ከተማዋን ከእህል በማገናኘትና አንጋፋውና የሚደርስበትም የለም። በስምና በዝናው የከተማዋ ነዋሪዎች፣ ወፍጮ ቤቶችና ነጋዴዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ በተለያዩ ክልሎችና የከተማዋ አካካቢዎች የሚኖሩ ህዝቦች በተለይም ገበሬዎችና የእህል ነጋዴዎች ጭምር የህይወታቸው ዋልታና ማገር አርገው ይመለከቱታል። የመሳለሚያ እህል በረንዳ።
እህል በረንዳው የሚገኘው በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለከተማ መሳለሚያ በሚባለው አካባቢ ነው። ከመርካቶ አውቶብስ መናኸሪያ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኘው የእህል በረንዳው፣ መሳለሚያ በሚገኘው አዲስ ከተማ እሳት አደጋ መከላከያ ጣቢያ እና በአማኑኤል የአዕምሮ ህክምና ሆስፒታል መካከል ይገኛል። ከመሳለሚያ በአማኑኤል ወደ ኮካኮላ ፋብሪካ የሚወስደው ጠባብ አስፋልት መንገድም በእህል በረንዳው አርጎ ነው የሚያልፈው።
እህል በረንዳው አራት ትልልቅ በግምብ የተሠሩ የእህል መሸጫ መጋዘኖች አሉት። አካባቢው ከምሽት እንስቶ እስከ ረፋድ ድረስ ከፍተኛ የሆነ የከባድ መኪና ተሽከርካሪዎች መጨናነቅ ይታይበታል። ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ የሚታይበት አካባቢ ነው። ከክልል እህል ጭነው የመጡ እንዲሁም ከእህል በረንዳ እህል ጭነው መውጣት የሚፈልጉ ከባድ ተሽከርካሪዎች የሚያራግፉትም አራግፈው የሚጭኑትም ጭነው ከተማዋን ለመልቀቅ የሚጣደፉባትና እንቅልፍ የሌለበት አካባቢ ነው። የእህል በረንዳ ገበያው የሚታየው ጠዋት ጠዋት ነው።
የበዓል ቀን ካልሆነ በስተቀር ገበያው መቀዛቀዝ አይታይበትም። ዓመቱን ሙሉ ገበሬዎች እያመረቱ ነው ብላችሁ ልትገምቱ ትችላላችሁ። የገበሬው እህል መጀመሪያ እህል በረንዳ አርፎ ነው ከዚያ ወደ ከተማው የተለያየ አካባቢ በነጋዴዎች እና በሸማቾች አማካይነት የሚሰራጨው።
ወደ ውስጥ ሲዘለቅም በተመሳሳይ መልኩ የተሠሩ አራት የእህል መሸጫ መጋዘኖች አሉ። ከአማኑኤል ቤተክርስቲያን ጀርባ ከአውቶቡስ ተራ እስከ 18 ማዞሪያና ሉኳንዳ የሚወስድ ባለሁለት ተካፋች ሠፊ መንገድም ከእህል በረንዳው በስተጀርባ አለ። ከእዚህ መንገድ በስተጀርባም ከአስፋልቱ ማዶ ቆርቆሮ በቆርቆሮ የተሠራ ትልቅ የእህል ገበያ መጋዘን ይታያል። ይህም አገልግሎቱ እየተስፋፋ መሆኑን ያመልክታል። ከእህል በረንዳ ጀርባ ሆናችሁ የአስፋልቱን ስፋት የጭነት መኪናዎቹን ብዛት ስታዩት የእህል በረንዳ ዋናው ቦታም ይሔኛው ሊመስላችሁ ይችላል።
