በዓለም አቀፍ ደረጃ ሦስት ዓይነት የምርጫ ሥርዓቶች አሉ። እነርሱም የአብላጫ ድምፅ (Majority system)፣ ሚዛናዊ የውክልና ሥሌት (Proportional Representation System) እና ድብልቅ ሥርዓት (Mixed system) ናቸው። በኢትዮጵያ ሕገመንግሥት አንቀጽ 56 ላይ በተደነገገው መሠረት በተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ ድምጽ (መቀመጫ) ያገኘ የፖለቲካ ድርጅት ወይም ጣምራ ድርጅቶች የፌዴራሉን መንግሥት የሕግ አስፈፃሚ ይመራል ወይም ያደራጃል።
እኛ ግን አስቀድሞ በሚሰራ እንዲሁም በማንአለብኝነት በሚሰራ የምርጫ ድራማ ውስጥ የቆየን በመሆናችን እነዚህን ሀሳቦች ከወረቀት በዘለለ አናውቃቸውም። አብላጫ ድምጽ ሲሉን የነበረውንም ቢሆን የይስሙላ መሆኑን ነው የምናውቀው። በአቶ ሀይለማርያም ዳሣለኝ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ዘመን የፓለቲካ ምህዳር ለማስፋት ይረዳል የተባለ ስራ እንደነበር አስታውሳለሁ። በዚያ ወቅት አብላጫ፣ ቅይጥ የሚባሉ የምርጫ ዓይነቶች የውይይት አጀንዳ ሆነው ነበር። በኢህአዴግ ዘመን ምርጫዎች ተካሂደዋል ከተባለ አምስት ጊዜ ምርጫዎች ተካሂደዋል። የዘንድሮውን ምርጫ ስድስተኛው ምርጫ እያልን እንደመሆኑ በቃ አምስት ጊዜ ተካሂደዋል።
ከምርጫዎቹ መካከል የብዙዎችን ቀልብ የሳበውና ኋላ ላይ የመራጩንም የተመራጩን ልብ የሰበረው በ1997 የተካሄደው ምርጫ ነበር። በወቅቱ ቅንጅት የተባለ ፓርቲ የተወሰኑ አካባቢዎችን አሸንፎ ነበር፤ አባላቱ ምርጫው ስለተጭበረበረ ፓርላማ አንገባም አሉ፤ በዚህ ላይ አባሎቹም ተከፋፈሉ። አውራው ፓርቲም አጋጣሚውን ተጠቀመበት። በአንዳንድ አካባቢዎችም ግጭት ተከሰተና ከቅንጅት የተወሰኑት ወደ ፓርላማ ይገባሉ ሲባል ማረሚያ ቤት ገቡ።የዴሞክራሲ ጭላንጭል ተዳፈነ። ከዚያ በኋላ የተካሄዱት ምርጫዎች በሙሉ የኢህአዴግ ቀልዶች ነበሩ።
አሁን የምርጫ ጠረን እያወደ ይመስለኛል። ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ዜጎች ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን የሚጠቀሙበት እንደሚሆን የለውጡ መንግስት በተደጋጋሚ አስታውቋል፤ ቁርጠኝነቱን ምርጫ ቦርድን በአዲስ በማዋቀር፣ የምርጫ ህጉን በማሻሻል የፓለቲካ ምህዳሩን በማስፋት አረጋግጧል። እየተካሄዱ የሚገኙ እንቅስቃሴዎችም የዚሁ ውጤቶች ናቸው። ይህን መልካም አጋጣሚ መጠቀም ያስፈልጋል።
