ሰው ይወለዳል፤ ያድጋል፤ ይሞታል። የተረኝነት ጉዳይ ነው እንጂ ከሞት የሚቀር የለም። በሀዘኔታ ሽኝት ተደርጎለትም ይቀበራል። ሁሉም የማይቀሩ እንደመሆናቸው የሰው ልጅ ሊዘጋጅባቸው ይገባል። መወለድ መኖሩን አውቆ ህጻኑን ለመቀበልና ለማሳደግ እንዲሁም ለቁም ነገር ለማድረስ ዝግጁ ሊሆን ያስፈልጋል። እንደዚህም ሁሉ ሞት መኖሩንም ተገንዝቦ ሞት ቢከሰት ማድረግ ባለበት ሁሉ በጋራ መዘጋጀት ይጠበቅበታል።
በሀገራችን አሟሟቴን አሳምርልኝ ከሚልባቸው ምክንያቶች አንዱ የቀብር ስፍራና ስርዓትን የሚመለከተው ነው። ሰው በጥሩ ሁኔታ እንደ እንደኖረ ሁሉ ጥሩ በተባለ የቀብር ስፍራና ስነ ስርዓት እንዲሸኝም ፍላጎቱ ነው። አንዳንዶች ለዚህ ቁብ ባይሰጣቸውም ጥቂት የማይባሉት ግን በዚህ ላይ አይደራደሩም። በዚህ የተነሳም የሚቀበሩበትን ስፍራ ከመወሰን አንስቶ እስከ መቃብር ቤት ማዘጋጀት ይደርሳሉ።
ይህ ሁኔታ አስቀድሞም የነበረ ሲሆን፤ የቀብር ስፍራ ጥበት እና ውድነት እየበዛ በመጣባቸው ከተሞች ግን በስፋት መከናወን ውስጥ ገብቷል። እንደሚታወቀው እንደ አዲስ አበባ ባሉ ከተሞች እየተፈጠረ ባለው የቀብር ስፍራ ጥበት የተነሳ የቀብር ስፍራን ለዳግም አገልግሎት ወደ ማዋል ከተገባ ዓመታት ተቆጥረዋል። በዚህም በተወሰነ መልኩ የቀብር ስፍራ ላይ ሊደርስ ይችል የነበረውን ጥበት ማቃለል ተችሏል። የቀብር ስፍራ ጥበቱ ግን ቀጥሏል።
የቀብር ስፍራዎችን የሚያስተዳድሩ አካላት /በተለይ በእምነት ተቋማት የሚተዳደሩ የቀብር ስፍራዎችን የሚያስተዳድሩት/ ለቀብር ስፍራ የሚያስከፍሉት ዋጋ እየጨመረ መጥቷል። እንደ አዲስ አበባ በመሳሰሉ ከተሞች ለቀብር ስፍራ /የመሬት/ የሚጠየቀው ገንዘብ ሰውን በቁሙ የሚቀብር ይመስላል።
በአዲስ አበባ አብዛኞቹ የቀብር ስፍራዎች የተያዙት በእምነት ተቋማት መሆኑ ይታወቃል። የቀብር ስፍራ ውድነት የሚታየውም በእነዚሁ አካባቢዎች ነው። ከፍተኛ የሆነ የቀብር ስፍራ ሽሚያ ይስተዋልባቸዋል።
ለቀብር ስፍራ ባለወለል ፉካዎች እየተገነቡ፣ የቀብር ስፍራዎች ለእንደገና አገልግሎት እየተዘጋጁም ነው እጥረቱ እየተፈጠረ ያለው። ባለወለል ፉካዎች በእድሮችና በሌሎች ቡድኖች በብዛት ይገነባሉ። የቀብር ስፍራ እጥረትን በመፍታት በኩል የፉካዎች ሚና ከፍተኛ መሆኑን እዚህ ላይ ሳይገልጹ ማለፍ ትክክል አይሆንም። ወለሎቹ እንዲጨምሩ እንዲሁም ከምድር በታች ሊኖሩ የሚችሉትን ወለሎች ቁጥር መጨመር ላይ ቢሰራበት ጥሩም ይመስለኛል።
