በቀደሙት ዘመናት የነበሩት ትምህርት ቤቶቻችን ከመደበኛ ትምህርት በተጓዳኝ ትምህርቱን የሚያጎልብቱ የተለያየ እውቀት ያስጨብጡም ነበር። ግጥምና ስነጽሑፍ፣ ሥዕል፣ ድራማ፣ ዘፈንና ውዝዋዜ፣ የመሳሰሉትን ። እነዚህም ያደርጉ የነበረው ክበባትን በመመስረት ነው። አሁንም ይህን መሰል ከበቦች በዓይነትም ሰፋ ብለው በየትምህርት ቤቶቹ ይታያሉ።
በተጓዳኝ ትምህርት ረገድ ፈር ቀዳጁ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ነው። በዚህም ተሰጥኦን ለማዳበር ከመደበኛ ትምህርት ሰዓት ውጪ ሲሰጡ በነበሩ ትምህርቶች ፍሬያማ የሆኑበትን ሁኔታ መጥቀስ ይቻላል። እነዚህ ደግሞ አሁን ላሉት ታዳጊዎችና ወጣቶች ብቻ ሳይሆን ለትምህርት ቤቶችም ጭምር ምሳሌ ናቸው።
ክበባት በአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተጓዳኝ የትምህርት አካል ሆነው በትምህርት ቤቶች ይመሠረቱ ነበር፤ በክበባቱም ተማሪዎች እንደፍላጎታቸውና ችሎታቸው ተሳትፎ ያደርጋሉ። በትምህርት ሙያዊ ቋንቋ ተጓዳኝ ትምህርት ማለትም (Co-curricular activity) ተብለው ይጠቀሳሉ። በተለይ አንደኛ ደረጃ እያለን የነበሩ የሚዲያ ክበባትን አስታውሳለሁ። ነገር ግን ከትምህርት ቤቱ ተማሪዎቹ ሲለቁ ቀጣዮች እየተቀበሉ አስቀጥለውት ነበር።
ክበብ ማለት እንደ ደርጅት ከአንድ በላይ በሆኑ ሰዎች ሊመሠረት የሚችል ፤ በአብዛኛው በአንድ ነጠላ ጉዳይ ሙያ ላይ አተኩሮ የሚሠራ ነው። እነዚህ ክበባት በትምህርት ቤት ውስጥ ብቻ የሚመሰረቱ አይደሉም። በየአካባቢው፣ ወረዳው ቀበሌውም እየተመሰረቱ ወጣቶች ያላቸውን ክህሎት እንዲያዳብሩ ያስችላሉ። ክበባቱ ከንድፈ ሃሳብ ትምህርት ባሻገር ተግባራዊ ትምህርት የሚሰጥባቸው እንደመሆናቸው ማህበረሰብ ውስጥ ገብተው ለመሥራት ጥሩ ሜዳ ናቸው ማለት ይቻላል።
በአዲስ አበባ በቲያትርና በሙዚቃ ወጣቶችን በማሰልጠን የሚታወቁት አቶ ተስፋዬ አበበ በተለምዶ ፋዘር ብዙ ዝነኛ ወጣቶችን አብቅተዋል። በተዘዋዋሪ ወጣቶቹ በክበባት ባይደራጁም አማተሮች የነበሩ ለመሆኑ ጥናትና ምርምር አያሻውም። ስለ ቲያትር ክበባት ካወራን አፍለኛው ይጠቀሳል። እነ ሠራዊት ፍቅሬ የዚሁ ክበብ ውጤት ናቸው።
ደራሲና ሃያሲ አስፋው ደምጤ ባንድ ጥናታዊ ጽሑፋቸው በእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የሌለ የክበብ ዓይነት እንደሌለ ይጠቅሳሉ፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ከመደበኛው ትምህርት ባልተናነሰ ጥቅም ያገኙባቸው ሁለት ክበባት ተሳታፊ ነበሩ፤እነሱም የስነ ግጥም ክበብና የፍልስፍና ክበብ መሆናቸውን በማኅበራዊ ጥናት መድረክ መጽሐፍ ህትመት(በ19 98) አስረድተዋል።
