ፍሬህይወት አወቀ
በሀገሪቱ ከሚስተዋሉ በርካታ ችግሮች መካከል የመኖሪያ ቤት ችግር ቀዳሚው ስለመሆኑ የከተማዋን ገጽታ አጠልሽተው በየጥጋ ጥጉ የተኮለኮሉት የላስቲክና የሸራ መጠለያዎች፤ በከተማዋ ዳርቻና ወንዞች አካባቢ ተስፋፍተው የሚታዩ የጨረቃ ቤቶች ምስክር ናቸው። በአጭር ጊዜ ተገንብተው ለአገልግሎት የሚበቁት እነዚህ ህገ ወጥ ቤቶች ማታ ተሰርተው ጠዋት አገልግሎት ላይ ይውላሉ።
በከተማዋ የሚታየው የመኖሪያ ቤት ችግር ከመሬት አጠቃቀም ስርዓት ጋር ተያይዞ የመጣ ስለመሆኑ ባለሙያዎች ይናገራሉ። ችግሩን መፍታት የሚቻለው እንደምን ባለ መንገድ ነው? በስፋት የሚታየውን የጨረቃ ቤት ግንባታስ እንዴት ማስቆም ይቻላል? እነዚህ የጨረቃ ቤቶች ባይኖሩስ ዜጎች ምን አይነት ዕጣ ፈንታ ይገጥማቸው ይሆን? ለሚሉት ጥያቄዎች በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የከተማ ፕላን ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር ፍሬው መንግስቱ ምላሽ ሰጥተውናል።
አዲስ አበባ ከተማ የመኖሪያ ቤት ችግር ጎልቶ የሚታይባት ብትሆንም አጠቃላይ ለነዋሪዎቿ ምቹ አይደለችም። በተለይም በአሁን ወቅት ከገጠር ወደ ከተማ የሚፈልሰው ህዝብ ከፍተኛ ቁጥር ያለው በመሆኑና የከተማዋ ኢኮኖሚ ደግሞ ይህን ቁጥር መሸከም የሚችል ባለመሆኑ ችግሩን ይበልጥ ያገዝፈዋል። በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው አብዛኛው ህዝብ በኢመደበኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚተዳደር ነው ። ይህም የሆነው የከተማው ኢኮኖሚ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ለዜጎች ማሟላት ባለመቻሉ ነው።
የመኖሪያ ቤት አቅርቦትንም በተመለከተ እንዲሁ ነው። ሰዎች በሕይወት ሲኖሩ ለመኖር የሚያስፈልጋቸውን መሰረታዊ የሚባሉትን ምግብ፣ ልብስና መጠለያ ማግኘት ይፈልጋሉ። መንግስት እነዚህን መሰረታዊ ፍላጎቶች ዜጎች በቀላሉ ማግኘት የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸት ይጠበቅበታል። ነገር ግን መንግስት ይህን ማሟላት ካልቻለ ዜጎች የራሳቸውን አማራጭ ይወስዳሉ። እራሳቸውን እና ቤተሰቦቻቸውን ከአውሬ ከመበላት ለማዳን በቻሉት አቅም ሁሉ የሚታትሩ በመሆናቸው የጨረቃ ቤት ይሰራሉ።
አንዱ ማሳያም አሁን በከተማችን ተንሰራፍቶ የሚታየው የጨረቃ ቤት ነው። ምክንያቱም የሰው ልጅ በተፈጥሮው እራሱንና ቤተሰቡን መጠበቅ ያለበት መሆኑና ተፈጥሯዊ መብት በመሆኑም ጭምር በህገ ወጥ መንገድ መጠለያ ይሰራሉ። ስለዚህ የሚመለከተው አካል ለምን የጨረቃ ቤት ተሰራ ብሎ ከመጠየቅ ባለፈ ለችግሩ መፍትሔ መፈለግ ይኖርበታል።
በአሁን ወቅት በከተማ ውስጥ ዕለት ዕለት እየተስፋፉ ያሉትን የጨረቃ ቤቶች ማስቆም ከባድ ነው። ነገር ግን የሞያ ማህበራትን ጨምሮ የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ ለመፍትሔው በጋራ መሰለፍ ይኖርባቸዋል። ችግሩ በመንግስት አቅም ብቻ የሚፈታ ባለመሆኑ የሁሉንም ተሳትፎ ይፈልጋል። ስለዚህ እዚህ አካላት የችግሩን ስፋትና ጥልቀት በሚገባ በመረዳት በሞያቸው መፍትሔ ማቅረብ አለባቸው።
