የስራ መውጫ ሰዓት ደርሷል፤ ወደ ቤት ለመሄድ ቶሎ ወጣሁ፤ ውጪ የተመለከትኩት አዲስ ነገር ግን ቆም ብዬ እንዳስብ አደረገኝ። ያለማጋነን ሰላማዊ ሰልፍ በሚመስል መልኩ በርካታ ሰዎች በእግራቸው ይተማሉ። የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥ አንድም ተሸከርካሪ ዝር አይልም፤ምን እየተካሄደ ስለመሆኑ አልገባኝም።
በርካታ የእስልምና እምነት ተከታዮች በመንገድ ላይ ይታያሉ፤ ስለማንነታቸው አለባበሳቸው ያስታውቃል፤ የመስገጃ ምንጣፍ ይዘው ቁልቁል በቤተ መንግስት ወደ መስቀል አደባባይ ይነጉዳሉ። አንዱን ይቅርታ ጠይቄ አስቆምኩና ህዝቡ ወደየት እንደሚሄድ ጠየቅሁት። የተከለከለው የአደባባይ አፍጥር ፕሮግራም መፈቀዱንና ህዝቡም አፍጥር ወደሚካሄድበት ስፍራ እየተጓዘ መሆኑን ሲገልጽልኝ አንድ ነገር ብልጭ አለለኝ። የአፍጥር ፕሮግራሙ ከሜክስኮ እስከ ባምቢስ ባለው መንገድ ላይ እንደሚካሄድ በዜና ተገልጾ እንደነበር አስታወስኩ።
በመገናኛ ብዙሃን የተመለከትኳቸው በባህርዳርና ደሴ የተካሄዱ የአፍጥር መርሃ ግብሮችም ታወሱኝ። በሰፋፊ ጎዳናዎች ላይ እጅግ በርካታ የእስልምና እምነት ተከታዮች በተገኙበት መርህ ግብሩ መካሄዱ ለኢትዮጵያ አዲስ ነው። በዚህ ሰው ያለውን በሚያካፍልበት በሮመዳን ጾም ወቅት በጎዳና ላይ የተካሄደው ይህ የአፍጥር ፕሮግራም የሙስሊሙ ብቻ ሳይሆን የመላ የኢትዮጵያውያንን የመተሳሰብና መረዳዳት እሴት አጎልቶ ያሳየ መሆኑ ታሰበኝ፤ የአዲስ አበባው ደግሞ ልዩ ስነ ስርአት ሊደረግበት እንደሚችል ገመትኩ። እናም የተቀረው ህዝብ የተወሰኑ ርቀቶችን በእግር መጓዙ እዳው ገብስ ነው እንድል አረገኝ።
ይህን መረጃ እንዳገኘሁ እንዴት አድርጌ ወደቤቴ መሄድ እንዳለብኝ መወሰን ነበረበኝ። ትራስንፓርት እስከሚገኝ ድረስ በአግር መሄድ እንዳለብኝ ተረዳሁ። ሳላቅማማ በእግሩ ከሚተመው ህዝብ ጋር ተቀላቀልኩ። የሌሎች እምነት ተከታዮችም ከየቢሮው እየወጡ የእግር ተጓዡን እየተቀላቀሉ ናቸው። ሰራተኞች ስራ ላይ ሲደክሙ ቢውሉም፣ ፈጥነው ቤታቸው መድረስ ቢፈልጉም ትራንስፓርት የለም። ሰራተኞቹ የተፈጠረው የትራንስፓርት መስተጓጎል ምቾት አልነሳቸውም፤ ይልቁኑም ድካማቸውን ረስተው፣ ፈጥነው ቤታቸው ለመድረስ የነበራቸውን ፍላጎት ትተው መጓዛቸውን ቀጥለዋል። ለዚያውም ረጅም ርቀት።
