የምርጫ አውድ ! ምርጫ ምርጫ የሚያውድ የሀገር ጠረን። የተፎካካሪ ፓርቲዎችና እና የግል ተወዳዳሪዎች የምረጡኝ ቅስቀሳና የክርክር መድረክ፤ የመራጮች ምዝገባ ፤ የዚህ ወቅት የሀገራችን ምርጫ መገለጫዎች ናቸው።
ዜጎች ሲናፍቁት የኖሩት የዴሞክራሲ ስርአት መሰረት የሚጣልበት ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ሊካሄድ አንድ ወር ገደማ ይቀረዋል። ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ባወጣው የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት በርካታ ተግባሮች ተከናውነው አሁን የምረጡኝ ቅስቀሳና ክርክር የሚደረግበት ወቅት ላይ እንገኛለን።
መንግስት ህዝቡ በዚህ ምርጫ በንቃት በመሳተፍ በዴሞክራሲ ስርአት ግንባታው ላይ አሻራውን እንዲያሳርፍ፣ ከዚህ በኋላ ስልጣን በምርጫ እንጂ በሀይል እንደማይያዝ በተደጋጋሚ እያስገነዘበ ይገኛል። ምርጫውን ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠርም ፈረሱም ሜዳውም ይሄው ብሏል። ምርጫው ፓርቲዎች ከአጃቢነት ወጥተው ራሳቸውን ችለው የሚወዳደሩበት፣ ዜጎች ይበጀኛል የሚሉትን ፓርቲ በነጻነት የሚመርጡበት ነው።
ምርጫው የታለመለትን ግብ እንዲያሳካ መራጮች በቅድሚያ ለመራጭነት የሚያበቃቸውን ካርድ መውሰድ ይኖርባቸዋል። ከመጋቢት 21 ቀን 2013 አንስቶ የመራጮች ሲካሄድ ቆይቶ የተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ ቢጠናቀቅም፣ ተጨማሪ የምዝገባ ጊዜ ተሰጥቶ ዜጎች የምርጫ ካርድ እየወሰዱ ይገኛሉ። በምርጫው 50 ሚሊየን ዜጎች ድምጽ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ወቅቱ የፓለቲካ ፓርቲዎች የምረጡኝ ቅስቀሳ የሚያደርጉበትም ነው። የአዲስ አበባ አደባባዮችና ጎዳናዎች በእርግጥም ምርጫ ምርጫ እያሉ ናቸው። በፓርቲዎች ቅስቀሳ መልእክቶችና በእጩዎቻቸው ምስሎች ደምቀዋል፤ የሐገሪቱን ሰንደቅ አላማ ፣ አርማቸውን፣ የምርጫ ምልክታቸውን ይዘው በልዩ ልዩ ተሽከርካሪዎች ፣ በሰልፍ በመሆን በግዙፍ ድምጽ ማጉያዎች በመታገዝ ብትመርጡን ይህን እናደርጋለን፤ ፕሮግራማችን ስትራቴጂያችን ይህን ይመስላል እያሉ የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን አጠናክረዋል።
መገናኛ ብዙሃንንም በመጠቀም በተመደበላቸው የአየር ሰአትና የጋዜጣ አምድ ላይ ቅስቀሳቸውን እያካሄዱ ይገኛሉ። ከህዝብ ጋር መገናኘት ባለባቸው በዚህ ወቅት በተደለደለው የአየር ሰአትና የጋዜጣ አምድ በሚገባ እየተጠቀሙ ነው ወይ ተብሎ ሊጠየቅ ይችላል። መልሱ አይደለም የሚል ነው። የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎችም ይህን ሲያረጋግጡ ነው የቆዩት።