በዚህ ምርጫ 47 የፖለቲካ ፓርቲዎች ይወዳደራሉ፤ 8 ሺ209 እጩዎች ተመዝግበዋል። ከእጩዎቹ መካከልም 125ቱ በግል የሚወዳደሩ ናቸው። ይህ ሰፊ የምርጫ ተሳትፎ ለሀገራችን አዲስ ነው። የተፈጠረው ምቹ የፓለቲካ ምህዳር መገለጫ ተደርጎም ሊወሰድ ይገባል።እስከ ቅርብ ቀን ድረስም 36 ሚሊየን 245 ሺህ 444 መራጮች በምርጫው ድምጻቸውን ለመስጠት መመዝገባቸው በቅርቡ የወጣ መረጃ ያመለክታል። የፓሊቲካ ፓርቲዎች ቅስቀሳና ክርክር ማድረጋቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል።
ምርጫ ቦርድ ራሱን እየገመገመ ሂደቱን የተቃና ለማድረግ እየሰራ ነው። በአንዳንድ የፀጥታና የመሳሰሉት ችግሮች ሳቢያ ከተራዘሙ መርሀ ግብሮች በቀር ሁሉም እንቅስቃሴዎች የምርጫው ሂደት በታሰበው ልክ እየሄደ መሆኑን ያመለክታሉ። በምርጫው ለመሳተፍ እየተዘጋጁ የሚገኙ የፓለቲካ ፓርቲዎችና መራጮችም ራሳቸውን ሊመለከቱ ይገባቸዋል የሚያሰኙ ሁኔታዎች እንዳሉ መጠቆም እፈልጋለሁ። ራሳቸውን ተመልክተው አዲስ አቅጣጫ አዘጋጅተው ህዝቡን ለድምጽ አሰጣጡ ማዘጋጀት አለባቸው።
ለሁሉም ፓርቲዎች የሚዲያ ሰዓትና የጋዜጣ አምዶች በፍትሐዊነት የተከፋፈለ መሆኑ ይታወቃል። ይህን ውድ ሀብት በሚገባ የሚጠቀሙ ፓርቲዎች የመኖራቸውን ያህል በሚገባ የማይጠቀሙ ለይስሙላ ብቻ የሚጠቀሙም ስለመኖራቸው መገናኛ ብዙሃኑ ከሚሰጡት መረጃ እንዲሁም ከየአየር ሰዓቶቹ እና አምዶች ባዶ ሆኖ መገኘት እንገነዘባለን።
ፓርቲዎቹ ምቹ ሁኔታውን በቅጡ ለመጠቀምና ዓላማቸውን ለማስተዋወቅ ለህዝቡም ግንዛቤ ለመስጠት ዘገምተኝነት እና ቸልተኝነት እየተያባቸው ነው። የአየር ሰዓትና የጋዜጣ አምድ ሳይጠቀሙ በየጎዳናውና አደባባዩ በመንቀሳቀስና የቅስቀሳ ጽሁፎችን በማሰራጨት ብቻ ህዝቡን እናገኘዋለን ብለው አስበው ከሆነ ስህተት ነው። ይህን በቀሪው ጊዜ በማረም ህዝቡ የሚመርጠውን የሚያውቅበትን እድል ማስፋት ይኖርባቸዋል።
ህዝቡን በተለያዩ አማራጮች ማግኘት መቻል አለባቸው። ህዝቡ ባተሌ ነው። አመራጮችን እያሰፉ ሊያገኙት ካልቻሉ ያጡታል። በምርጫው ለማሸነፍ ከፈለጉ ማድረግ ያለባቸው ይኼንን ነው።
ለጋዜጣ ቅርበቱ አለኝ፤ በጋዜጣ የተሰጣቸውን ከግማሽ በላይ በሚያሰኝ መልኩ ፓርቲዎች እየተጠቀሙበት አይደለም። ጋዜጣው ሥማቸውን ብቻ ይዞ ሲወጣ ሳይ የእነሱም ባዶነት ይታያኛል። ትዝብት ላይ ይጥላቸዋል፤ አሁንም ቀሪውን ጊዜ ሊጠቀሙበት ይገባል።
በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች የምርጫ ቅስቀሳዎች ሲካሄዱ አይቻለሁ። የምርጫ ቅስቀሳው በብዛት በዋና ዋና አደባባዮች እና ጎዳናዎች ላይ ነው እየተካሄደ ያለው። በመኪኖች ላይ የፓርቲ የምርጫ አርማ ተለጥፎ፤ ወጣቶች ሰንደቅ ዓላማ ይዘው ሲቀሰቅሱ ይታያል፤ ከፍ…ከፍ ባሉ መኪኖች ላይ ወጣቶች ተጭነው በድምጽ ማጉያ የፓርቲያቸውን ዓርማ እና ዓላማ እያስተዋወቁ የቤት መኪናዎች ጡሩንባቸውን እየነፉ ያልፋሉ።
መኪኖቹ በአብዛኛው በፍጥነት የሚያልፉ በመሆናቸው ምን ያህል መልዕክት ያስተላልፋሉ የሚለው ግን ያጠያይቃል። የመኪና ላይ ቅስቀሳው የመኪና እሽቅድድም ውድድር እንጂ የምርጫ ውድድር ቅስቀሳ እያደረጉ አይደለም ቢባል ስህተት አይሆንም።
መንደር ላለው ሰው ይታሰብለት፤ በየመንደሩ በየቀበሌው እየወረዱ በመቀስቀስ መራጩን ለድምጽ መስጠቱ ሊያዘጋጁት ይገባል ብዬ አስባለሁ። ህብረተሰቡ በተለይ ወጣቱ ክፍል እንደ ማህበራዊ ሚዲያ፣ የቴለቪዥን ፊልሞች፣ የአውሮፓ እግር ኳስ ጨዋታዎች የመሳሰሉት ሱሰኛ መሆኑ ይታወቃል። እነዚህ ደግሞ በመኖሪያ ቤትና አካባቢ በስፋት የሚከናወኑ ናቸው። በእነዚህ ክፉኛ በመጠመዱ ከእነዚህ ውጪ ያለውን እንቅስቃሴ አይከታተልም።
በዚህ የተነሳም በቴሌቪዥን የሚደረገውን ቅስቀሳ ታዳሚው ሥራዬ ብሎ ለማየት ፍላጎት የለውም። ፓርቲዎቹ ያገኙትን የአየር ሰዓትና አምድ እያዋዙ መጠቀም ቢጠቀሙ ህብረተሰቡን ሊቀርቡት ይችላሉ። ይህን ህዝብ ለምርጫው ማዘጋጀት ብዙ መሥራትን እንደሚጠይቅ የፓለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም የግል ተወዳዳሪዎች መገንዘብ ይኖርባችኋል።
ሌላው በሚዲያ የሚደረገው የምርጫ ቅስቀሳን የተመለከተ ነው፤ አብዛኞቹ ቅስቀሳዎች ቀልብን የሚስቡ አይደሉም፤ ፓርቲ ተችተው ሰዓታቸውን ጨርሰው የሚሰናበቱ አሉ። ሀሳባቸውን ሰው አንብቦ እንዲረዳ ነው የሚጠቁሙት። ሰነዱ የት እንደሚገኝ እንኳን ሳይገልጹ።
ህዝቡ ፓርቲዎችን ሳይሆን ይዘው የተነሱትን ሀሳብ እንዲገነዘብ ማድረግ ላይ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፤ አሁን ባለው ሁኔታ አብዛኛው ህዝብ የፓርቲዎቹን ስም ከማወቅ የዘለለ ይዘው ስለተነሱት ሀሳብ ያውቃል ብሎ መናገር ይከብዳል። ይኼ ትልቅ ድክመት ነው። በአስቸኳይ ሊታረም የሚገባው ድክመት ነው።
ፓርቲዎችም ሆናችሁ የግል ተወዳዳሪዎች ሀሳባችሁ እንዲታወቅ ማድረግ ላይ መስራት አለባችሁ። ለዚህም እስካሁን የሄዳችሁበትን ርቀት በመገምገም ለቀጣይ ስራችሁ የሚሆነውን አቅጣጫ መቀየስ ይገባችኋል። ህዝቡን በተደጋጋሚ ማግኘታቸሁ ላይ አጥብቃችሁ ስሩ።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ግንቦት 15/2013