ፉካዎቹ ለሽያጭ የሚቀርቡበት ዋጋ ግን በጣም ያሳስባል። በቀብር ስፍራ አካባቢ አንድ ኢንቨስትመንት የተጀመረ ያስመስላል። እርግጥ ነው ፉካዎችን ማዘጋጀት ብዙ ወጪን ይጠይቃል። ያም ቢሆን ግን መሬት በቀላሉ የሚገኝ እንደመሆኑ / የሊዝ ጉዳይ እዚህ ያለ አይመስለኝም/ ያን ያህል የተጋነነ ክፍያ ሊጠይቅበት አይገባም።
ሌላው የአፈር ላይ ቀብርም ውድ እየሆነ ነው። ይህ የቀብር ስፍራ ለቁፋሮ ምናልባትም ለሊሾና ለመሳሰሉት ወጪ ይደረግበታል። ያም ሆኖ ግን ዋጋው ውድ መሆኑን ቀብር ያስፈጸሙ አካላት ሲያማርሩ ይሰማል። ችግሮችን እንደ መልካም አጋጣሚ የመቁጠር ሁኔታ ያለ ይመስለኛል። ይህ ዓይነቱ አሰራር ድሆችን ከግምት ያላካተተ የቀብር ቦታ ክፍያ ማስከፈል ተገቢ አይደለም።
ይህን ስል የሃይማኖት ተቋማትን እየተጋፋሁ እንዳልሆነ ተረዱኝ፤ ያነሳሁት ሃሳብ ከማኅበራዊ ሕይወት አንፃር ነው። ነገር ግን በአንዳንድ የእምነት ማዕከሎች በህዝብ ስም ለቀብር የተወሰደ መሬት ለልዩ ልዩ ተግባራት እየዋለ ነው፤ ይህ ምን ያህል ተገቢ ነው? ማለቴ ልማትን ነቅፌ አይደለም። ማልማት ከፈለጉ ከሚመለከተው አካል ጋር በመነጋገር በዙሪያቸው የሚገኙ ነዋሪዎችና ነጋዴዎች ቤቶች ጋር ተወያይተው የሚገባውን ከፍለው እነሱም ሁሉንም የሚያግባባ ክፍያ የሚከፍሉበትን ሁኔታ አመቻችተው፣ በትንሽ መሬት ብዙ ህንፃዎችን መገንባት የሚችሉ ይመስለኛል።
የተወሰኑ የእምነት ድርጅቶች ከሁለት የዘለለ የቀብር ቦታ የላቸውም፤ የቀብር ቦታ ጠይቀው ለማግኘት ብዙ ዓመታት የወሰደባቸው እንዳሉ አውቃለሁ። እነዚህ ሁሉ ለቀብር ራቅ ወዳለ አካባቢ ለመሄድ ይገደዳሉ። በእስልምናም የኮልፌን መቃብር ጨምሮ በጀሞ፣ ጉራራ፣ ንፋስ ስልክ ላፍቶ፣ ኮተቤ፣ ቱሉ ዱምቶ፣ ሽሮ ሜዳ መቀጠያ አካባቢ እንዲሁም ቀጨኔ በአጠቃላይ ወደ ስምንት መካነ መቃብሮች አሉ። ለቆፋሪዎች ታስቦ ከ300 እስከ 500 ብር ለቀብር ያስከፍላሉ።
ችግሩን ከግምት ማስገባት ያልፈለጉት አንዳንዶች አጋጣሚውን እንደ ሠርግና ምላሽ እየተጠቀሙ ለቀብር ብዙ ገንዘብ እየጠየቁ ነው። በአንዳንድ ቦታዎች በመሀል አዲስ አበባ ለቀብር ስምንት ሺህ እና ዘጠኝ ሺህ ብር ይጠይቃሉ። ሐዘንተኛ ሰዎች ቤተሰብ ሞቶባቸው በክፍያው ሲያማርሩ ሰምቻለሁ።
ወደ ዳር ባሉ አካባቢዎች ለቀብር እስከ ሦስት ሺህ ብር ይከፈላል፤ ግን ወደ ዳር ሄዶ ለመቅበር ከእምነት ተቋማቱ እስከ 500 ብር የሚጠየቅበት ሸኚ ደብዳቤ ይጠበቃል። ይህን ለማጻፍ ደጅ መጥናትና መመላለስን ይጠይቃል። አንዳንዱ መጉላላቱ ሲሰለቸውና ሐዘንተኛውን ቶሎ ለማሰናበት ብሎ ከከተማ ዳር ከግማሽ ባነሰ ክፍያ መቅበር የሚቻልበትን ሁኔታ ትቶ ውድ ክፍያ ከፍሎ ያስቀብራል።