ይህ እንዲታረም የሚዲያ ተቋማቱ እያስገነዘቡ ይገኛሉ። መገናኛ ብዙሃኑ ፓርቲዎቹ እድሉን እንዲጠቀሙበት ጭምር እየወተወቱ ናቸው። ይህን እድል ሳይጠቀሙ ሁዋላ ላይ መገናኛ ብዙሃን ተጠያቂ ማድረግ አይቻልም፤ ተቋማቱም ፓርቲዎቹ ያልተጠቀሙባቸውን አምዶች በስማቸው በመመዝገብ ክፍቱን እያወጡ ናቸው። መገናኛ ብዙሃኑ ውርድ ከራሳችን እያሉ ናቸው። ፓርቲዎች ሆይ የአየር ሰአትና አምድ ተይዞላችሁ አለመጠቀም ለጉዞ ትኬት ተቆርጦላችሁ እንደ መቅረት ነው የሚቆጠረው።
እድሉን በአግባቡ ወይም ፈጽሞ ያልተጠቀማችሁ ፓርቲዎች ፣በዚህ በውድድር ላይ በተመሰረተ ምርጫ ይህን እድል ባለመጠቀማችሁ ሀገራችሁ ፣ዜጎች፣ ደጋፊዎቻችሁ፣ አባሎቻችሁ ሊቀርባቸው የሚችለውን አስቡ። ለምርጫው ዝግጁ ከሆናችሁ ጽሁፎቻችሁን አስቀድማችሁ ማዘጋጀትና በወቅቱ ማቅረብ ይጠብቅባችሁዋል።
የቅስቀሳ ጽሁፍ ማቅረብ አለመቻል የሀሳብ ድህነት መኖሩን እንዲሁም ለምርጫው በሚገባ አለመዘጋጀትንም ያመለክታል። አሁንም በቀሪው ጊዜ በመጠቀም ጽሁፎቻችሁን እያዘጋጃችሁ አምዶቹንና የአየር ሰአታቱን ተጠቀሙ።
በቴሌቪዥን በሚካሄደው የፓርቲዎች ክርክርም ፓርቲዎቹ በአንድ ርእሰ ጉዳይ ላይ እርስ በርሳቸው እየተከራከሩ ይገኛሉ። ይህን አይነቱን ክርክር በምርጫ 97 ተከታትለነዋል። ከምርጫ በሁዋላ ያ ሁሉ እንዳይሆን ሆነ እንጂ ያ ዘመን ሀገራችን የዴሞክራሲ ጠረን ማወድ የጀመረበት ነበር።
የዘንድሮውን ክርክር የተከታተሉ ወገኖች በክርክሩ ሀሳብን ከማስተዋወቅና ከማብራራት ይልቅ የሌሎችን ሀሳብ ማጣጣል በብዛት ይስተዋላል። አንዳንድ ፓርቲዎች የሀሳብ ድህነት ታይቶባቸዋል ሲሉ ይጠቁማሉ።
የምርጫ ክርክሩን እኔም በተወሰነ መልኩ እየተከታተልኩ ነው። ጥሩ ጥሩ ሀሳቦች ሲነሱ አድምጫለሁ። ክርክሩ በራሱ የምር ክርክር ነው፤ የማስመሰል ነገር አላየሁበትም። ይህ በራሱ ትልቅ ነገር ነው። ያድጋል።
ማን ምን እንደሆነም ለመገንዘብ ክርክሩን ጥሩ መሳሪያ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ክርክሩን የተከታተሉ እንዳሉት ሁሉ እኔም የሀሳብ ድህነት ያለባቸውን ፓርቲዎች አስተውያለሁ። የሌሎችን ሀሳብ ማጣጣል ላይ ማተኮር እንዳለም ተረድቻለሁ።
የክርክር መንፈሱ የራስን ሀሳብ ሊያስረዱ የሚችሉ ሀሳቦችን በመደርደር ማሳመን ነው። ሌላው የሚያቀርበው ሀሳብ ትክክል ከሆነ መደገፍ፣ ትክክል ካልሆነም በማስረጃ ትክክል አለመሆኑን ማስገንዘብ ነው። ይህ ጨዋነት የተሞላበት የክርክር ሂደት ነው።
