ዘለዓለም የሳጥን ወርቅ (የእፀ ሳቤቅ አባት)
ደረቱ ላይ ናት አይኖቿን ከድና ዝምታ ውጧት:: ረጅም ጸጉሯ ከጀርባዋ ሸሽቶ እንደ ሸማ ሁለቱንም አልብሷቸዋል:: ቀይ ናት በወናፍ እንደ ፋመ የምድጃ እሳት ጸበል ዳር እንደ በቀለ ዋርካ እንዳጠላው ትርንጎ እንደዚህ:: ማመስገኛው ናት የቃል ኪዳን ገመዱ በዝምታ የሚያደምጣት በተመስጦ የሚቀኛት ቅኔ ማህሌቱ::
ናርዶስ ትባላለች እሱ ናርዶሴ ይላታል:: በህይወቱ ከትናንት እስከዛሬ የእውነት የሚያውቃቸው ሶስት ሴቶች አሉ:: አብረውት የተሸመኑ፣ አብረውት የተደሩ የነፍሱ ድርና ማግ:: ትኩስ ረመጣዊ ትንፋሽ ደረቱን እየገረፈው አይኖቹን ወደ ግድግዳው ወረወረ::
ጠይም ሴት በትልቅ የፎቶ ፍሬም ውስጥ ታየችው:: እንደ እግዜር የምትስቅ፣ እንደ እመብርሀን ብሩክ የሆነች እንስት:: እናቱ ናት የነፍሱ ውብ ስዕል:: በልጅነቱ ነው ያጣት ብዙ ነገሯ አይረሳውም እናቱን ላለመርሳት ሲል ትላንትን እንደ ዛሬ ይኖረዋል:: እግዜሩ ትመስለው ነበር፣ የፍጥረት ሁሉ አለኝታ እንዲህም ትመስለው ነበር::
ጠዋት ከእንቅልፉ ሲነሳ የሚወደውን ቁርስ ሰርታ ነበር የምትጠብቀው:: ከዛም እያጎረሰችው በልቶ ይጨርሳል:: ከዛም ልብሶቹን ታለብሰዋለች ፤ከዛም ፊቱንና ጭንቅላቱን በቅባት አውዝታ እጁን ይዛ ግማሽ መንገድ ድረስ ትምህርት ቤት ትሸኘዋለች:: እየጠየቃት እሷም እየመለሰች::
‹እማ ለምን አንቺ አብረሽኝ አትማሪም? ወደ ላይ አንጋጦ እያያት ይጠይቃታል::
ሳቋን መቆጣጠር እያቃታት ‹እኔ ትልቅ ነኛ በዛ ላይ ደግሞ ምሳ ማን ሰርቶ ይጠብቅሀል?
‹ትልቅ ሰው አይማርም እንዴ? ደሞ እግዚአብሄር ነው ለሰው ሁሉ ምግብ የሚሰጠው አላልሽኝም?
መልስ አጥታ ዝም ትለዋለች ጉንጩን አገላብጣ ስማ ወደ ትምህርት ቤት ትልከዋለች ከአይኗ እስኪሰወር ድረስ ቆማ ታየዋለች ሲመለስም ግማሽ መንገድ ድረስ ሄዳ ትቀበለዋለች ስትሸኘው እንደምታደርገው አቅፋ ትስመዋለች ቦርሳውን ይዛለት እያወሩ እየተሳሳቁ፣ አፉ ውስጥ የሚያላምጠውን ከረሜላ ሰብሮ ሊሰጣት እየታገለ ወደ ቤት ይመጣሉ::
‹ትምህርት እንዴት ነው? ትጠይቀዋለች::
‹የሰራሽልኝን የቤት ስራ አስር ከአስር አገኘሁ የጠየቀችውን ትቶ ያልጠየቀችውን ይመልሳል በደስታ በኩራት::
‹ጎበዝ የኔ ልጅ! ትለዋለች እያቀፈችው::
‹ቆይ እማ ግን ላንቺ ልብስ እንድገዛልሽ መቼ ነው የማድገው? እንደ አባዬ ትልቅ አልሆንም? ሌላ ጥያቄ ይጠይቃታል::
እያሳቃት እያስገረማት በዚህ ሁሉ ቤት ይደርሳሉ እንደተለመደው ቤት የሚወደውን ምሳ ሰርታ አብረው ይበላሉ ከምሳ በኋላ እሱ የቤት ስራውን እሷ ደግሞ ለቅዳሜ ገበያ የሚደርስ እጅ ስራ ዳንቴሏን እየሰሩ እያወሩ፣ እየተላፉ ይቆያሉ እንደምትወደው አንድ ሚሊየን ጊዜ ትነግረዋለች መልስ የሌላቸውን አንድ ሚሊዮን ጥያቄ ይጠይቃታል::
