እያንዳንዱ ህዝብ የተለያየ የስራ ባህል አለው።ከጥንት ህዝቦች የስራ ባህል እንደማሳያነት ብንመለከት በጥንት ግሪካውያን ዘንድ ስራ እርግማን እንደሆነና የሰዎችን ክብር የሚያዋርድ ተግባር የሚል አመለካከት ያላቸው ሲሆን የህይወት ግባቸው ዕረፍት፣ ደስታ፣ ፍስሃ ነው በማለት ያምናሉ፤ አማልክቶቻቸውም ለደስታ እንጂ ለስራ ትኩረት አይሰጡም።በተጨማሪም በግሪካውያን ዘንድ አምላክን መምሰል ማለት ከስራ ነጻ መሆን ማለት ነው።
ነጻ ሰዎች እንዲያስቡ፣ እንዲመራመሩ እንዲጠበቡ፣ እንዲፈላሰፉ፣ እንዲያስተዳድሩ እንጂ እንዲሰሩ፣ እንዲጥሩ እንዲደክሙ አልተፈጠሩም የሚል ዕምነት ነበራቸው።በሌላ መልኩ ደግሞ በጥንት ምስራቃውያን ህዝቦች ዘንድ የስራ ባህል የሚመዘነው ህብረተሰቡ ከሚያመልከው አምላክ የተነሳ በመሆኑ ህብረተሰቡ የሚያመልከው አምላክ ታታሪ ከሆነ ህዝቡም ታታሪ የሚሆንና ህብረተሰቡ የሚከተለው ዕምነት ትጉህነትን የሚያበረታታ ከሆነ ህዝቡም ትጉህ የሚሆን መሆኑን እንረዳለን።በጥንት አይሁዳውያን ዘንድ ከሚያመልኩ አምላክ የተነሳ የስራ ባህላቸው ጠንካራ የነበረ ቢሆንም ከአካባቢያቸው ተጽህኖ የተነሳ ለስራና ለሰራተኝነት ያላቸው አመለካከት ተቀይሮ ለስራ ደረጃ በማውጣትና ቅዱስና እርኩስ ስራ በማለት ስራን የመከፋፈል አስተሳሰብ የመርቀቅና የመጎልበት ዕድል ገጥሞታል።
በኢትዮጵያውያን ዘንድ ስራ ዝቅተኛ ስፍራ የሚሰጠው ሲሆን ለዚህም እንደመነሻ የሆነው ባህላችን የሚመራበት ስርአት ሲሆን ይህም ማለት ባህላችን ክቡር የሚለውና የተዋረደ የሚለው ነገር ያለው በመሆኑ በዚህ መነሻነት የተዋረደና ክቡር በማለት ስራን ስለሚከፋፍሉ ለስራ ያለን አመለካከት ዝቅተኛ እንዲሆንና ሰነፎች እንድንሆን አድርጎናል።ስንፍናችንም ለድህነት፣ ለረሃብና ለጉስቁልና ዳርጎናል።ለዚህም መንፈሳዊ መሪዎቻችን፣ ቤተሰቦቻችን፣ መምህሮቻችን እንዲሁም እያንዳንዱ ግለሰብ ተጠያቂ መሆኑን መዘንጋት የለበትም።ለዛሬ ለብዙ ዘመናት በሚሰሩት ስራ የተሳሳተ ስም ተሰጥቷው ተገለው የነበሩ ነገር ግን የስራ ውጤቶቻቸው ግን “በተከበሩ” ቦታዎች የሚገኙት የሸክላ ውጤቶችን ስለሚያመርቱት እናቶች ነው፤ መልካም ንባብ።
መነሻ
የሸክላ ስራ መነሻው እንዴት እና የት እንደሆነ ባይታወቅም ከሌሎች በማህበረሰቡ ዘንድ ዝቅተኛ ቦታ ከሚሰጣቸው ማለትም እንደ አንጥረኛ፣ ሸማና፣ ሙዚቃ ተጫዋች … በአጠቃላይ የዕደ ጥበብ እና ሙዚቃ ጋር ተገሎ የነበረ መሆኑ እሙን ነው፤ ሙያው ብቻ ሳይሆን ሙያተኛውም እንዲሁ ይገለል ነበር።
እነዚህ በማህበረሰቡ “የተዋረዱ” ተብለው የተለዩት የስራ (የጥበብ) ዓይነቶችን ግን ህብረተሰቡ የሚጠቀምባቸው ለተመረጡ እና ለከፍተኛ ባህላት ነው።“እኔን እኔን ይጠላሉ፤ ምንትሴን ይወዳሉ” እንዳለችው ንብ ማህበረሰቡ ለእነዚህ የጥበብ ሰዎች የተለያዩ ሰሞችን በመስጠት ከተለያዩ ማህበራዊ ህይወት ያገለሏቸው እና የስራ ውጤታቸውን ግን ሲጠቀም ይስተዋላል።ለምሳሌ የሸክላ ውጤቶች ከጥንት ነገስታት ጅምሮ ከማድጋ እስከ እንስራ ለጠጅ ለመጣል እና ጠላ ለመጥመቅ ይጠቀሙበታል።ነገስታቱ ከቦታ ቦታ ለማዘዋወር ሲያስቡ በእነዚሁ ቁሶች ተጠቅመው ነበር የሚጠጡትን ይዘው የሚጓዙት።
