ውቤ ከልደታ
ሰላም የአዲስ ዘመን ቤተሰቦች፤ እንደምን ሰነበታችሁ፣ መቼም በአገራችን ከሳምንት ሳምንት አዳዲስ አጀንዳ አልጠፋ ካለ ሰነባብቷል። ለመጪው ሳምንት ደግሞ ምን አዲስ አጀንዳ ተዘጋጅቶልን ይሆን የሚል ጥያቄ ብዙዎቻችንን ማሳሰብ ከጀመረ ሰነባበተ። ጭር ሲል የማይወዱት ጠላቶቻችን በየጊዜው አዳዲስ አጀንዳዎችን እያዘጋጁ ይሰጡናል፤ እኛም እንደወረደ እየወሰድን እናባዛለን፤ እናሰራጫለን።
እንዲያው ግን ጎበዝ እኔ ያልገባኝ አንድ ጥያቄ አለ፤ ለመሆኑ በአገራችን በየጊዜው የሚከሰተው ችግር እውን አገርን ወደፊት ለማስኬድ ይጠቅማል ብለው የሚያስቡ ሰዎች ናቸው እንዲህ አዳዲስ አጀንዳዎችን የሚያቀብሉን? ከእነዚህ አጀንዳዎችና ጥቃቶች በስተጀርባስ ያለው ድብቁ ኃይል መቼ ይሆን ራሱን ወይም ጊዜ የሚያጋልጠው? ዜጎቻችንስ ሰላማዊ እንቅልፍ የሚተኙት መቼ ይሆን? ኢትዮጵያዊያንስ የቀደመውን የአንድነትና የአብሮነት ባህል አትንኩብኝ ማለትን ለምን አልቻልንም? እኔ የአገራችንን ችግሮች ባሰብኩ ቁጥር “የእንቁራሪቷ ታሪክ” ውልብ ይልብኛል። መቼም ስለእንቁራሪቷ ብዙዎቻችሁ ታውቃላችሁ ብዬ ባስብም ላስታውሳችሁ።
በአንድ ወቅት አንዲት እንቁራሪት በኩሬ ውስጥ ሆና እሷ ከምትገኝበት ቅርብ ርቀት ላይ የሚገኘው ጫካ መቃጠሉን ሰማች። በዚህም በጣም ደነገጠች። ከዚህ በኋላ ሰዎች ያንን እሳት ወደእሷ ከመቅረቡ በፊት ቶሎ እንዲያጠፉት መማፀን ጀመረች። ይህንን የተመለከቱ ሌሎች ከውሃ ውጭ የሚኖሩ እንስሳት ግን ይህች ምን ሆና ነው እንዲህ የምትሆነው፤ ብለው ተናደዱባት። ከዚያም ቀረብ ብለው ጠየቋት። ለመሆኑ አንቺ እንዲህ የምትፈሪው ምን ሆነሽ ነው። እኛ እንኳን ጫካ ውስጥ ያለነው እሳቱ ቢመጣ ይጎዳናል ብለን ነው። አንቺ ግን ውሃ ውስጥ ሆነሽ እንዴት ትፈሪያለሽ? ብለው ተሳለቁባት። እሷ ግን አርቆ አሳቢ ነበረችና አትሳሳቱ አለቻቸው፤ እናንተ ያያችሁት የላይ የላዩን ብቻ ነው፤ ይህ እሳት ጠንክሮ ከመጣ ሰዎች እሳቱን ለማጥፋት ውሃ ከዚህ መውሰዳቸው አይቀርም። ያኔ ደግሞ እኔንም አብረው ጨልፈው ሊወስዱኝ ይችላሉ። ባይወስዱኝ እንኳ ውሃው ተወስዶ እሳቱ መጥፋት ካልቻለ እኔን ባዶ ሜዳ ላይ ነው የሚያገኘኝ፤ ስለዚህ ጥፋትን ከመድረሱ በፊት መከላከል ይገባል ስትል መልሳላቸዋለች።
አዎ፣ አጉል ፍርሐት ተገቢ ባይሆንም ሊከሰቱ የሚችሉ ችግሮችን ግን ቀድሞ መገመትና ከዚያ ራስን መከላከል የብልሆች አስተሳሰብ ነው። ዛሬ በአገራችን ጉዳይ ላይ ጫካው ሲቃጠል ቁጭ ብሎ የማየት ነገር በስፋት ይስተዋላል። አንዳንዶቻችን የዚህ ምሳሌ ዓይነት ነን። ጥቂቶች አገር ለማፍረስ ያለ የሌለ ኃይላቸውን ተጠቅመው ሲሯሯጡ እኛም ልክ እንደ አሯሯጭ አብረናቸው ከኋላ ስንሮጥ እንታያለን። ይህንን ስል ግን ሁሉንም ማለቴ
አለመሆኑን ልብ በሉልኝ፤ እኔ እያልኩ ያለሁት ችግሮች ሲከሰቱ በተለይ በማህበራዊ ሚዲያ ጥፋተኞችን ተከትለው ችግር ለሚያባዙት አልያም ለሚያራግቡት ነው።