‹አንተ የተስፋዬ ጥግ ነህ በእንባዬ ያበቀልኩህ ከነፍሷ በፈለቀ እናታዊ ሀቅ እንዲህ ትለዋለች::
የምትለው አይገባውም እያዳመጠ ዝም ይላታል::
‹አንተ በመኖሬ ውስጥ አለክ በዚህኛውም በዚያኛውም አለሜ ትልቅ ጉዳዬ ነህ እንደምወድህ መቼም እንዳትረሳ ትለዋለች እንደ መገበሪያ ስንዴ የሚያሳሱ ጉንጮቹን አገላብጣ እየሳመችው::
ጉያዋ ውስጥ ሸጉጣ በመኮርኮር እያሳቀችው ጸጉሩን እያሻሸችው አብረው ያመሻሉ ቅዳሜና እሁድ ገላውን አጥባ ጸጉሩን ላጭታ ለሰኞ ማለዳ ታዘጋጀዋለች አንድ ቀን ከትምህርት ቤት ልትቀበለው ወደ እሱ እየመጣች ነበር እያያት ነበር እሷም እያየችው ናፍቀህኛል ብላ ጉንጩን ልትስመው ከንፈሯን ስታመቻች አይቷታል ልታቅፈው እጆቿን ስትዘረጋ ትዝ ይለዋል እየሳቀች እንደነበር የሚወደውን ቸኮሌት በእጇ ይዛ እየጠበቀችው እንደነበር ይሄም ይታወሰዋል ቀዩን የቤት ውስጥ ፒጃማዋን ለብሳ ነበር ቅዳሜ እለት ዳንቴል ሸጣ የገዛችውን አዲሱን ጫማዋንም ተጫምታ ወደ እሱ ስትመጣ የምትስቀውን ሳቋን ስቃ ነበር::
ድንገት ግን መኪና ገጭቷት አስፓልት ላይ ስትወድቅ አያት ይሄው ለዘለዓለም ተለየችው ሀገሩ ነበረች ትልቅ አለሙ ሁሉን የሰጠችው ሁሉን ያገኘባት አንድም ያላጣባት በለሱ በለጋነት የሚያውቃት አንድ እውነቱ የልጅነት ማስታወሻው ራሱን እያለቀሰ አገኘው አባቱን አይወደውም እዚህ ምድር ላይ አብዝቶ የሚጠላው አንድ ሰው አባቱ ነው ፤ምክንያቱ ደግሞ እየሰከረ እየመጣ እናቱን ስለሚደበድባት ነበር::
ሁለተኛዋ ሴት ሰርካለም ናት እናቱ ከሞተች በኋላ ያወቃት፣ አባቱ ሌላ ሴት አግብቶ ከቤት ካባረረው በኋላ የቀረባት፣ በጎዳና ተዳዳሪነት አራት ኪሎ ጎዳና ላይ ውሎ ሲያድር የቀረባት እንስት ሰርካለም ባሏን ፈትታ ከሶስት ልጆቿ ጋር የምትኖር ሴት ናት መሀል አራት ኪሎ በቡና መሸጥ የምትተዳደር በገጽዋ ላይ እናቱን የሚመስል ገጽ አለ እናቱ እሱ ፊት ስቃ አባቱ ፊት ስታለቅስ ያውቃታል ሰርካለምም እንደዛ ነበረች እያለቀሰች የምትስቅ ትንሳኤና ምጽዓት ሁሌ ጠዋት ከሰዐትም ከእንባና ሳቋ ጋር ያያታል ለምን ተከፍታ እንደምትኖር አይገባውም ግን ያያታል በብዙ መከፋት በብዙ ተስፋ::
ትልቅ ዳሌ አላት በተራመደች ቁጥር የሚወዛወዝ አብዛኞቹ ወንዶች ከቡናዋ በላይ ዳሌዋን ብለው እንደሚመጡ ያውቃል ብዙ ወንዶችም ቡናዋ እንደሚጣፍጥ ሲያወሩ ሰምቷል አብዛኞቹ ደንበኞቿ ወንዶች መሆናቸው ደግሞ የልጅነት ግራ አጋቢ ጥያቄው ነበር ሁሌ በወንድ ደንበኞቿ ተከባ ነው የሚያያት ሁሉም ሰው የሚወድላትን ሳቋን ስቃ ፍንጭት ጥርሷን ገልጣ ወጣትነት የከዳው ዳሌዋን እየነቀነቀች በቃ እንደዚህ::