ጉዞው የማይተዋውቁትን እያስተዋወቀ ጨዋታ የደራበት ሆኗል። አብረውኝ ከሚጓዙ ሰዎች መካከል አንደኛው “ይህች ናት የኔ ኢትዮጵያ !” ሲል ተናገረ። መልስ ከማንም ሳይጠብቅ ስላነሳው ሀሳብ ማብራራት ጀመረ።ግለሰቡ ከአነጋገሩ የክርስትና እምነት ተከታይ እንደሆነ ተረዳሁ። ይህን ያልኩት “እኛ!” ጥምቀትን እንዲሁም የተለያዩ ሀይማኖታዊ ወርሃዊ እና ዓመታዊ የንግስ በዓላትን ስናከብር እና መንገድ ስናዘጋ ሙስሊሙ ማህበረሰብ በመቻቻል በሰላም እንድናከበር ሲያደርግ ነው የኖረው፤ እኛም ይኸው በእግራችን እየተጓዝን እነሱ የአደባባይ የአፍጥር ስርዓት እንዲያከብሩ ምቹ ሁኔታ እየፈጠርን ነው ሲል ማብራራቱን ቀጠለ።
አሁንም የት ቦታ ላይ ታክሲ እንደማገኝ አላውቅም፤ ብቻ ወደ አካባቢዬ የሚወስደኝን መንገድ ይዣለሁ፤ ህዝበ ሙስሊሙም ከተለያየ አቅጣጫ መትመሙን ቀጥሏል። ሰውዬው መናገሩን ቀጥሏል። ያለአንዳች ማቅማማት በተፈቀደው መንገድ በእግር እየተጓዝን ነው፤ ከዚህ በላይ “ኢትዮጵያዊነት” እና መቻቻል የለም፤ ሲል ሀሳቡን አብራራ። ሁላችንም በሀሳቡ መስማማታችንን ጭንቅላታችንን በማነቀሳቀስ እየገለጽን ጉዟችንን ቀጠልን።
በመሐል በእድሜ ከፍ ያሉ ግለሰብ ደግሞ ሀሳባቸውን መስጠት ቀጠሉ። እኚህ ሰው አራት ኪሎ ከሚገኙ የመንግስት መስሪያ ቤት በአንዱ ለበርካታ ዓመታት የሰሩ ናቸው። ለዚህች ሀገርና ህዝብ መቻቻል ትልቅ ዋጋ እንዳለው ነገሩን። መቻቻል የተለየ የዓለም አተያይ፣ የአኗኗር ዘይቤ፣ ባህሪ እና ወጎችን የሚያመለክት ገዥ ሀሳብ ነው ሲሉ አብራሩልን።
አስተያየቶቹን ስሰማ የደበተኝ ሁሉ ይለቀኝ ጀመር። መቻቻል የተለየ የዓለም አተያይ ወይም ባህሪን መቀበል ማለት አይደለም፣ ለሌሎች እንደፈለጉት የመኖር መብትን መስጠት ብቻ ነው አሉን። እኛም በደስታ ከአጠገባቸው ሆነን እየተጓዝን በዘመን መካከል የተማሩትን እውነት እየቀሰምን እየተጓዝን ነው፤ ከጎናችን ለሃይማኖት፣ ለፖለቲካ ወይም ለሥነ ምግባር ተቃራኒ አመለካከት ያላቸው ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፣ እነዚህ ሰዎች የተለየ የዓለም አተያይ ስላላቸው ብቻ መጥፎዎች ናቸው ማለት አይደለም ሲሉ አብራሩ።
መቻቻል ማለት የሌሎችን ባህሎች ማክበር እንዲሁም የሰዎች ግለሰባዊነት መገለጫ መሆኑን ተናገሩ። በተመሳሳይም የመቻቻል መገለጫ በጭራሽ ማህበራዊ ኢ-ፍትሐዊነትን መቻቻል፣ የራስን አመለካከት አለመቀበል ወይም የራስን አመለካከት በሌሎች ላይ መጫን ማለት አለመሆኑንን ገለጹልን።በግለሰቦች ወይም በማኅበረሰቦች መካከል ውጥረቶች የሚከሰቱት ከአድሎና ካለመቻቻል ነው። አለመቻቻል ለማንኛውም ማኅበረሰብ ሰላምና መረጋጋት አደጋ ወይም ስጋት ነው። የተለያየ ዘውግ፣ ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለምና ኢኮኖሚያዊ ደረጃ ባላቸው ቡድኖች መካከል የሚኖር መረዳዳትና መተባበር ለሰው ልጆች ሕልውና ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሰላምም ያስፈልጋል። መቻቻል አመጽንና ጭቆናን ለማጥፋት ተፈላጊ የማኅበራዊ ግንኙነት ቀዳሚ እሴት ነው።
