ታይዋን ለቻይና ዛቻና ማስፈራራት ቦታ እንደማትሰጥ የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ አሌክስ ሁግ አሳወቁ፡፡ ደሴቷ የቻይናን ጥቃት ለመመከት የሚያስችል የጦር ልምምድ እያደረገች መሆኗን አሳይታለች፡፡ ታይዋን ከሰሞኑ ከቻይና የሚደርስባትን ዛቻና ሊደረግባት የታሰበውን ጥቃት ለመመከት ሳትወድ በግድ እራሷን ለመከላከል እንደምትገደድ እያሳወቀች ትገኛለች ፡፡
ቀደም ሲል ለዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ የድረሱልኝ ጥሪ ስታሰማ የነበረችው ታይዋን አሁን ላይ አንጀቷን ጠበቅ አድርጋ የለየለት ለሚመስለው ጦርነት እራሷን እያዘጋጀች ትገኛለች፡፡ ይህንንም በአራቱ ማዕዘናት የሚገኙት የዓለም ማሕበረሰቦች እንዲያውቁላትና ከጎኗም እንዲቆሙ ድጋሚ ጥሪ ማቅረቧን የፕሬዚዳንት ሴንግ ውን ቃል አቀባይን ጠቅሶ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ እ.አ.አ በ1949 አብዛኛው የቻይና ግዛት የኮሚኒስት ርዕዮተ ዓለምን ሲከተል ነበር የተቀሩት ጥቂት የዴሞክራሲ አቀንቃኞች ወደ ታይዋን በመሄድ ደሴቲቱን እንደ ሀገር መሰረቷት፡፡ በዚህም ከቻይና ጋር ያላቸውን ልዩት እያሰፉ ሙጡ፡፡
የቻይና ሲቪል አቬሽን አስተዳደር የታይዋንን ዋና ከተማ በበረራ ዝርዝሩ በማካተት የቻይና ግዛት እንደሆነች በማድረግ ለዓለም አስተዋውቋል፤ ይሁንና እንደ እንግሊዝና ሲንጋፖርን የመሳሰሉት አየር መንገዶች ድርጊቱን በማውገዝ እውቅና ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ግሎባል ታይምስ እንደዘገበው ታይዋን፣ ሆንግ ኮንግና ማካኦ በድረገጻቸው እንዳስነበቡት የዚህ ሁሉ ችግር መንስኤ ቻይና አንድ ቻይና፣ አንድ ሀገር የሚል መርህ በመከተሏ ነው፡፡
ቤጂንግ ታይዋንን ወደ እራሷ ለማካተት ጠንከር ያለ አቋም የያዘችው እ.አ.አ ከ2016 በኋላ ፕሬዚዳንት ሴንግ ውን የታይዋን መሪ ሆነው ከተመረጡ ወዲህ ነው፡፡ ምክንያቱም ፕሬዚዳንቱ በደሴቲቱ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለማሥፈን ቁርጥ አቋም ያላቸው መሆኑና ይህም ለቻይና ትልቅ ስጋት እንደሆነ በማሰብ ነው፡፡ በዚህም ፕሬዚዳንት ሺ ዥን ፒንግ በተለያዩ መድረኮች ታይዋን የቻይና ግዛት መሆኗን ማንም ሰው ሊክደው አይችልም በመሆኑም ቻይና ደሴቲቱን ወደራሷ ለመጠቅለል ማንኛውንም የሃይል እርምጃ መውሰድ እንደምትችልም አሳውቀዋል፡፡ ታይዋን ይህንን ከወደ ቻይና የሚደርስባትን ዛቻ በመመልከት ወታደሮቿ ከወትሮው የተለየ ልምምድ በማድረግ የሚከፈትባቸውን ጥቃት ለመመከት የሚያስችል የጦር ልምምድ እያደረገች ትገኛለች፡፡
የአሜሪካው የመከላከያ ሚኒስትር በበኩላቸው ቻይና በታይዋን ላይ ጥቃት የምትሰነዝር ከሆነ አሜሪካን ነገሩን በቸለተኝነት እንደማታልፈው ከወዲሁ እያሳሰቡ ይገኛሉ፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 18/2011
ሰለሞን በየነ