ማታ ስራዋን ጨርሳ ወደ ቤት ስትሄድ የራት ሰጥታው ነው የምትሄደው አንድ ቀን ጠዋት ከተኛበት ሲነሳ ከደንበኞቿ ከአንዱ ጋር ከሆቴል ቤት ስትወጣ አያት እየቆየ ሲመጣ ከቡና ደንበኞቿ ውስጥ አባቱም አንዱ ሆኖ አገኘው እየቆየ ሲመጣ ከሶስት ልጆቿ ሁለቱ የአባቱ ልጆች እንደሆኑ ሰማ እየቆየ ሲመጣ ከልቡ አወጣት::
ከራሱም ከሰው ልጅም ሸሽቶ አራት ኪሎ ጎዳና ላይ አስራ አምስት አመታትን ኖረ የማታ እየተማረ ትምህርቱን እስከ አስር ቆጠረ:: አልቆመም ቀን እየሰራ ማታ እየተማረ በማርኬቲንግ ዲግሪውን ያዘ:: እናቱ በህይወቱ ውስጥ ብዙ እውነትን አስቀምጣለች ትምህርት ቤት ስትወስደውና ስትመልሰው በልጅነት ነፍሱ ውስጥ ትልቅ አለም ገንብታለች አብሯት በቆየበት የልጅና የእናትነት ጊዜውም የማይፈርስ ዘለዓለማዊ ስንቅን ሰንቃለታለች::
ከትላንት እስከዛሬ በእናቱ እውነት ላይ ተረማምዷል በአንድ ድርጅት ውስጥ ተቀጥሮ በመስራት ላይ ይገኛል ሁሌ ጠዋት ስራ ሲሄድ አንዲት ሴት አንድ ትንሽ ልጅን በእጇ ይዛ ወደ ትምህርት ቤት ስትወስደው ያያል ማታ ከስራ ሲወጣም እንደዚሁ ይቺኑ ሴት ከዛ ህጻን ጋር ድሮ እሱና እናቱ እንደሚሆኑት ህጻኑ እየጠየቀ እሷ እየመለሰች ወደ ቤት ሲመለሱ ያያል በጣም ይገረማል ያኔ እሱና እናቱ እንዲህ ነበሩ ለበርካታ ጊዜ ሲሄዱና ሲመጡ ቆሞ አይቷቸው ያውቃል እሷ እናቱን ህጻኑ ደግሞ እሱን ሆኖ ልጇ ይሁን አይሁን የሚያውቀው ነገር የለም አጋጣሚው ከእሱ ትናንትና ጋር በመመሳሰሉ ብቻ ደስተኛ ነበር:: አንድ ቀን ከሰዐት በኋላ ከትምህርት ቤት ሲመለሱ ከኋላቸው እየተከተለ አብሯቸው ሄደ የሚያወሩትን ሁሉ ሰማ::
‹አንተ ደስታዬ ነህ ሳቅህ ነው የሚያኖረኝ ትለዋለች::
ህጻኑ መልስ አጥቶ ዝም ይላታል
‹አድገህ ትልቅ ሆነህ ማየት ህልሜ ነው› ትደግምለታለች::
‹እንዳንቺ? ሲል ይጠይቃታል::
‹ከኔም በላይ ከሰው ልጅ ሁሉ በላይ ስትል ትመልስለታለች::
እናቱ ፊቱ መጣች እንዲህ ነበር የምትለው በነጋታው ወደ ትምህርት ቤት ሲሄዱ ጠብቆ ‹ከእናቴ ጋር እንዳንቺና እንደ ልጅሽ ሆኜ ነበር ያደኩት:: አላት::
‹እድለኛ ነህ› እንደ በርሀ እንኮይ የላመ ቀይ ፊቷን በፈገግታ ሞልታ መለሰችለት::
‹ማርቆስ እባላለሁ..ማታ በዚህ መንገድ ላይ ስትመለሺ የማወራሽ አለኝ›
አፈር አለች ሴታዊ እፍርታ::
‹ቢያንስ ስምሽን ነግረሽኝ ሂጂ?
‹ናርዶስ› ሙዚቃዊ ድምጽ ከአንደበቷ ወጣ::
‹እኔ ናርዶሴ እልሻለው›
አቀርቅራ ሄደች::
ተቀራረቡ ጠዋትና ማታ አብረው መሄድና መምጣት ጀመሩ ህጻኑ የእህቷ ልጅ እንደሆነ አወቀ ናርዶስ እንደ እናቱ የእውነት የሚያውቃት ሶስተኛዋ ሴት ሆና ወደ ህይወቱ መጣች የእናቱ ሀቅ ሁሌም አብሮት ይኖራል በህይወቱ ውስጥ፣ በኑሮው ውስጥ ሁሉም ቦታ ያገኘዋል::
ናርዶስን አያት ደረቱ ላይ አሸልባለች::
አዲስ ዘመን መጋቢት 26/2013