እኔም ከወዳጆቼ ጋር የተስማማሁባቸው ብዙ እውነታዎች አሉ፤ መቻቻል በማኅበረሰብ ውስጥ ሊከሰቱ የሚችሉ አለመግባባቶችንና ብጥብጦችን አስወግዶ ሰላምን ለማስፈን ያስፈልጋል። አለመግባባትና አለመስማማት የሰው ልጅ ሕይወት አካል ናቸው። ከመቻቻል ሌላ ያለው ብቸኛ አማራጭ ደግሞ ግጭት ነው። መቻቻል ነጻነትን ይወልዳል፤ ነጻነት ማለት የራሳችንን ሕይወት በፈለግነው መንገድ መምራት ማለት ነው። ሕይወታችንን በመረጥነው መንገድ መምራታችን፣ የራሳችንን ምርጫ በራሳችን መወሰናችን ትልማችን፣ ሀሳባችንና ስሜታችንን ለመግለጽና ለማጎልበት ይረዳናል። ነፃነት ደግሞ በራሱ ደስታ፣ እርካታ አለው። ይህን ማድረግ በራሱ የራሱ እርካታና ደስታን ይሰጣል። ሰዎች ነፃ ከሆኑ፣ የተለያየ እምነቶችንና እሴቶችን ማንፀባረቅ ይችላሉ፤ ይህን ደግሞ ተቻቻይ መሆንን ይጠይቃል።
ሰዎች መልካም የሚሉትን በራሳቸው መንገድ ለማግኘት ሲጥሩ፣ የሕይወትን መንገድ ይመለከታሉ፤ በዚህም ኑሯቸው ምን እንደሚሰራና ምን እንደማይሰራ፣ ምን ወደ መልካሙ እንደሚመራቸውና ምን እንደሚያስተጓጉላቸው ያውቃሉ።
ይህ የሕይወት ተሞክሮ ከተገደበ የመሻሻል፣ አዲስ ነገር የማግኘት ዕድልም ይገደባል፤ ትክክለኛ እንዲሁም ጎጂ መንገዶች እንዳይታወቁ ያደርጋል፤ ሰዎች ሌሎች አማራጮችን አይተው የአኗኗር ዘይቤያቸውን እንዳይጠይቁ እንቅፋት ይሆናል፤ የተለያዩ ሰዎች ለማደግና የተሻለ ደረጃ ለመድረስ የሚያስፈልጋቸውን የተለያየ ከባቢ እንዳያገኙ ያደርጋል ።
ከዚህ ሁሉ ብዝሃነት ወደተሻለ የአኗኗር ዘይቤ፣ ማኅበራዊ መሻሻልና ታላቅ ደስታ እንደሚመራን እንረዳለን። ብዝሃነት ደግሞ መቻቻልን ይሻል። አዲስ አበቤዎች ከአፍጥር መርሀ ግብሩ ጋር በተያያዘ ጎዳናዎች ለተሸከርካሪዎች ዝግ መሆናቸውን ተከትሎ ብዙ ኪሎ ሜትሮችን በእግር የተጓዙበት የሜክሲኮ አደባባይ ባምቢስ የጎዳና ላይ አፍጥር መርሀ ግብር 15 ሺህ ሰዎችን በማሳተፍ ተጠናቅቋል።
ታላቅ ትዕይንት የተካሄደበትና እና ተጠቃሽም ለመባል በቅቷል። መርሀ ግብሩን በቀጥታ ስርጭት እንደተከታተልኩትም ደማቅና የእምነቱን ተከታዮችም በእጅጉ ያስደሰተ ነው። ለሀገራችን አዲስ ከስተትና ደማቅም ነው።የአፍጥር መርሀ ግብሩ መሳካት ትርጉሙ ብዙ ነው። የኢትዮጵያውያንን የመረዳዳትና የመቻቻል እሴት በጉልህ ማሳየት የቻለና የአለመግባባት ደጋሾችን በእጅጉ ያሳፈረም ነው። በእርግጥም መቻቻልን ያዩበት ትእይንት። ሰላም !!
የልቤ ደርሶ
አዲስ ዘመን ግንቦት 7/2013