የእለቱ ጉዞዬ የፈለገው ነገር ቢመጣ የሚሰረዝ አይደለም። ገና ከቤት ስወጣ የጸሀዩ ማቃጠል ተቀበለኝ። ሰማዩ ለምድር የቀረበ እስኪመስል ድረስ የረፋዱ ጸሀይ ከቀትሩ ይፎካከራል፤ ይፋጃል፤ ጃኬቱን አውልቄ ትከሻዬ ላይ ጣል አድርጌያለሁ።
ወደ አሰብኩበት ቦታ ለማቅናት ለትራንስፖርት ጥበቃ ተሰልፍኩ። ጸሀዩ መፋጀቱን ቀጥሏል፤ በዚህ ላይ ሰልፍ አለ፤ ሁሉም ያማሉ። ለማይቀርበት ጉዳይ ነው የወጣሁት። ከግማሽ ሰዓት ጥበቃ በኋላ ሸገር አውቶቡስ መጣ።
ሶስት ብር እየከፈልን ወደ አውቶቡሱ ዘለቅን ጉዞ ወደ ስድስት ኪሎ ሆነ። ከብዙ አመታት በኋላ ነው ወደ ስድስት ኪሎ የምሄደው። ስድስት ኪሎ መቼም ቢሆን ከህሊናዬ አይወጣም። ያን አካባቢ የሚያውቅ በሙሉ ከእኔ የተለየ አመለካከት አይኖረውም። ሌሎች የራሳቸው ሌላ ምክንያት ሊኖራቸው ይችላል። ህጻናት በአንበሳ ግቢ ያስታውሱታል።
እንደ እኔ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ግቢ የተማረ ደግሞ ትዝታው ልዩ ነው። ይህን በህሊናዬ እያመላለስኩ ነው የእለቱን መርሀ ግብሬን ለመፈጸም ወደ ስድስት ኪሎ መጓዝ የጀመርኩት።
እንዳልኳችሁ ከብዙ አውቶቡስ ጥበቃ በኋላ ነው ሸገር የተገኘችው። ድካም አለ። ጸሀይ መቶኛል። ከፊት ተሰልፌ ስለነበር በፈቀድኩት ወንበር ላይ ተቀመጥኩ። የሸገር ወንበር የኋላው ነው ደስ የሚለው። እንደሌላ አውቶቡስ መንገጫገጭ የለም፤ ከተማ እና ተሳፋሪውን እንደልብ እየቃኙ መሄድ ያስችላል። ሸገርን ስሳፈር ሁሌም በጉብኝት ላይ ያለሁ ያህል ይሰማኛል።
ለነገሩ ዛሬ ጎብኚ ነኝ። አውቶቡሱ በአራዳ ጊዮርጊስ አርጎ ወደ አፍንጮ በር አቀና። ደጃች ውቤ ሰፈር በተለይ በስተቀኝ ያለው ለመልሶ ልማት ከተነሳ የቆየ ቢሆንም አሁንም አልፎ አልፎ ከሚታዩት ጥቂት አዳዲስ ህንጻዎች ውጪ አሁንም እንደፈረሰ ነው። አፍንጮ በር አካባቢ ትልቅ መስኪድ አየሁ። አደባባዩ ላይ። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ አፍንጮ በር አካባቢ ያለው የግቢው አካል ትልቅ ህንጻ ተሰርቶበታል። ወደ ስድስት ኪሎ የሚወስደው መንገድ በሰፊው ተገንብቷል።
አሁን ስድስት ኪሎ ደረስን ከፊት ለፊት የየካቲት 12 ሰማእታት ሀውልት ከእነ ግርማ ሞገሱ ቆሟል። ፋሽስት ጣልያን በ1928 የካቲት 12 ቀን የፋሽስት አገዛዝን አሻፈረኝ ባሉ ጀግኖች ኢትዮጵያውያን በወቅቱ የጣሊያን ጦር መሪ ግራዚያኒ ላይ ቦምቦች መወርወራቸውን ተከትሎ በአዲስ አበባ ነዋሪዎች ላይ በበቀል በመነሳሳት የተፈጸመውን ጭፍጨፋ ለማሰብ የቆመ ሀውልት ነው። 30 ሺ ኢትዮጵያውያን በወቅቱ በአሰቃቂ ሁኔታ መጨፍጨፋቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።