የሞያ ማህበራት ለመፍትሔው ሰፊ ተሳትፎ ማድረግ የሚጠበቅባቸው መሆኑን ያነሱት ዶክተር ፍሬው፤ በተለይም የአርክቴክቶች የሙያ ማህበራት፣ የከተማ ፕላን ባለሙያዎች ችግሩን በማጥናት የመፍትሔ አቅጣጫ ለመንግስት ማቅረብ እንዲሁም በውጭ ሀገራትም ያሉ የሞያ ማህበራትም በተመሳሳይ የመፍትሔ አቅጣጫ ማመላከት ይጠበቅባቸዋል በማለት መንግስት ብቻውን የሚፈታው ችግር አለመሆኑን ይጠቅሳሉ።
አብዛኛው መካካለኛ ገቢ ያለው የማህበረሰብ ክፍል የራሱ የሆነ መኖሪያ ቤት ማግኘት አይችልም። መንግስት መኖሪያ ቤት ማቅረብ ካልቻለ ደግሞ ዜጎች ጨረቃ ቤት ሰርተው ሊኖሩ ይገደዳሉ። እንደ አንድ የመንግስት አካል ዜጎች የጨረቃ ቤት ለምን ይሰራሉ ከማለት ባለፈ እኛ ምን እየሰራን ነው ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል ይላሉ ዶክተር ፍሬው። ዜጎች የጨረቃ ቤት ሰርተው ችግራቸውን ለማቃለል የመፍትሔ አካል መሆናቸውንም ማድነቅ አስፈላጊ እንደሆነ ይናገራሉ። ይህ ማለት ጨረቃ ቤትና ህገ ወጥነት ይስፋፋ ማለታቸው እንዳልሆነና የሚመለከታቸው አካላትም መፍትሔ ከመስጠት ባለፈ የኛ ችግር ነው ብለው መቀበል ያለባቸው ስለመሆኑ ያነሳሉ።
እርግጥ ነው በአስገዳጅ ምክንያቶች ህገወጥ ቤቶችን የሚገነቡ እንዳሉ ሁሉ፤ አንዳንዶች ደግሞ የመንግስትን የግንባታ ፈቃድ ላለማውጣት፣ የንብረት ዝውውር ወጪ ላለመክፈል እና ሌሎች የመንግስትን ግብር እና ሌሎች ህጋዊ መንገዶችን ላለመከተል በከፍተኛ ገንዘብ ወጪ ፎቅ የሚገነቡም አሉ። መንግስት እንደእነዚህ አይነቶቹን መከታተልና ወደ ህጋዊ መስመሩ እንዲገቡ አስተማሪ ቅጣት መጣል ይኖርበታል። ነገር ግን አማራጭ አጥተው በእንጨትና በጭቃ ቤት ለሚሰሩ ዜጎች አማራጭ ለማቅረብ ጥረት ማድረግ ከመንግስት ይጠበቃል።
በህጋዊም ይሁን በህገ ወጥ መንገድ ቤት ለመስራት አስፈላጊውና መሰረታዊው ነገር መሬት እንደሆነ ይታወቃል። ነገር ግን በሀገሪቱ ያለው የመሬት አጠቃቀም እጅግ ከስርዓትና ከአግባብ ውጭ በመሆኑ በከተማዋ ለሚታየው የመኖሪያ ቤት እጥረት የጎላ ድርሻ አለው። መሬት ኢትዮጵያ ውስጥ ልክ እንደ ነዳጅ ብቸኛው የሀብት ምንጭ ሆኖ ብዙዎች ዕድሉን ያገኙ ቡድኖችም ሆኑ ግለሰቦቸ እየተቀራመቱት እንደሆነ የሚያነሱት ዶክተር ፍሬው፤ መሬት የማህበረሰቡ የጋራ ውስን ሀብት ተብሎ መወሰድ የነበረበት ነው ይላሉ። ነገር ግን ይህ ባለመሆኑ በመሬት ምክንያት አሁን ላይ በሀገሪቱ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ተፈጥረዋል። ከእነዚህም መካከል የመኖሪያ ቤት አቅርቦት እጥረት በዋናነት ይጠቀሳል።
ውስን ሀብት ማለት ልንለጥጠውና ልንጨምርበት የማይቻል ሆኖ ሳለ ነገር ግን ገንዘብ መክፈል ስለተቻለ ብቻ አንድ ሰው ውስንና የጋራ የሆነውን ሀብት ብቻውን ሲሰበስበው ይስተዋላል። የግል አልሚዎችን ለአብነት የሚያነሱት ዶክተር ፍሬው፤ እነዚህ የግል አልሚዎች ገንዘብ ስላላቸው ብቻ አንድ ሺ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ አንድ ቪላ ቤት ሰርተው ይሸጣሉ። በተቃራኒው ደግሞ ለአንድ ደሃ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ለመስራት 50 ካሬ ሜትር ቦታ ለመስጠት ችግር ሲሆን ይታያል። ስለዚህ መንግስት መሬት የማህበረሰቡ ውስን የሆነ የጋራ ሀብት ነው በማለት መሬትን በአግባቡ ማስተዳደር የሚቻልበትን መንገድ መቀየስ እንዳለበት ይመክራሉ።