አንዳንድ ጊዜ እኛ ኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲ አልገዛን አለ እንዴ የሚል ጥያቄን የሚያጭሩ ሃሳቦች ወደ አዕምሮዬ ይመጣሉ። ይህንን ስል ያለምክንያት እንዳይመስላችሁ። ከቅርብ ጊዜ ከነበረኝ ትዝታ ጋር እንኳ አነጻፅሬ ከምሰማውና ከማየው ነገር ዴሞክራሲን የሚፃረሩ ድርጊቶችን ስመለከት የዴሞክራሲ ጭላንጭል ለማጥፋት በዚህች አገር በርካታ ኃይሎች መሰለፋቸውን ስለምገነዘብ ነው። እስኪ ጥቂት ሃሳቦችን ላንሳ።
ባለፉት 30 ዓመታት አምስት ያህል ምርጫዎች በአገራችን ተካሂደዋል። እነዚያ ምርጫዎች ምን ዓይነት ምርጫዎች እንደነበሩ ሁላችንም ስለምናውቅ እዚያ ውስጥ አልገባም። ነገር ግን ዘንድሮ መንግሥት በተቻለ መጠን በሮችን ሁሉ ክፍት በማድረግ ዴሞክራሲዊ ምርጫ ለማካሄድ እየሠራ መሆኑን በተደጋጋሚ አስታውቋል። ለዚህም ቢያንስ በገለልተኝነታቸው የምናውቃቸውና በቀላሉ እጃቸው የማይጠመዘዙ የምርጫ ቦርድ አስፈጻሚ አካላትን መድቦ እየሠራ ነው። እስከአሁን ድረስ ባለው ሁኔታም በምንም መመዘኛ ዘንድሮ የሚካሄደው ምርጫ ከዚህ ቀደም ከነበሩት ምርጫዎች ይልቅ የተበላሸ ይሆናል የሚል ግምት ለመውሰድ የሚስችል አሳማኝ ምክንያት የለም። ይህ በሆነበት ሁኔታ ግን ይህ ምርጫ አይመጥነንም በማለት ከዚህ ምርጫ የወጡ ፓርቲዎች አሉ።
ምናልባት እነሱ የለመዱት በአፈና ስርዓት ውስጥ ምርጫ መወዳደር ልምድ ስለሆነባቸው ዴሞክራሲያዊ ምርጫ አውድ ከብዷቸው ከሆነ አንድ ነገር ነው፤ ነገር ግን ምርጫውን በዚህ መልኩ ስም ሰጥቶ መውጣት ከወዲሁ የመሸነፍ ምልክት ነው እላለሁ።
እነዚህ ሰዎች ግን ምርጫው ባይካሄድ “ይህ አፋኝ መንግሥት ነው፤ ህጋዊ አይደለም” ለማለት የሚቀድማቸው የለም። በሌላ በኩል ኑና ወደ ምርጫ ግቡ ሲባሉ ደግሞ በዚህ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት የላቸውም። ምክንያም ለመሳተፍና አገር ለመምራት የሚያስችል አንዳችም አቅም የላቸውምና። አሁን አሁን ምርጫው የማይቀር መሆኑን ሲረዱ ደግሞ ምርጫውን ለማደናቀፍ የተለያዩ የማተራመስ ሥራዎችን ጀምረዋል። አሁን ሰሞኑን ምርጫው በተቃረበበት ወቅት እዚህም እዚያም የሚከሰቱ ችግሮች በአገራችን ግጭት ለመፍጠርና ምርጫውን ለማደናቀፍ እንደሆነ መረዳት ተመራማሪ መሆንን አይጠይቅም። ለዚህ ደግሞ መንግሥት ፋታ አጥቶ ትኩረቱን ሁሉ በዚህ ላይ እንዲያደርግና ሌሎች የልማት ሥራዎችን በተለይ የታላቁን የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ሥራ ችላ እንዲል ለማድረግ የሚሞክሩ የውጭ ኃይሎችም የራሳቸውን ድጋፍ ከኋላ ያደርጋሉ፡፤
በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ አንዳንድ መሰረታቸውን ውጭ ያደረጉ ሚዲያዎችና ማህበራዊ ሚዲያዎች እሳቱን በመቆስቆስ ህዝብን ከህዝብ የማጋጨት ሥራቸውን በስፋት ይሠራሉ። ለምሳሌ የሰሞኑ የአጣዬ፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እና በጎንደር ጭልጋ አካባቢ የተፈፀሙ ጥቃቶች ዝም ብለው የተከሰቱ እንዳልሆኑ ግልጽ ነው። እነዚህን ጥቃቶች የሚፈፅም ኃይል የመኖሩን ያህል ደግሞ ከዚህ ጎን ለጎን በማህበራዊ ሚዲያ ይህንን በማራገብና ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨት የሚሠራ ኃይል አለ።
ለአብነት ያህል ሰሞኑን በተለያዩ አካባቢዎች የሚፈጸመውን ዘር ተኮር ጥቃት በመቃወምና በማውገዝ በአማራ ክልል በተለያዩ ከተሞች ሰልፎች ተካሂደዋል። በተካሄዱት ሰልፎች ውስን ቦታዎች አላስፈላጊ ሁከት ለመፍጠርና ህዝብን ከህዝብ ለግጭት የሚዳርጉ መፈክሮችን በማዘጋጀት ለጥፋት የሚሠሩም አሉ። ግርግር ለሌባ ይመቻል እንዲሉ የሚጮኸው ሁሉ ለህዝብ ተቆርቁሮ ብቻ ነው ማለት አይደለም። አንዳንዱ የሚጮኸው የቁራ ጩኸትም ነው።
ስለዚህ በዚህ ወቅት ጠንቃቃ መሆን ከእያዳንዱ ህብረተሰብ የሚጠበቅ ተግባር ነው። ችግሮች ሲፈጠሩ አብሮ ከማራገብ ይልቅ ችግሩ ወደፊት ደግሞ እንዳይፈጠ መከላከል ላይ ማተኮሩ ይጠቅማል። ከዚህ ውጪ ግን ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል ዓይነት አንዳንዱ እሳት እየለኮሰ መልሶ በመጮህ ግጭት ለመፍጠር ይንቀሳቀሳልና ጥንቃቄ ሊለየን አይገባም።
አገራችንን ወደፊት ለማሻገርና ለልጆቻችን የተሻለች አገር ለማድረግ ዛሬን በትዕግስት ማለፍ የግድ ይላል። ትዕግስት አንዳንድ ሰው መሸነፍ ይመስለዋል። ዛሬን በትዕግስት ለማሳለፍና ለነገ የተሻለች አገር ለመገንባት ነው። ከሁሉም በላይ ዕርስበርስ በመቻቻልና በመከባበር ስለነገ ማሰብ ከሁላችንም ይጠበቃል።
ከዚህ ውጪ ግን ኃላፊነት በጎደለው መልኩ ሁሉም እየተነሳ ጦር የሚሰብቅ ከሆነ አሸናፊ የሚሆነው የጥፋት ድግሱን የሚደግሰው ኃይል ብቻ ነው። ይህ የጥፋት ኃይል አሁን ያዘጋጀው ድግስ በአግባቡ እንዲበላለት ቢፌውን አቅርቦልናል፤ ያንን ቢፌ የመብላትና ያለመብላት ደግሞ የኛ ፈንታ ነው።
ዛሬ የመን፣ ሶርያ፣ ኢራቅ፣ ወዘተ የመሳሰሉ አገራት ዜጎች በብዙ መልኩ ከእኛ የተሸለ ህይወት ነበራቸው፤ ልጆቻቸው የነገ ተስፋ ነበራቸው። እጆቻቸው ከመለመን ይልቅ ለመስጠት ቅርብ ነበሩ። ዛሬ ግን በየመንገዱ እጃቸውን ዘርግተው ስናይ ሊዘገንነንና ከዚህ ለመራቅ ወደ ህሊናችን የምንመለስበትን መንገድ መፍጠር አለብን። የሰው ልጅ ለማደግ፤ ሀብት ለማፍራት፣ የተሻለ ለመኖር የሚያስችለውን ነገር ለመፍጠር ረዘም ያለ ጊዜ ሊፈጅበት ይችላል፤ ለጥፋት ግን የደቂቃዎች ጊዜ ብቻ በቂ ነውና ቆም ብለን እናስብ፤ ዛሬም ፣ነገም፣ ቀንም፣ ሌሊትም ከዚህ ችግር የምንወጣበትን መንገድ እንፈልግ።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 18/2013