የካቲት 12 ሆስፒታል አጠገብ አውቶቡስ ቆመና ወረድኩ። ለሆስፒታሉ አዲስ ግዙፍ ህንጻ ተሰርቶለታል፤ ያምራል። የህብረተሰቡን የጤና ተቋማት ተደራሽነት ችግር በወሳኝ መልኩ ለመፍታት እንደሚረዳ ታሰበኝ።
ወደ ዩኒቨርሲቲው አቅጣጫ ለማቋረጥ መንገድ ክፍት እስኪሆን እዛው የወርድኩበት ቦታ ቆሜያለሁ። በአካባቢው ጨርቅ ዘርግቶ የተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን ደርድሮ የሚሸጥ ሰው እንዳለ ገባኝ። “በቻርጅ የሚሰሩ አምፖሎችን በቅናሽ” ይላል ነጋዴው። ሰውዬው ግን በሰዎች ተከቧል። ሁሉም አምፖሉ ላይ ነው የሚረባረቡት። በገንዘብ ሳይሆን በነጻ የሚታደል ይመስላል።
ከዚህ ትእይነት / የሰው ትርምስ ያው ትእይነት በሉት/ ራቅ ብዬ ወደ ዩኒቨርሲቲው ግቢ አሻግሬ ተመለከትኩ። የማላውቀው አዲስ ግዙፍ ህንጻ ታየኝ። ወደ አጥሩ ተጠግቶ የተገነባ ስለሆነ ቀድሞ በአጥር ወደ ውስጥ አሻግሮ ለተመለከተ ይታይ የነበረው አረንጓዴ ስፍራ አይታይም።
ግራቀኝ ተሽከርካሪ መቅረብ አለመቅረቡን አየሁና ወደ ዩኒቨርሲቲ አቋረጥኩ። ጉዜዬን ወደ ዋናው በር አካባቢ አደረግሁ። በዚህ በኩልም እንዲሁ ሌላ ግዙፍ ህንጻ ተገንብቷል። ዱሮ በአረንጓዴ ስፍራ ውስጥ አሻግረን የምንመለከተው የአርትስ ቢልዲንግ አብዛኛው ክፍል በአዲሱ ግዙፍ ህንጻ ተሸፍኗል። ወደ አካባቢው ሳልመጣ ብዙ ጊዜ እንደሆነኝ ህንጻዎቹም በሚገባ አስረዱኝ።
አሁን ዋናው በር ደርሻለሁ። ከዚያ ከሚያምረውና ባለ ግርማ ሞገስ መግቢያ በር። በግቢው የመጻህፍት ኤግዚቢሽን መኖሩን የሚያመለክት መረጃ ተመለከትኩ። በርካታ ሰዎችም ይህን ኤግዚቢሽን ለመመልከት መምጣታቸውን ለጥበቃዎች እየገለጹ ወደ ውስጥ ሲገቡ አየሁና እኔም ተቀላቀልኳቸው። እለቱን ለዚህ አላማ ለማዋል አስቤ ነው በዩኒቨርሲቲው የተገኘሁት።
ይህ የቀድሞ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ አባት የራስ መኮንን መኖሪያ የነበረውና ኋላ ላይ ንጉሱ ለዩኒቨርሲቲ እንዲውል ያደረጉት ግቢ ሲበዛ ውብ ግቢ ነው። አሁን ደግሞ እኔ በማውቀው ውበቱ ላይ ሌሎች ውበቶችን ተጎናጽፏል።
ከውጪ ሆኜ የተመለከትኳቸው አዳዲስ ህንጻዎች እንዳሉ ሆነው ሌሎች ለእኔ አዳዲስ የሆኑ ህንጻዎችም ይታያሉ። የእግረኛ መንገዱ፣ አረንጓዴ ስፍራው ቀድሞ ከነበሩት በተጨማሪ አዲስ የተተከሉት እጽዋት ለግቢው ተጨማሪ ውበት አጎናጽፈውታል።
በእለቱ ወደ ዩኒቨርሲቲው የወሰደኝ ጉዳይ በግቢው የሚካሄደው የመጽሐፍ አውደ ርዕይ መሆኑን ገልጬያለሁ። ዩኒቨርሲቲው ታላላቅ የመጽሀፍት ኤግዚቢሽኖች እንደሚያዘጋጅ መረጃው ነበረኝና ነው በስፍራው የተገኘሁት። ይህን ኤግዚቢሽን በሚገባ ለመጎብኘት የሚጠቅሙኝን መጻህፍትም ለመግዛት ተዘጋጅቻለሁ።