በተለይም ከኢንዱስትሪው ቀጥሎ ከፍተኛ ትኩረት ለመሬት በመስጠት እንደ ከተማ አስተዳደር የመሬት አስተዳደሩ ላይ ሰፊ ሥራ መሰራት ይኖርበታል። በአሁን ወቅት ዕድሉን ያገኘ ሁሉ መሬትን አየር በአየር በመሸጥ በቀላሉ የሀብት መሰብሰቢያ ሲያደርገው ይታያል። ይህ ደግሞ ዳር ቆሞ ለሚታዘብ አሳፋሪና ትዝብት ውስጥ የሚጥል ሥራ ነው የሚሉት ዶክተር ፍሬው፤ መሬትን እያስተዳደርን ያለንበት መንገድ መፈተሸ ይኖርበታል ባይ ናቸው። ምክንያቱም የመሰረተ ልማት አቅርቦትና አገልግሎት አሰጣጥን ማስፋፋት የሚቻለው የመሬት አስተዳደር ስርዓቱ ጤናማ መሆን ሲችል መሆኑን ያስረዳሉ።
አዲስ አበባን ጨምሮ ሌሎች ከተሞች ላይ የሚስተዋሉ የመኖሪያ ቤትና አጠቃላይ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት የመሰረተ ልማት ፖሊሲውን ማየት ተገቢ መሆኑን የሚያነሱት ዶክተር ፍሬው፤ የመሰረተ ልማት አቅርቦትና የመሬት አስተዳደር የተያያዙ ጉዳዮች መሆናቸውን ይጠቅሳሉ ።
መሰረተ ልማቶች የሚስፋፉትም በሀገር ውስጥ ከሚሰበሰቡ ግብሮች እና መሬትን ሊዝ በማድረግ ከሚገኝ ገቢ ነው። ከመሬት በሚገኝ ገቢ መኖሪያ ቤትና መንገዶች ይስፋፋሉ የሚል ፖሊሲ መኖሩን አስታውሰው፤ መሬት በሊዝ ተሸጦ ለጊዜው የተወሰነ መንገድ ይሰራ ይሆናል። ነገር ግን ከሊዙ የሚገኘው ገቢ ቀጣይነት ባለውና ዘላቂ በሆነ መንገድ ለመሰረተ ልማቱ ማስፋፊያ የሚውልበትን መንገድ ማሰብ እንደሚያስፈልግ ይናገራሉ ።
የአዲስ አበባ ከተማ መሬት በሊዝ ጨረታ ሳይሆን በአስተዳደራዊ ምደባ ሲሰጥ እንደነበር ያስታወሱት ዶክተር ፍሬው፤ ይህ አስተዳደራዊ ምደባም ከፍትሀዊነት አንጻርም ተገቢነት የሌላው በመሆኑ ውስንና የጋራ ሀብት አስተዳደሩ በአግባቡ ሊመራው የግድ ያስፈልጋል ። በተለይም በአሁን ወቅት የመሬት አስተዳደሩ እነዚህን ችግሮች በመፈተሽ ውስን እና የማህበረሰቡ የጋራ የሆነውን ሀብት ፍትሀዊ በሆነ መንገድ በማስተዳደር የመኖሪያ ቤት እጥረትን ማቃለል ይቻላል።
ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ ያልነበሩ ህንጻዎች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከተማዋ እያደር የሚበቅሉ እንጉዳይ ሆነዋል። እነዚህ በርካታ ግንባታዎች በመንግስትም ሆነ በግልና በጋራ የሚገነቡ ቢሆኑም ሀብት ከመፍጠርና ንብረት ከማፍራት አንጻር የሚበረታቱ ናቸው። የኮንስት ራክሽን እድገቱንም ማሳየት የሚችሉ ናቸው። ነገር ግን ንብረት ማፍራት ብቻውን በቂ ካለመሆኑም በላይ የራሱ ችግር ያለው መሆኑን ያነሱት ዶክተር ፍሬው፤ ለአብነትም መንግስት የሚገነባቸው የጋራ መኖሪያ ቤቶች በሙሉ በትክክል ለታሰበላቸው ዓላማ ውለዋል ወይ ተብሎ ቢፈተሸ ጥያቄ ውስጥ የሚገቡ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ። ምክንያቱም በርካቶች የደላሎች ሲሳይ ሆነው የሚቀሩበት አጋጣሚ አለ። ስለዚህ ለተጠቃሚዎች መድረስ እንዲችል በጥንቃቄ መመራት ይኖርበታል።
