የልቤ ደርሶ
ሀገራችንን ለበርካታ ዓመታት ሲመራ የነበረው ኢህአዴግ ብዙዎች እንደሚስማሙበት የሚያወጣቸው ስትራቴጂዎች ፖሊሲዎች እንዲሁም መመሪያዎች ለፍጹምነት የቀረቡ ናቸው። “ፖለቲከኛውም” “ምሁሩም” በዚህ ይስማማሉ።
ይሄ ነገር አይሆንም፤ መሬት ላይ አያርፍም ቢባልም የወቅቱ መንግስት ለመቀበል ፈቃደኛ አልነበረም፤ በተለይ ሀሳቡ ከሚጠላቸው ቡድኖች ወይም የህብረተሰብ ክፍሎች የፈለቀ ከሆነ ለምን መንግስተ ሰማያት የሚያስገባ ሀሳብ አይሆንም አይቀበለውም።
በምትኩ ይህን ሀሳብ የነሱ ቡድኖችንና ግለሰቦችን ሁሉ የማርያም ጠላት ያደርግ ነበር። የሚገርመው ግን ይህን ያጣጣለውን ሀሳብ በሌላ ጊዜ የኔ ሀሳብ ብሎ ይዞት ይመጣል።
በዚያ መንግስት ዘመን የበለጸጉ አገራትን ተሞክሮዎች ከአገር በቀል እውቀቶች ጋር በማዛመድ ተሰሩ ከሚባሉ ንድፎች (ዕቅዶች) መካከል ብዙዎቹ መልካምነታቸው ወረቀት ላይ ብቻ ቀርቷል። የንድፉ ቅንጣት የምታህል እንኳ መሬት ላይ ያልታየችበት ሁኔታ ጥቂት አይደለም።
አስፍቶ ማሰብና ማቀድ ጥሩ ነው። ትንሽ አቅዶና ፈጽሞ ከመኩራራት የሚያጠግብ እቅድ አዘጋጅቶ ለመፈጸም መረባረብ ጥሩ ነው። በሀገራችን በአንደኛውና በሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የተለጠጠ የሚባል ነበር። የሀገራችን እቅድ ምን ያህል ችግር ያለበት እንደ ነበር ከዚህ እቅድ ብቻ መገንዘብ ይቻላል።
ለዚህም ፓርቲው “በጥልቅ ታደስኩ” ባለበት ወቅት ከአነሳቸው ክፍተቶች መካከል የቀረጽኳቸው ፖሊሲዎች እና ስትራቴጂዎች መልካም ቢሆኑም አፈጻጸማቸው ግን ችግር አለበት ሲል የገለጸው። ወዳጄ የአፈጻጸም ችግር ካለ የነደፍከው መሬት ላይ እንዳታሰበው ካልወረደ በቃ ምንም “የዳቦ ስም” አያስፈልገውም ስራ አልተሰራም ማለት ነው።
የቀድሞውን ክፍተት እንደ መነሻ አነሳሁ እንጂ አሁንም ቢሆን እንዲህ አይነቱ ችግር በተለያዩ መንገዶች ይስተዋላል። በአገሪቱ የተለያዩ አቅጣጫዎች ይበል የሚያሰኙ የልማት ስራዎች ይታያሉ። ታዲያ እነዚህ የልማት ስራዎች ከመተግበራቸው በፊት በተሰራላቸው ንድፍ መሰረት ነው የተሰሩት ሲባል ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ይሆናል ነገሩ። በንድፍ ያየነው ገነት የመሰለ ስፍራ መሬት ወርዶ አናየውም።
የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት በሚል ሲካሄድ የቆየውን የመንግስት የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክትን ለእዚህ በአብነት መጥቀስ ይቻላል። የኮንደሚኒየም ልማት ሊጀመር አካባቢ ይሁን ከዚያ ወዲህ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት የሚመለከተው አካል በተመረጡ የቤቶች ልማት አካባቢዎች ለሚሰሩ ህንጻዎች ዲዛይን እንዲቀርብ ውድድር አውጥቶ ነበር።
የቤቶቹ ብሎኮች በአብዛኛው የተወሰኑ ቢሆንም (ማለትም የቤቶች አይነት ቁጥርና የፎቅ ብዛትና የመሳሰሉት) የወጣው ውድድር ለቤቶች ዲዛይን፣ ለብሎኮች አቀማመጥና ክፍት የሚተው ቦታዎችን ያካትታል። ዲዛይኖችም ተመርጠው እንደነበር አስታውሳለሁ።
የኮንደሚኒየም ቤቶችን ስመለከታቸውና ያንን ዲዛይን ሳስታውስ ያ ሁሉ ድካም ለምን ነበር ስል እጠይቃለሁ። አሸናፊዎቹ ዲዛይኖች እና መሬት ላይ ያረፈው ግንባታ ፈጽሞ የማይገኛኙ ናቸው። አስታውሳለሁ ህንጻዎቹ በሚሰሩበት ቦታ የተለጠፈው ንድፍ የልጆች መጫወቻ የአረንጓዴ ቦታ ያለው ሲሆን፣ መሬት ላይ የወረደው ግን ፈፅሞ የማይገናኝ ነው።