ከዚህ አኳያ የኛ ፓርቲዎች በክርክሩ በሚያደርጉት ምልልስ አንዱ አንዱን ገላልጦ ማስቀመጡ ጥሩ ሆኖ አማራጭ ሃሳብ ማቅረብ ላይ ግን ብዙ ርቀት ሲኬድ አይታይም። አንዳንድ ፓርቲዎች የራሳቸውን ሀሳብ ለማንጸባረቅ ስራ ትኩረት ሳይሰጡ የሌላውን ፓርቲ ሲያጣጥሉ የክርክሩ ጊዜ ሲያልቅባቸው ይታያል። ይሄ መታረም አለበት።
በአንጻሩ በፓርቲዎች ነቆራ የተበሳጨ ፓርቲ ተወካይ የተናደደ በሚያስመስለው መልኩ ተፎካካሪ ፓርቲዎቹን ዘንድሮም ምንም አይነት ሀሳብ ይዛችሁ አልመጣችሁም ብሎ ሲናገር ሰምቻለሁ። ይህ መልስ በመሰረቱ ባለፉት አመታት ምን ክርክር ነበርና ነው ወደዚህ መደምደሚያ የተሄደው የሚል ሀሳብ ያጭራል።
ቢያንስ በክርክር መድረኩ መገኘትን እንደ ትልቅ ዋጋ መቁጠር ይገባል። ሀሳቡ ተሰሚነት እንዲኖረው ማብራሪያ ቢሰጥ ነበር የሚሻለው። የማይቀበሉት አይነት ከሆነም ለህዝብ መተው ነው የሚሻለው ።
የፓርቲዎቹን ስም መጥቀሱ እምብዛም አስፈላጊ ስላልመሰለኝ ትቼዋለሁ፤ነገር ግን ፓርቲዎቹ ሌሎች ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ከማብጠልጠልና ከመተቸት፤ ይልቅ በራሳቸው ዓላማና ሀሳብ ዙሪያ ባጠነጠኑ ጉዳዮች ላይ ቢያተኩሩ ይመረጣል የሚል እምነት አለኝ።
በቴሌቪዥን የማስተዋወቂያ ፕሮግራማቸው ሰአታቸውን የሚያባክኑት የሌሎችን ፓርቲዎች ፕሮግራም በመተቸት ነው። የራሳቸውን ፕሮግራም በቅጡ ሳያሳውቁ ሰአታቸውን ጨርሰው ሲሰናበቱም ተጨማሪ መረጃዎችን ከሰነዶቻችን ተመልከቱ የሚሉ አጋጥመውኛል።
በእኛ ሀገር መራጮች ንቃተ ኅሊና ከሰነዶቻችን ተመልከቱ ማለት ለኔ ሰነድ የለንም እንደ ማለት ይመስለኛል። እንኳን መራጮች እኔም ብዕረኛው የፓርቲዎችን ሰነድ ለማግኘት መንከራተት የለብኝም። በከተማ የሚኖሩ የፓርቲዎቹን ሰነድ ያገኛሉ ብንል በገጠርና ገጠር ቀመስ ከተሞች ያሉ እንዴት በቀላሉ ሰነዱንስ ያገኛሉ?
አንድ ጓደኛዬ ከክርክራቸው የተመቸኝ ምልልሳቸው ነው ሲል የነገረኝ ታወሰኝ። እውነቱን ነው። አንዱ የሌላውን ሲያጣጥል የሚገልጽበት መንገድ ክርክሩን ትታችሁ አትሂዱ አትሂዱ ያሰኛል። የቋንቋ አጠቃቀማቸው ከባድ ነው። መሰዳደብ እኮ ነው የሚቀራቸው ነው ያለኝ። ከሀሳቡ ይልቅ ምልልስ የሚያደርጉበት መንገድ የተመቻቸው ብዙ ናቸው።
በመሰረቱ የሁላችንንም ቀልብ ሊይዝ የሚገባው የሚያቀርቡት ሀሳብ ነበር። እዚህ ላይ ክፍተት አለ። ይህን አካሄድ መቀየር ይኖርበታል፤ አሁንም ጊዜው አለ። የክርክር ባህል ተክሎ ለመሄድም ስለሚጠቀም ይህን ጤነኛ መንገድ ለማጎልበት ፓርቲዎች ብዙ መስራት አለባችሁ።
አሁን በአብዛኛው የሚታየው ግን ክርክር ወይስ ንቁቁር የሚያሰኝ ነው። ፓርቲዎች ጥሩ ሀሳብ ካላቸው በዚህ ቅስቀሳ ህዝቡን መሳብ ይችላሉ። ጠንካራ መንግስት ለመመስረት የመስሪያው ጊዜ አሁን ነው። ክርክሩን ለዚህ ታላቅ አላማ ተጠቀሙበት!
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 24/2013