ወደ ጎን በተደረደሩት ግዙፍ የእህል ገበያ መጋዘኖች መካከል ላይ በርካታ ትላልቅ ባለተሳቢ የጭነት መኪኖች እህል ጭነው ገብተው ሲያራግፉ ማየት የእለት ተእለት ትእይንት ነው። ወደ እህል በረንዳው የሚመጣውን የእህል ጭነት ብዛት ለተመለከተ መጋዘኖቹ ምን ያህል ሰፊና ግዙፍ እንደሆኑ መረዳት አያዳግትም። የሌለ የእህል አይነት የለም፤ ጤፉ፣ ስንዴው፣ ባቄላው፣ በቆሎው፣ አተሩ፣ ሽንብራው. የቅባት እህሎቹ ወዘተ፣ በመጋዘኑ ይራገፋል ፤ ይሸጣል። ነጋዴዎች ከመሳለሚያ እሳት አደጋ ጀምሮ ያሉት ትናንሽ ቤቶች ለእህል መሸጫ ይጠቀሙበታል። የተወሰኑትም ዱቄት ይሸጣሉ ፤ በእህል መጋዘንም እህል እያራገፉ የሚያከማቹ ነጋዴዎች አሉ።
በጅምላና ችርቻሮ ንግድ የተሰማሩ ነጋዴዎች፣ ለቤተሰብ ፍጆታ እንዲሁም ለተለያዩ አገልግሎቶች እህል የሚሸምቱ የህብረተሰብ ክፍሎችን፣ አሽከርካሪዎች፣ ረዳቶች፣ ደላሎችን በአካባቢው በስፋት ታያላችሁ፤ ማለዳ ላይ ደግሞ በእጃቸው ጆንያ መሠርሰሪያ ወይም መጎርጎሪያ (እንደ ጦር የምትወጋ ብረት) ይዘው የሚሸጡትን የእህል ዓይነት ከየጆንያው ውስጥ እየሰረሰሩ እያወጡ የሚያሳዩ በጣም በርካታ ናቸው። ለነጋዴዎቹ እያሳዩ በአይሱዚ የጫኑትን እህል የሚያስረክቡ ይታያሉ። የእህሉን ዓይነትና ጥራት ለማሳየት በእህል መሠርሰሪያው ማዳበሪያውን ወጋ አድርገው የሚያሳዩ ሰዎችን ከየጭነት መኪናው ላይ ታያላችሁ። ማዳበሪያው ተቀደደ እህሉ ፈሰሰ ብትሉም ማዳበሪያም ተመልሳችሁ ስታዩት የተነካ አይመስልም፤ የእህሉ መጠን ላይም ያን ያህል ሊደርስ የሚችል ቅናሽ አይኖርም።
ከአማኑኤል ሆስፒታል ፊትለፊት ባሉት መንደሮችም እህል የጫኑ መኪኖች በብዛት ይቆማሉ፤ ከመኪኖቹ ላይ ለነጋዴው በጅምላ፣ ለሸማቹ ደግሞ በችርቻሮ ይሸጣል። በጆንያ መሰርሰሪያ እህል ከሚያሳዩት በተጨማሪም ጠዋት ላይ የጫኑትን እህል ለናሙና በላስቲክ ይዘው በየቦታው የሚቆሙ ሻጮችና ደላላዎች በርካታ ናቸው። እግረ መንገዳችሁን ስታልፉ እንደ መስታወት በጠራ ፕላስቲክ የያዙት የእህል ዓይነት ወለል ብሎ ይታያቹሀል። ጤፍ ከሆነ ነጭ ይሁን ቀይ ወይም ሠርገኛ በቀላሉ ትለያላችሁ።
ይህን ይዛችሁ የእህል በረንዳ ነጋዴዎችን ከጥቃቅንና አነስተኛ ነጋዴዎች ተርታ የሚመደቡ ናቸው ብላችሁ እንዳታስቡ። አደራ። ዕውቅና ስላልተሰጣቸው ነው እንጂ፣ ከአስመጪና ላኪ ተርታ የሚመደቡ ናቸው። እህል በረንዳ እህል፣ እህል የሚጭኑ ተሽከርካሪዎች፣ ደላሎች፣ ሾፌሮች፣ ረዳቶች፣ ወዘተ ብቻ የሚተራመሱበት አይደለም። ወፎችና አህዮች በጎችና ፍየሎችም የመሳለሚያ በረንዳ ትእይንት አካላት ናቸው።
ሁሉም ተዋንያን የየራሳቸው ሰአት አላቸው። እህል የሚገባበትና የሚወጣበት ጊዜ አለ፤ ከምሽት እስከ እኩለ ቀን። ከዚህ በሁዋላ ያለው ተራ ደግሞ የወፎች ነው ይባላል። በረንዳው የወፎች ህልውና ነው። በዚያ ያለው የእህል ፍሳሽ ወፎቹን አካባቢውን እንዲመርጡት አርጓቸዋል።
