ጌትነት ምህረቴ
የዛሬው ዘመን ላይ መጠጦች፣ አልባሳት፣ የታሸጉ ምግቦችና ሌሎች የፍጆታና የመጠቀሚያ ዕቃዎች የሚመረቱት የኑሯችን የህልውና አካል በሆነው የኤሌክትሪክ ሀይል ነው፡፡ በአገራችን የኤሌክትሪክ ሀይል ለብርሃን ብቻ ሳይሆን ለምግብ ማብሰያ፣ ለውበታችን መጠበቂያ፣ ልብሶቻችንን ለማምረትና ለማዘጋጀት ጭምር ነው የምንጠቀምበት፡፡ ይህም እውነት የኤሌክትሪክ ሀይል አስፈላጊነት በሰዎች ህይወት ምን ያህል ዘልቆ እንደገባ አጉልቶ ያሳየናል፡፡
ኤሌክትሪክ ሀይል ለአንድ አገር አንቀሳቃሽ ሞተር ስለመሆኑ ዕለት ከዕለት ስራችን የምንገነዘበው ነው፡፡ ኢትዮጵያ ብዙ ኤሌክትሪክ ሀይል የሚያመነጩ በርካታ ወንዞች ቢኖራትም ባላት ውስን ሀብት ምክንያት በወጉ አልምታ መጠቀም አልተቻላትም፡፡‹‹የአባይን ልጅ ውሃ ጠማው›› እንዲሉ በኤሌክትሪክ ሀይል አቅርቦት ችግር ምክንያት በመኖሪያ ቤቶችና ፋብሪካዎች የኤሌክትሪክ ሀይል የሚቆራረጥበት ሁኔታ እየተለመደ መጥቷል፡ ፡ይህም በህብረተሰቡ ህይወት ላይ የሚፈጠረውን ጫና ቀላል አያደርገውም፡፡በኢኮኖሚውም ቢሆን ሰፊ የሚባል አሉታዊ ሚና አለው፡፡
ኢትዮጵያ የከተሞችን መስፋፋትና የኢንዱስትሪዎችን መበራከት ተከትሎ የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎቷ በእጅጉ እየጨመረ መጥቷል። መንግስትም ይህን በመገንዘብ የኤሌክትሪክ ኃይል እጥረት ለኢኮኖሚው ቀጣይ ዕድገት ፈተና እንዳይሆን አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማሟላት ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፤ መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ ከተጣለበት ዕለት ጀምሮም ለፕሮጀክቱ ልዩ ትኩረት በመስጠት ግንባታውን በማፋጠን ላይ ይገኛል፡፡
ለዚህም ነው ህዝቡ አባይ ተገድቦ ኤሌክትሪክ ማመንጨቱን ሲረዳ ከችግርና ድህነት እንወጣለን በሚል በሁለንተናዊ ድጋፍ ቁርጠኝነቱን ያሳየው፡ ፡ በተግባራዊ እንቅስቃሴውም ለግንባታው ሂደት ከፍተኛ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። ይህ ህዝባዊ ድጋፍና ንቅናቄም እስከ ዛሬ ድረስ በጥንካሬ ቀጥሏል፡፡ ህዝቡ ይህን ድጋፍ ባለፉት አስር ዓመታት በተግባር በማሳየት ለግንባታው የሚውል ቦንድ በመግዛት፣ደመወዙን በመስጠትና በሀሳብ በተጠናከረ ድጋፍ አጋርነቱን አሳይቷል፡፡እስከዛሬም ለግድቡ ግንባታ እያንዳንዱ ዜጋ የሚችለውን ያህል አስተዋፅኦ እያደረገ ነው።ቦንድ በመግዛት፣ ስጦታ በማበርከት፣ ደመወዙን በመለገስና በሌሎችም ድጋፉን ቀጥሏል።
በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውለድ ኢትዮጵያውያንም እንዲሁ ቦንድ በመግዛት ለግድቡ ግንባታ የበኩላቸውን ድጋፍ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡
አርሶ አደሩም ቦንድ በመግዛት ከሚያደርገው አስተዋፅኦ ጎን ለጎን ወደፊት ግድቡ ሲጠናቀቅ በደለል እንዳይሞላ ከወዲሁ የተጠናከረ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራን በየዓመቱ እያከናወነ ነው።በመጪው ክረምትም በአገር አቀፍ ደረጃ ሶስት ቢሊዮን ችግኞች የሚተከሉ ሲሆን የአባይ ተፋሰስ አካባቢዎችንም የሚያካትት እንደሆነ መረጃዎች ያረጋግጣሉ፡፡
ህዝቡ ከገጠር እስከ ከተማ፤ አዋቂና ህፃን፤ ባለሀብትና ድሀ ሳይል ድጋፉን እየሰጠ ይገኛል። ግድቡም አገሪቷን ከድህነት የሚያፋታ ብቻ ሳይሆን በሌሎች አገራት ዘንድ ጭምር የሚኖራትን ተሰሚነት የሚያጎላና የኢኮኖሚ ደረጃዋንም ከፍ የሚደርግ ነው። ህዝቡም ከድህነት ለመውጣት ያለውን ቁርጠኝነት እያንፀባረቀበት ይገኛል።
የግድቡ ግንባታ ህዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሔራዊ ምክር ቤትም ልዩ ልዩ ሽልማቶችን በማዘጋጀት በ ”8100 ኤ” አጭር የጽሁፍ መልዕክት አማካኝነት ለግንባታው የሚውል ገንዘብ አሰባስቧል፤ እያሰባሰበም ይገኛል።በቅርቡም የኢትዮ ቴሌኮም በ 8100 አማካኝነት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት በሶስተኛ ዙር ከህዝቡ የተበረከተውን የገንዘብ ድጋፍ 122 ሚሊዮን 467 ሺህ 676 ብር አስረክቧል፡፡
ህዝቡ የግድቡ ግንባታ የደረሰበትን ደረጃ በተለያዩ የመረጃ ምንጮች አማካኝነት እየተከታተለ ከመሆኑ በተጨማሪ ድጋፉን አጠናክሮ ቀጥሏል። ይህ ድጋፍ ኢትዮጵያዊ እንደ አይኑ ብሌን የሚመለከተው ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ በአሁኑ ወቅት ከ79 በመቶ በላይ ተጠናቋል።ይህም ለመጠናቀቅ መቃረቡንና የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ መድረሱን ማረጋገጫ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ እየገነባችው የምትገኘው በአፍሪካ በቀዳሚነቱ የሚጠቀሰው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት የሚገነባው በውጭ ዕርዳታ ሳይሆን በራስ አቅም መሆኑ ለአገሪቷም ሆነ ለህዝቦቿ ብሄራዊ ኩራትን የሚፈጥር ነው።