አውደ ርዕዩ ወደሚካሄድባቸው የፕላስቲክ ዳሶች ወደ ተጣሉት እና በመደብ በመደብ ወደተደረደሩት ስፍራዎች አመራሁ። በርካታ አስደማሚ ነገሮች ታዩኝ። የዩኒቨርሲቲ አዳራሾችና ግቢው ሙሉ በሙሉ አገልግሎታቸውን ለኤግዚቢሽኑ አውለዋል፤ በመጽሐፍት ሻጮች እና አሳታሚዎች ተሞልተዋል። ሁሉም መጻህፍት የሚያስተዋውቀው ያስተዋውቃል፤የሚሸጠው ይሸጣል። በጣም በርካታ ሰዎችም ለግብይት በግቢው ተገኝተዋል።
ኤግዚቢሽኑን በሚገባ ለተመለከተ የመጻህፍት ዘር በሙሉ በስፍራው ያለ ሊመስለው ይችላል። አይገኝም ያሉት መጽሃፍ በዚያ ይገኛል፤ እግራችሁ እስኪነቃ ፈልጋችሁ ያጣችሁትን መጽሐፍ ታገኛላችሁ። ውድ ነው ያላችሁት መጽሃፍ ባልተጠበቀ ዝቅተኛ ዋጋ ይገኛል። እንዴ በዘንድሮ የመጽሀፍ ዋጋ ውድነት ማመን በሚቸግር ገንዘብ መጽሀፍ ሊገዙ የሚችሉበት ስፍራ ነው።
ብቻ ምን አለፋችሁ እኛ የምናውቀው የምግብ ቡፌ ነው። አውደ ርእዩ ላይ ግን የመጽሃፍት ቡፌ ነው የታየው። በአውደ ርእዩ ላይ የተመከትኩት ህብረተሰብ ብዙ ቢሆንም ፣ በአውደ ርእዩ ከቀረበው ዝግጅት አንጻር አንሶብኛል። ወደ ግቢው ስገባ እንዳየሁት አምፑል በሚሻማው ህብረተሰብ ልክ ጎብኚም ይሁን ገዥ በአውደ ርዕዩ ባለማየቴ ቅሬታ ተሰማኝ። ምናልባት በስፍራው የተገኘሁት መዝጊያው አካባቢ ስለሆነ ሊሆን ይችላል። እንዲያም ቢሆን ግን ይህን ቡፌ ለመቋደስ ብዙ ሰው መገኘት ነበረበት። እኔ ግን የተወሰኑ መጻህፍት ገዛሁ። እጅ አጥሮኝ እንጂ ብዙ እገዛ ነበር።
ይሄውላችሁ ወዳጆቼ ከሰውነት አካላችሁ ውስጥ አንዱ እጃችሁ ቢቆረጥ ሌላኛው አለ፤ አንዱ አይናችሁ ቢጠፋ ሌላኛው አለ፤ አንዱ እግራችሁ ቢቆረጥም እንደዚያው። የአካል ጉዳት እንኳን ደርሶባችሁም ይሁን በተፈጥሮ አካል ጉዳተኛ ብትሆኑ አሳምራችሁ መኖር ትችላላችሁ ፤ የአካላችሁ አዛዥ አንዱ አዕምሮ ጤና ካጣ መላ አካላችሁ ጤና ያጣል። እንደ ሌላው የሰውነት ክፍል ተተኪ የለውም። ታዲያ ይህ ተተኪ የሌለው አዕምሮ ተገቢው እንክብካቤ እና የተመጣጠነ ምግብ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ማንበብንም ይፈልጋል። የዩኒቨርሲቲው የመጽሐፍ ቡፌ የሚከፈለው ዋጋ እየተከፈለ በአመት ሳይሆን በመንፈቅ ቢዘጋጅ መልካም ነው። ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎችም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተሞክሮ ቅሰሙ።
አብርሃም ተወልደ
አዲስ ዘመን ግንቦት 21/2013