የሪል ስቴት አልሚዎች ዘንድም ተመሳሳይ ችግር ይታያል። የሀገራችን የሪል ስቴት አልሚዎች በሀገራችን ያልነበረ የቤት ልማት ማምጣታቸውና መግዛት የሚችለውንማህበረሰብ መሸከም መቻላቸው ሊያስመሰግናቸው ይገባል። በዚህ ልማት የተገነቡ መንደሮች ጥቂት አይደሉም። በርካታ ዜጎቻችን የዘመናዊ መኖሪያ ቤት ባለቤት ሆነዋል።
አልሚዎቹ ይዘውት በተነሱት ዲዛይን መሰረት የከተማዋንም የነዋሪውንም ፍላጎት የሚያሟላ ስራ ሰርተዋል ወይ ሲባል ግን መልሱ አልሰሩም የሚል ይሆናል። በዲዛይን በኩል ጥሩ ስም አላቸው ብዬ አልወስድም።
እንደሚታወቀው ሪል ስቴት በቀጥታ ትርጉሙ የጋራ መኖሪያ መንደር ወይም ትንሽዬ ከተማ እንደ ማለት ነው። በሳይንሳዊ አገባቡ ደግሞ መሬት ላይ ያረፈ ንብረት ማለት ነው። ይህ መሬት ላይ ያረፈ ንብረት ማንኛውንም አገልግሎት መስጠት የሚችል ሕንፃ ሊሆን ይችላል።
በአገራችን ሕጎች የተሰጠው ብያኔ ደግሞ በራስ ይዞታ (መሬት) ላይ ወይም በኪራይ (ሊዝ) ይዞታ ላይ የሚለማን ቤት የሚመለከት ሲሆን፣ በህጎቹ ከአንድ ሺሕ ቤቶች በላይ ለማቅረብ የሚፈልግ አልሚ “ግዙፍ ሪል ስቴት” ተብሎ ልዩ ማበረታቻና ምቹ ሁኔታዎች እንዲፈጠሩለት እንደሚደረግ ይደነግጋሉ።
ይህን እውነታ እንዳለ ሆኖ መንግስት በሪል ስቴት ዘርፉ ለተሰማሩ አልሚዎች የሚገባውን በህግ የተደነገገውን ካቀረበ በኋላ አልሚዎቹ ከግንባታው በፊት እና በግንባታ ላይ እያሉ የሚገነቧቸውን ቤቶች እና ሱቆች ለማሻሻጥ ማስታወቂያ ያሰራሉ። እነዚህ አልሚዎች ልንገነባ ያሰብነው ትንሽዬ ከተማ ንድፍ ብለው በማስታወቂያ ሲያሳዩ ለተመለተከተ ወደ ሀገራችን ታምር ሊመጣ መሆኑን በማሰብ ይደነቃል። ይህ ንድፍ መሬት ላይ ወርዶ ለማየት የማይጓጓም የለም።
ግንባታቸው የተጠናቀቀ ቤቶችና መንደሮች ሁኔታ ሲታይ ግን በዲዛይኑ ላይ ያለውና መሬት ላይ ያለው ጨርሶ የተለያየ ሆኖ ይገኛል። እስቲ ያ መንደር የት ደረሰ ብሎ አካባቢው ላይ የተገኘ ሰው የሚመለከተውን ለማመን ተቸግሮ “የታል ንድፉ” ብሎ ሊጠይቅም ይችላል ።
በሀገራችን አንጋፋ የሚባል አንድ የሪል ስቴት አልሚ በቀጣይ ስለሚገነባው መንደር በቴሌቪዥን ሲያስተዋውቅ ሀገራችን እነ ሲንጋፓርን ልትሆን ነው ያላለ አልነበረም። ይህን ማስታወቂያ ሲያስነግር የነበረ ድርጅት ያን መንደር አይደለም ወጣ ያለ መንደርም እስከ አሁን አላሳየም።
ታዲያ ይህን ችግር ለመፍታት ምን መከናወን ይኖርበታል? ንድፍ አውጪው እና ተግባሪው መናበብ አለባቸው፤ ሁለቱ ካልተናበቡ ዲዛይንና ትግበራ ሊዋደዱ አይችሉም። እነዚህ ሁለት አካላት ማለትም ንድፍ አውጪው እና ተግባሪው ሊናበቡ ይገባል።
የገንዘብ፣ የባለሙያ አቅምን፣ የግንባታ ስፍራ ተፈጥሯዋዊ ባህሪን፣ ግምት ውስጥ ያስገባ ንድፍ አለማቅረብ ሌላው ችግር ነው። ንድፍ አውጪዎች ባለሙያዎች ናቸውና ራቅ አርገው አስበው ንድፉን ሊሰሩ ይችላሉ። የውጪ ሀገር ንድፎችን ገልብጠው ያቀርቡ ይሆናል።
ተቋራጮቻችንና ባለሙያዎች ደግሞ ይህን መሬት ላይ ለማውረድ የሚያስችል የአቅም ውስንነት ሊኖርባቸው ይችላል። ከዚህ የተነሳ ንድፉ የማይተገበር ሆኖ ሊቀር ይችላል። የፋይናንስ ችግር ደግሞ አለ። ባለቤት አቅሙን ግምት ውስጥ ሳያስገባ በውጭ ሀገር ያየውን ዲዛይን ስሩልኝ እያለ ግንባታ ውስጥ የሚገባበት ሁኔታ እንዳለም ይገለጻል። ወደ ግንባታ መግባት ሲታሰብ በየትኛውም መልኩ ያለውን የአቅም ውስንነት መፍታት ያስፈልጋል።
ስለዚህም ግንባታውን የሚገነባው ድርጅት ሀላፊነቱን ወስዶ ስራውን ከሰራ በኋላ ግንባታውን አጠናቅቄያለሁ ብሎ ሲያስረክብ ከተነደፈው ንድፍ ጋር አመሳክሮ መረከብ ተገቢ ነው። ከዚያ ውጭ ከሆነ ግን “የታለ ንድፉ!” ብሎ መጠየቅ ይገባል። አለበለዚያ ግን ያላስፈላጊ ወጪ ይዳርጉናል።
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 17/2013