ብዛታቸው ይገርማል፤ እጅግ በርካታ ናቸው። ምንም ዓይነት ዛፍ በሌለበት ከየት መጡ ያሰኛል። በእህል መሰርሰሪያ እህል የሚያሳዩ የመኪና ጫኝ ነጋዴዎች፤ እህል በላስቲክ የያዙ ነጋዴዎችና ደላላዎች በመኪና እህል ጭነው ያመጡ የእህል በረንዳ ነጋዴዎች ሁሉ ለናሙና ለገዢዎች እህል አሳይተው ሲያበቁ የቀራቸውን እህል መሬቱ ላይ ይበትናሉ፤ ጆንያው ሲወርድ ሲወጣ የሚንጠባጠበው አለ፤ ጫኝና አውራጆችም ሲጭኑ የተወሰነ እህል ይበትናሉ። የእህል ገበያ ውስጥ ለውስጥ መንገዱ አስፋልቱም ሆነ እግረኛ መንገዱ እህል አይጠፋበትም።
ይህን ህይወታቸው ያረጉ ወፎች የበረንዳው ግርግር እስከሚሰክን ድረስ፣ እርግቦችና የተለያዩ ወፎች በመጋዘኖቹ ጣራና በአቅራቢያው በሚገኙ ህንፃዎች ላይ እንዲሁም በኤሌክትሪክ መስመሮች እንደ ወታደር ጎን ለጎን ተሠልፈው ተቀምጠው ይቆያሉ። ስታዩዋቸው ትገረማላችሁ። ችግሩ የኔ ይሆናል እንጂ በአካባቢው ዛፎች በብዛት አሉ ብላችሁ ልትናገሩም ትችላላችሁ። አማኑኤል ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ እንዲሁም ከመሳለሚያ አዲስ ከተማ እሳት አደጋ መከላከያና መቆጣጠሪያ አጠገብ በሚገኘው ምዕራብ ጤና ጣቢያ ጥቂት የሚባሉ ዛፎች ከመኖራቸው በስተቀር፣ በአካባቢው ዛፎች የሉም፤ አካባቢው እንደ መርካቶና ሰባተኛ ሁሉ ዛፍ ነጻ የሚባል ነው። ወፎቹን ስትመለከቱ ግን ዛፍ በሌለበት ሁኔታ ከየት መጡ ትላላችሁ።
ከሰዓት በኋላ ገበያው ሲቀዘቅዝ እናቶች እህል ሲያበጥሩ እንደ ኑግ ዓይነት ምርቶችን ደግሞ ሲነፉ ከመታያታቸው ውጪ ገበያተኛው ቀዝቀዝ ይላል። አሁን ተራው የወፎች ይሆናል። በመንገዶቹ እና በአስፋልቶቹ ወፎች እያረፉ እህል እንደልብ ይለቅማሉ። እኔ በእህል በረንዳዎቹ አስፋልት መካከል አልፌ እንዳየሁት ወፎቹ አስፋልቱን ይሞሉታል። ሰው ሲያልፍ ትንሽ ፈቅ ይላሉ እንጂ ተነስተው እንኳ በረው አይሄዱም። ወፎቹ ለማዳ ሆነዋል ቢባል አባባሉ አይገልጸውም። መኪና ከመጣ ወይም ሰዎች እየበረሩ ወደ ወፎቹ ከመጡ ወፎቹ ወደ ጣራቸው እየበረሩ ይወጣሉ።
በሥፍራው የሚገኘው አህያ ብዛትም ሌላው የእህል በረንዳው ትእይነት ነው። በአዲስ አበባ ከተማ ይህን ያህል አህያ ሊኖር ይችላል ተብሎ አይታሰብም። የኢትዮጵያ ዋና ከተማ፣ የአፍሪካ ህብረትና የተመድ ተቋማት መቀመጫ በሆነች ከተማ የእህያ ትራንስፖርት በዚህ ልክ መኖር ቢያስገርም አይደንቅም።በርካታ አህዮች ያላቸው የእህል ጭነት አገልግሎት ሰጪዎች አሉ። በርካታ ሰራተኞችን ቀጥረውም ነው የሚሰሩት። በአንድ ጊዜ በአንድ አህያ 100 ኪሎ እየጫኑ ወፍጮ ቤት እና መኖሪያ ቤት ያደርሳሉ። በቀን አራት አምስቴ ይጭናሉ።
የአህዮቹ መኖም ከእህል በረንዳ እህል ብጣሪዎች ይገኛል፤ አንዳንዴም አህያው ቀኑን ሙሉ የለፉበትን ለመካስ ከወፍጮ ቤት የሚወገድ ዱቄትና ብጣሪ እንዲመገብ ይደረጋል። የደረቀ ቄጠማ ጉዝጓዝም ሰብስበው የሚመግቡ አሉ። አህዮቹ የሚያድሩት በተለያየ አካባቢ ነው፤ ቀደም ሲል ከእህል በረንዳው አጠገብ አህያ በር በሚባል አካባቢ እንዲያድሩ ይደረግ ነበር።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ግንቦት 14/2013