በ19 90ዎቹ አካባቢ የጋዜጠኞችና የስነጽሑፍ ክበባት እንደአሸን የፈሉበት ወቅት ነበር። ውበት፣ ጳውሎስ ኞኞ፣ ሠናይና ክልል 14 በወቅቱ ከነበሩ ከሚጠቀሱ አማተር የጋዜጠኞች መካከል ናቸው። ለዚህም በወቅቱ በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ይታተም የነበረው የዕለተ ሰንበት አዲስ ዘመን ዝግጅት ክፍል ትልቅ ሚና ነበረው። የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል የዕለተ ሰንበት ጋዜጣ የአንባቢያን ክበብ እንዲቋቋም መሠረት ጥሏል።
አማተር የጋዜጠኞች ክበባቱ ጋዜጣው ላይ የሚወጡ ጽሑፎችን አንብበው ግብረ መልስ (feedback) እየሰጡ ሲሳተፉ ቆይተዋል። ቀስ በቀስም ለጋዜጣው ልዩ ልዩ ዓምዶች ወጥ ጽሑፎች ግጥምና ትርጉም ጽሑፎችን በመስጠት ተሳታፊዎች ነበሩ። ይህም ክበባቱ ታዳጊዎቹ የማንበብ ባህል እንዲኖራቸው ብቻ ሳይሆን የጽሑፍ ክህሎት እንዲኖራቸው መሠረት የጣለ መሆኑን ያመለክታል።
በዚህም መሠረት አባላቱ ለጋዜጣና ለሬዲዮ ዝግጅቶች በስማቸውና በክበባቸው ስም ግብረ መልስና አስተያየት ከመስጠት በተጨማሪ በግጥም በልቦለድ በወጥና ትርጉም ጽሑፎች ተሳታፊዎች ነበሩ። ጽሑፎቹ ሲወጣላቸው የሚያገኙት ገንዘብ ባይኖርም እርካታ ይሰማቸው እንደነበር አስታውሳለሁ። ከአማተር ተነስተው በእርካታ እርካብ ወደ ስነጽሑፍና ጋዜጠኝነት መንበር የወጡ ይገኙበታል።
እኔ የዚሁ አካል ስለነበርኩ በመርካቶ የግል ሙያዊ ሥራዬን እየሠራሁ ስሳተፍ ቆይቻለሁ። በዚሁ ጋዜጣ በባህል እና የልጆች ዓምድ በትርጉምና ወጥ ጽሑፎች ተሳታፊና ተሰላፊ መሆኔን አስታውሳለሁ። ዛሬ ብዕሬ ወግ ደረሳትና በአማተርነት እሠራበት በነበረው በዚሁ ጋዜጣ በፕሮፌሽናልነት ተቀጥሬ በቋሚ ተሰላፊነት እየሠራሁ ነው።
በስነጽሑፍ በኩልም ሐመረኪን የስነጽሑፍ እና ጎልማሳዎቹ የፍካት ደራሲያን አባላት ይጠቀሳሉ። በክበባቱ በሩሲያ ፑሽኪን የባህል ማዕከልና በተለያዩ አዳራሾች በየጊዜው የግጥም ስነጽሑፍ ምሽቶች ይካሄዱ ነበር። እነ ደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ እና በዕውቀቱ ስዩም ከስነፅሑፍ ክበባቱ የወጡ ናቸው።
ክበባቱ ዛሬ ባይኖሩም አንባቢያንን መፍጠር ብቻ ሳይሆን አንጋፋ ወጣት ፀሐፊያንን ለማብቃት የቻሉበት ደረጃ ደርሰዋል። እናም በወቅቱ በክበባት የታቀፉትን ወጣቶች የሚበረታቱ እንቅስቃሴዎችና ዘገባዎች በዘመኑ በነበሩት በጣት የሚቆጠሩ ሚዲያዎች ይተላለፉ ነበር። ትልልቅ የስነጽሑፍ ምሽት ሲኖራቸው በሬዲዮ ቴሌቪዥንና ህትመት ሚዲያዎች ሽፋንና ዘገባ ያገኙ ነበር።
ከክበባቱ በርካታ ሰዎች የማንበብ ባህል አዳብረዋል፤ በክበባቱ ታቅፈው ደራሲ ገጣሚና ጋዜጠኛ የሆኑ ሰዎች አሉ። ፍካት የደራሲያን ክበብ በሕይወት እያለ (ክበቡን ማለቴ ይሰመርበትና) አንድ መጽሐፍ አባላቱ በጋራ የጻፉበትን አሳትመው ነበር። በክበባቱ ታቅፈው የነበሩ ወጣቶች ገሚሶቹ በዝንባሌያቸው እየሠሩ ሲሆን፤ ሌሎቹ በሌላ ሙያም እየሠሩ ውጤታማ መሆን የቻሉ በራስ የመተማመን መንፈስን የገነቡ ናቸው።