ይሁንና እስካሁን በከተማዋ የሚታየውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል በመንግስትም ሆነ በግል አልሚዎች የተደረገው ጥረት ከነችግሩም ቢሆን ሊበረ ታታ የሚገባው መሆኑን ዶክተር ፍሬው ያነሳሉ። ነገር ግን በጥንቃቄ ካልተመራ ተጠቃሚ መሆን የሚገባቸው አካለት ተገፍተው የማይመለከታቸው አካላት ሊጠቀሙ ይችላሉ። ይህ ደግሞ ሊታሰብበት የሚገባውና ከግንባታው ባሻገር በዘርፉ ፍትሀዊ ተጠቃሚነት እንዲኖር በማረጋጋጥ ማነው ተጠቃሚ እየሆነ ያለው የሚለውን መፈተሽ ያስፈልጋል።
ከዚህ ጋር ተያይዞ ፍትሀዊ ተጠቃሚነትና አገልግሎት አሰጣጥን አስመልክቶ የከተማ አስተዳደሮች በምን ቁመና ላይ እንደሚገኙ መጠየቅ ተገቢ መሆኑን ያነሱት ዶክተር ፍሬው። በሀገሪቱ ለቁጥር የበዙ የአስተዳደርና የመሪነት ብቃት ያላቸው መልካም ሰዎች እንዳሉ ይታመናል። ይሁንና ‹‹የከተማ ሥራ አመራር በልበ ብርሃንነት አይመራም›› ይላሉ። ስለዚህ የከተማ ሥራ አመራሮች የተወሰነ ዕውቀት ኖሯቸው ቢመሩት የተሻለ እንደሚሆን ይናገራሉ ። ለዚህም በከተሞች የሚስተዋሉ ችግሮች እጅግ የተወሳሰቡ መሆናቸው ከተማ አስተዳደሮች የተሻለ ዕውቀት ባላቸው አመራሮች መምራት አዋጭ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘርፉ ትምህርት መስጠት ተጀምሮ እንደነበር አንስተዋል። ሰዎች ባላቸው የአመራር ብቃትና ቅንነት ዕውቀት ቢጨመርበት የተሻለ ውጤት ማምጣት የሚቻል እንደሆነም ያላቸውን ዕምነት ይገልጻሉ።
ከተሞች ከፊት ለፊት እየገጠሟቸው ያሉ በርካታ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች እየተበራከቱ ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ ቆም ብለን ማሰብ የሚገባው ጊዜ አሁን ነው የሚሉት ዶክተር ፍሬው፤ እየመጣ ያለው ሰፊ የስራ አጥ ቁጥር ለመቀነስ፣ የመኖሪያ ቤት አቅርቦት እጥረትን ለመቅረፍና አጠቃላይ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ የሚያስችል አዲስና ፈጣን አሰራሮችን መከተል ያስፈልጋል። ይህን ማድረግ ካልተቻለ አሁን ባለው ዝግጁነት የችግሩ አሳሳቢነት በቀጣይ ከዚህ በበለጠ እንደሚሆን ያላቸውን ስጋት አስረድተዋል።
በተለይም የከተሞችን መሰረት ልማት ለማስፋፋት መንግስት ገንዘብ ሲያጥረው ይስተዋላል። ነገር ግን ችግሩን ለመፍታት ቁርጠኝነቱ ካለ በርካታ አማራጭ መንገዶች መኖራቸውን የሚገልጹት ዶክተር ፍሬው፤ ለአብነትም የግል ባለሀብቱን በማሳተፍ መስራት እንደሚቻል አንስተዋል። መኖሪያ ቤት ለመገንባት መንግስት እስካሁን ባደረገው ጥረት ተደራሽ መሆን ባለመቻሉ የግል አልሚዎችን በስፋት ማሳተፍ ተገቢ ነው። ይሁንና ከምንም ነገር በላይ ውስንና የጋራ ሀብት የሆነውን መሬት በአግባቡ መጠቀም እንዲቻል የመሬት አስተዳደሩ በአግባቡ ሊመራ የሚገባው አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን በአጽንኦት ይናገራሉ ።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 9/2013