ስለዚህ ሰው መጉላላት ሰልችቶት ገንዘቡን ከፍሎ ያስቀብራል። ፉካ በሚባለው የቀብር ዓይነት ደግሞ የሬሣ ሳጥን እንደ መሳቢያ ከቶ ለመሰናበት ከ30 ሺህ እስከ 60 ሺህ ብር ይጠየቅበታል። በርግጥ ፉካ በሚባለው የቀብር ዓይነት አቅም ያላቸው ሰዎች ሟች ቤተሰብ የሚቀበርበት ቢሆንም፤ ገንዘቡ በዛ ብቻ ሳይሆን ብዝበዛ ብለን ልንግለፀው እንገደዳለን።
የቀብር ሥርዓታችንም ለዛ እያጣ ነው፤ ቀብር ሲፈፀም የሬሣ መኪና እድሮች የሚያቀርቡባቸው አካባቢዎች አሉ። ሌሎች ደግሞ በራሳቸው መኪና ያዘጋጃሉ። ዋጋቸው እየበዛ መጣ እንጂ የግል የቀብር አስፈጻሚዎች እዚህ ላይ ጥሩ እየሰሩ ናቸው። ቀደም ሲል የቀብር ሥርዓትና የአስተዛዛኝ መስተንግዶ በእድር ይሸፈን ነበር። አሁን ዕድሮችም ሊሸፍኑት ስላልቻሉ ከአካባቢው ነዋሪዎች ለቀብር ማስፈፀሚያ መዋጮ ሲሰበሰብ እያየን ነው።
የቀብር ስፍራ እየራቀ መምጣት በራሱ ትልቅ ችግር መሆን ጀምሯል። ለእድርተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት የሚያቀርቡ እድሮች ቢኖሩም፣ የትራፊክ መጨናነቁም መከራ ሌላው ችግር ነው። ከአውቶቡስ ተራ ሽሮ ሜዳ በመኪና ከመሄድ እኮ ከአውቶቡስ ተራ አዳማ መሄድ የፈጠነ ነው ማለት እችላለሁ።
ለቀብር የሚጠየቀው ገንዘብ አንዳንዴ ሟቹ በሕይወታቸው ቆጥረውት የማያውቅ ይሆናል፤ ቤተሰብም ይቸገራል። ድሆችንስ ማን ያስባቸው? በሐዘናቸው ላይ የቀብር ክፍያ ቆልለን በሐዘን ላይ ሐዘን እየጨመርን መሆኑን ተመልከቱ። ድሆች ለመኖርም ተቸግረው ለመቀበርም መቸገር የለባቸውም።
አሁን…አሁን የእድሮች ሚና ለሀዘንተኞች ድንኳን ወንበር ትንሽ ብር በመስጠትና የቀብር ሽኝት ከመፈፀም የዘለለ አይደለም። ዕድሮች ለቀብር የሚከፈለውን ክፍያ እንዲቀነስ መከራከር ይኖርባችኋል። የአዲስ አበባ መስተዳድርም ጉዳዩ የሁሉንም ኅብረተሰብ የሚነካ መሆኑን በመረዳት ችግሩን ለመፍታት ከሚመለከታቸው ጋር እየተነጋገረ ቢሰራ መልካም ነው።
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ኅብረትም በሀገሪቱ ሠላምና ኮሮናን በመሳሰሉ ጉዳዮች እንደሚወያዩት ሁሉ ነዋሪው እየተቸገረ ያለበትን የቀብር ቦታዎች እጥረትና የቀብር ቦታ ውድነት ለመፍታት አጥብቀው ሊሰሩ ይገባል።
ከሞት የሚቀር የለም፤ ለመኖር መኖሪያ ቤትና የመሳሰሉትን እንደምናዘጋጅ ሁሉ ዘላቂ ማረፊያ /የቀብር ሥፍራ/ በግል ማዘጋጀት ባይጠበቅብንም የሚመለከታቸው አካላት የቀብር ሥፍራ ጉዳይ የማያነጋግር ሊሆን የሚችልበትን ሁኔታ እንዲፈጥሩ ግፊት ማድረግ ግን ይጠበቅብናል።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2013