ባለፈው ሳምንት በግዮን ሆቴል ግሮቭ ጋርደን መናፈሻ የውበት አማተር የጋዜጠኞች ክበብ አባላት ተሰባስበው 26 ዓመታቸውን አክብረው ነበር። አባላቱ በአሁኑ ወቅት በየፊናቸው በልዩ ልዩ ሥራዎች የሚገኙ ቢሆኑም ከፊሎቹን ጎን ለጎን የጋዜጠኝነትና የስነፅሑፍ ሥራ ይሠራሉ ፤ የተወሰኑት በተግባቦት ባለሙያነት የተወሰኑት ደግሞ ሙሉ ለሙሉ በጋዜጠኝነትና በስነጽሑፍ የሚሠሩም ይገኙባቸዋል። አስቻለው ጌታቸው፣ እስክንድር መርሐጽድቅ፣ አዜብ ታምሩ፣ ጅላሎ አወል፣ ጋዜጠኛሔኖክ ስዩም ሀገሬ፣ የአዲስ ስታንደርድ ኦንላይን ስርጭት መሥራችና ጋዜጠኛ ፀዳለ ለማ ይጠቀሳሉ።
ከውበት አማተር የጋዜጠኞች ክበብ በወቅቱ አዲስ አበባን ጨምሮ በ42 ከተሞች ቅርጫፍ ኖረውት አባላቱ በስነጽሑፍና በጋዜጠኝነት ይሳተፉ ነበር። በዚህም ለጋዜጦችና ሬዲዮ ፕሮግራሞች በመፃፍ አስተያየት በመስጠት ይታወቃሉ። ከነዚህ መካከል ሃይረዲን ከዲር ከአሰላ (አሁን በአዲስ አበባ በአንድ እምነት ተቋም በተግባት ባለሙያ የሚሠራ) ዑመር ጃፈር ከይርጋጨፌ ዓለምእሸት ምህረቴ ከደባርቅ ኤልያስ ተስፋዬ ከወንጂ (አሁን በዐቃቤ ሕግ ባለሙያነት እየሠራ ጎን ለጎን በህግ ጉዳይ ለጋዜጦች የሚጽፍ) ይገኙበታል።
ከክበቡ አባላት ስድስት ወጣቶች በሀገሪቱ ከመጀመሪያው የማስሚዲያ ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ተመራቂዎች መካከል (ጋዜጠኝነት በዲፕሎማ) ነበሩበት፤ ከአባላቱ 16 የሚደርሱት በየፊናቸው ግጥም ልቦለድ ትርጉም መፃሕፍት አሳትመዋል።
አሁን ግን ክበባቱ ተተኪ ሳያፈሩ ደርቀዋል። እነዚህን መሰል ክበባት እዚህ ጋ አሉ ለማለት የሚያስደፍር ሁኔታ የለም። ሌሎች ክበባት ተፈጥረው ቢሆን እነዚያን በዚያ ልክ ባናያቸው ብዙም ላያስገርም ይችላል።
እነዚያ ታላላቅ ክበባትም አድገው ከፍተኛ ደረጃ ደርሰው አላየንም። አሁን አንቱ ለመባል የበቁ የስነጽሑፍ ፣ የትያትርና ድራማ ፣ ወዘተ ባለሙያዎችን ያፈሩት እነዚህ ክበባት እንደ ባለሙያዎቹ አድገው ተመንድገው ቢያንስ በኮሌጅ ደረጃ ላይ መገኘት ነበረባቸው። ያ ግን ሆኖ አልታየም። ለምን?
በአዲስ አበባ ቀበሌዎቹ በወረዳ ቢጨፈለቁና ቢታጠፉም ከፈለጋችሁ ቢታቀፉም በሉት ፤እኔ ግን ታጠፉ የሚለው ይታየኛል። በየቀበሌዎች የወጣት ስብዕና መገንቢያ ማዕከላት ሕንፃዎች ተገንብተዋል። ፊልምና የአውሮፓ ኳስ በክፍያ ከማሳየት የዘለለ አላየሁም ፤ ስማቸው ደስ ይላል፤ የወጣት ስብዕና መገንቢያ ማዕከል የወጣት ስብዕና ግን የሚገነባ ነገር ብዙም የላቸውም። ቤተ መፃሕፍት ቲያትርና ሙዚቃ ስነፅሑፍና ጋዜጠኝነት ወዘተ። ለወጣቱ የሚበጁ ክበባት ማን ፈጃቸው? የሚለው ርዕስ እነ እንቶኔ ክበባቱን ፈጇቸው የምንልበት ምክንያት የለም። ግን ለወጣቱ የሚበጁ ማዕከላት ግን ይበጃጁ መልዕክታችን ነው።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ግንቦት 1/2013