ግድቡ በራስ አቅም እንደመገንባቱ የሁሉንም ህዝብ ተሳትፎና ርብርብ የሚጠይቅ ነው፡፡ የሚኖረው ጠቀሜታ ግን ከትውልድ ትውልድ የሚሸጋገርና የኢትዮጵያን ብሩህ ተስፋ የሚያመላክት ነው። ከግድቡ የሚመነጨው ኃይል ከፍተኛ በመሆኑ እንኳን ለኢትዮጵያውያን ለጎረቤት አገራት ጭምር የሚተርፍ ሀብት ነው።
እኛ ኢትዮጵያውያን ግዙፉን የታላቁን ህዳሴ ግድብ ተባብረን በመገንባት የኢኮኖሚ ዕድገታችን ነዳጅ ልናደርገው በመገስገስ ላይ ነን። የማህበረሰብ ጥናት ምሁራን እንደሚሉት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ በህበረተሰቡ ዘንድ የአንድነት መንፈስን ፈጥሯል።ህዝቡንም በጋራ ወደ ለውጥ እየመራው ይገኛል፡፡ ታላቅ ህዝብና ትልቅ አገር የመሆን ርዕይንም እንድንሰንቅ አድርጎናል።ከብድርና ከልመና በመላቀቅ በራስ ገንዘብና ሀብት መስራት እችላለሁ የሚለውን ስሜት አስርፆልናል።በቀጠናው ያሉትን አገሮችም በኃይል የሚያስተሳስር መሆኑ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትንም ያጠናክራል።
በኢትዮጵያ የግል ባለሀብቱ የአገራችን የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽ ሞተር ነው። በተለይ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመገንባት ከውጭ የምናስመጣቸውን ሸቀጦች በአገር ውስጥ ለመተካት መልካም ጅማሮዎች እየታዩ ናቸው፡ ፡ይህን ግብ ለማሳካት ደግሞ በርካታ መካካለኛና ግዙፍ ኢንዱስትሪዎችን በመቋቋም ላይ ይገኛሉ ።ለምሳሌ የብረታ ብረት፣የጨርቃ ጨርቅ፣ የቆዳና የግብርና ምርት ማቀነባበሪያዎች በብዛት በመቋቋምና በመስፋፋት ላይ ናቸው። ለአብነት ያህል የኢንዱስትሪ ፓርኮችና የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ፓርኮች ባባለሀብቱ ጭምር እየተቋቋሙ ያሉ ፋብሪካዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ለእነዚህ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ በቂ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦትን ማሟላት ያስፈልጋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ደግሞ ስድስት ሺህ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል የሚያመነጭ በመሆኑ ለአገሪቷ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለጎርቤት አገሮች ጭምር የሚተርፍ ይሆናል።
ይህን ስንል የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግንባታ አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡የዲፕሎማሲ ጫናውና በግንባታ ወቅት ያጋጠሙ የሙስና ችግሮችን አልፎና ተሻግሮ ነው እዚህ የደረሰው፡፡አሁንም የግድቡን ግንባታ ለማደናቀፍና አካባቢውን የትርምስ ቀጠና ለማድረግ ያልተሸረበ ሴራ ያልተደረገ ጥረት የለም፡፡እነዚህ ሁሉ ፈተናዎች ሳይበግሩት የግድቡ ግንባታ ፍጥነት እየጨመረ ነው፡ ፡ በመጪው ሀምሌ ወር ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት ለማካሄድም ዕቅድ ተይዟል፡፡በመጪው ዓመት መጀመሪያ ላይም የመጀመሪያውን የኤሌክትሪክ ሀይል እሸት የምንቀምስ ይሆናል፡፡
ስለዚህ ቀኝም ነፈሰ ግራ ፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ለአፍታ እንኳ ሳይቆም በተጀመረበት ፍጥነት እየተጓዘ አስረኛ ዓመቱን ይዟል።የህዝቡም ተሳትፎ ግለቱን ጠብቆ እየሄደ ነው።ስለዚህ የነገ የአፍሪካ የኃይል ማማ ባለቤትና የኃይልነታችን ትንሳኤ ማሳያ የሆነውን ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እስኪቋጭ ድረስ ድጋፋችንን አጠናክረን ልንቀጥል ይገባል።
“በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ” እንዲሉ የኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት እስካሁን ለፕሮጀክቱ ግንባታና ስምረት ያሳዩት ቁርጠኝነት ግንባታው እስኪጠናቀቅ አጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 16/2013