አይጠቅምም፤ ለዚያውም የዴሞክራሲ ሥርዓት ገና በሚዘራባት ሀገር።ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ሆኖ የሚቃናውን ማቃናት በሚቻልበት በዚህ ወቅት ምርጫውን ከዳር ሆኖ መመልከት ውስጥ መግባት የጤነኛነትም አይመስልም።ከፓለቲካ ፓርቲ የሚያስቆጥርም አይመስለኝም።ከምርጫው ራሳቸውን ያገለሉት ደግሞ አንጋፋ ፓርቲዎች ሲሆኑ ይበልጥ ያሳዝናል፤ በጣምም ተሳስተዋል።
ሀገር ከምርጫ የሚበልጥ አጀንዳ የለኝም ባለችበት በዚህ ወቅት በፓርቲ የውስጥ ጉዳይ መቆራቆስ ማብዛት አንጋፋነትንም ጥያቄ ውስጥ ያስገባል።ዕድሜ ብቻ ያሰኛል።እርስ በርስ እየተፋጩ ዋናውን የፓርቲው ጉዳይ አለማስታወስ ከታላቁ የምርጫ ገበታ እንዳይቋደሱ አድርጓል።
በዚህ ወቅት የሚቀድመው ሀገራዊ ጉዳይ ነው – ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ።በምርጫው እንዴት ሆነን ብንዘጋጅ ለዘመናት ህዝባችንን ማገልገል የሚያስችለንን ሥልጣን እንዴት በምርጫ ማሳካት እንችላለን የሚለው መቅደም ነበረበት።እነሱ ግን ይህ ሊሆን የሚችልበትን የዘንድሮውን ወርቃማ ዕድል አመከኑት።
ብርቱዎች መታየታቸውንም መጥቀስ ይገባል። አባሎቻቸው ታስረው እነሱ ካልተፈቱ በምርጫው አንወዳደርም ያላሉ ፓርቲዎች እዚህ ላይ ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አንድ ጡብ እንዳስቀመጡ ይቆጠራል።በፍርድ ቤት እየተከራከሩ ምርጫ ቦርድን ያሸነፉ ፓርቲዎችም ተመልክተናል።ይህ ነው ትክክለኛው መንገድ።መብትን ማስከበር።
በዚህች ሀገር የመብት ጥሰቶችን ህገወጥ ተግባሮችን በህግ መጠየቅ የሚቻልበት መንገድ መፍጠሩ እየታወቀ በሀይል ሥልጣን ሲሞከርም ነበር።ይኼ ጊዜው እንዳለፈበት መንግሥት በተደጋጋሚ አስታውቋል።ችግር ካለ ቅሬታ ካለ ለሚመለከተው አካል ማቅረብ ይቻላል።ዛሬ ሠሚ አለ።ሠሚ መኖሩን ፍርድ ቤት የሄዱ ፓርቲዎች አሣይተውናል።እንደ ቀደመው ዘመን የሚያስቡ ካሉ ተሳስተዋል፤ ፍርድ ቤቶችና ምርጫ ቦርድ የሁሉም ናቸው።
ሽንጥን ገትሮ ለመከራከር መዘጋጀትም ይገባል።የፓለቲካ ፓርቲ ሆኖ መከራከር አለመቻል ትንሽነት ነው።በቀጣይም የመብት የህግ ጥሰቶች ሲኖሩ መንገዱ ምርጫ ቦርድንና በየደረጃው ያሉ ፍርድ ቤቶችን በር ማንኳኳት ነው፡፡
ምርጫው የሣምንት ዕድሜ ነው የቀረው።ምርጫው የዴሞክራሲ ሥርዓት የናፈቀቸው በሚገባ ሊጠቀሙበት እየሰሩበት ነው።ሜዳውም ፈረሱም ይኸው ሲባሉ አንወዳድርም የሚሉት ደግሞ ዳር ቆመው እየተመለከቱ አንዳንዶቹም ለጥፋት እያኮበኮቡ ይገኛሉ።
በምርጫው የማትሳተፉ ፓርቲዎችም ሆናችሁ ሌሎች አካላትም ራቅ አድርጋችሁ አስቡ።ምርጫው የታሰበለትን ዓላማ እንዲያሳካ መስራት ይኖርባችኋል።ምርጫ ወቅትን እየጠበቀ ይመጣል።በዚህ ምርጫ አሻራችሁን በጉልህ ብታሳርፉ መልካም ነበር።ያ ካልሆነ ደግሞ ሂደቱን በጽሞና ተከታተሉ።ለቀጣዩ ምርጫ ዝግጅት የማድረጊያ ጊዜ አድርጋችሁ የምርጫውን ሂደት ተጠቀሙበት።ከዚህ አኳያ ብዙም ሚናችሁ እየታየ አይደለምና ሚናችሁን ተወጡ፡፡
እዚህ ላይ አንድ ጉዳዩ በፍትህ ሂደት ላይ የነበረ ፓርቲ አመራር ያሉትን መጥቀስ እፈልጋለሁ።እኚህ አመራር ፓርቲያቸው በተለያዩ ችግሮች ሣቢያ በምርጫው ለመወዳደር አልተመዘገበም።ለመመዝገብ ዝግጁ ነኝ ባለበት ወቅት ደግሞ ምዝገባው አብቅቷል።እኚህ አመራር ቦርዱ ጉዳዩን መልሶ ማየት የሚችል ከሆነ ግን ፓርቲው በምርጫው ለመሣተፍ እንደሚፈልግ ገልፀው፣ ከሌለ ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው አስተዋጽኦ ማድረጋችንን ግን በሌሎች መንገዶች እንቀጥላለን ማለታቸውን አስታውሳለሁ።ይኼ ነው ለዚህች ሀገር የሚጠቅመው።ሌሎችም ከዚህ ቢማሩ ነው መልካም ሊሆን የሚችለው።ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አስተዋጽኦ ማድረግ በዚህም ይገለጻል።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሰኔ 6/2013