ወጭትም ቢሆን በዘመኑ አለ የተባለው ይኸው የሸክላ ምርት ነበር፤ ለቅሶ ቢያጋጥማቸው፣ ለፍርድ ሸንጎ ሲቀመጡ፣ ለሰርግ፤ ለሀዘን… እንዲሁም በእለት ተለዕለት ኑሮአቸው የሚለበሱት ደግሞ የሸማኔን የስራ ውጤት ነው።ብቻ ምን አለፋቹ ህብረተሰቡም ሆነ ነገስታቱ እያንዳንዱ ኑሮአቸው ከእነዚህ ዝቅተኛ ስፍራ በተሰጣቸው የማህበረሰብ ክፍሎች የስራ ውጤት ላይ የተመሰረተ ነው።
የ“እንስራ” የሸክላ ስራ ማዕከል ጊዜያዊ የስራ አስተባባሪ የሆኑት አቶ ሰለሞን አባተ እንደሚሉት በተለያዩ ጊዜያት ለሸክላ ስራ እና ለሸክላ ሰራተኛ የተለያዩ ስሞችን በመስጠት በተለይ ሸክላው ሰሪ በአንድ ቦታ ብቻ ተከልሎ እንዲኖር እንዲሁም ከሌላው የህብረተሰብ ክፍል በየትኛው ማህበራዊ ህይወት እንዳይቀላቀል ሲደረግ መቆየቱን ያስታውሳሉ።አሁንም ቢሆን የተወሰኑ የተሻሻሉ ነገሮችም ቢኖሩም ቀድሞ በማህበረሰቡ ዘንድ የገቡ አመለካከቶች እና አስተሳሰቦችን ከማረቅ አንጻር የሚቀሩ ነገሮች እንዳሉም አቶ ሰለሞን ጠቁመዋል።
የማዕከሉ መከፈት
እንደ አቶ ሰለሞን ገለጻ ማህበረሰቡ ስለ ሸክላ ስራ እና ስራተኛ ባለው አመለካከት የተነሳ እናቶቹ በመሳቀቅ ስራቸውን የሚሰሩት ጫካ ውስጥ ተደብቅው እንደነበር አስታውሰው ይህንንም ያዩት የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ የሸክላ ስራ ሰራተኞችን መገፋት በመመልከት የሚሰሩት ስራ እንደማንኛውም ስራ ሀገሪቱ ለምታደርገው የብልጽግና ጉዞ የራሱ የሆነ አስዋጽኦ እንዳለው በመጥቀስ እናቶቹ በአደባባይ ስራቸውን እንዲሰሩ ያመረቱትንም ምርት በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ወደ ውጭ ኤክስፖርት አድርገው ራሳቸውን እንዲሁም አገራቸውን እንዲጠቅሙ በማለም የ“እንስራ” የሸክላ ማዕከል እንዲከፈት አድርገዋል።እንደ አቶ ሰለሞን ገለጻ በሰኔ 1 ቀን 2012 ዓ.ም የተከፈተው ይህ ማዕከል ለእናቶቹ ምቹ የሥራ ሁኔታ መክፈት ብቻ ሳይሆን ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችንም ይዞ የመጣ ነው፤ የማዕከሉ መከፈት በማህበረሰቡ ዘንድ የነበረውን አስተሳሰብ በተወሰነ ደረጃ የቀረፈም ሆኗል።ለዚህም መሳያ ይላሉ አቶ ሰለሞን ማህበረሰቡ ልጆቹን ወደ ማዕከሉ እያመጣ ልጆቹ ይህንን ሙያ እንዲለምዱ እና እንዲሰለጥኑ ጥያቄ እያቀረበ ነው።
ማን ይናገር የነበረ፤ ማን ያርዳ የቀበረ እንዲሉ በማዕከሉ የሸክላ ስራ ሲሰሩ ያገኘኋቸውን እናት ወይዘሮ አዛለች ገለቴ አንዷ ናቸው።ወይዘሮ አዛለች ለ25 ዓመታት የሸክላን ስራ ሰርተዋል፤ ቀድሞ የነበረውንም ሁኔታ ሲያስረዱ ቤተሰቦቻቸው ሲሰሩ እንደነበር እና እርሳቸውም ይህንኑ ሙያ ከቤተሰብ እንዳገኙት ይናገራሉ፤ ቤተሰቦቻቸው በሚሰሩበት ጊዜም ሆነ እርሳቸው በማህበረሰቡ ዘንድ መልካም የሚባል አመለካከት እንዳልነበረ ያስረዳሉ።
ስራውን ተደብቀው ጫካ ውስጥ ሲሰሩ እንደነበር አስታውሰው ለስራ የሚሆናቸውን ገል ለማምጣት ወደ መርካቶ እና ሌሎች ስፍራ ሲሄዱ ህብረተሰቡ መጡ መጡ በማለት ልጆቹን በመሰብሰብ በሩን በመዘጋት በጣም ልብ የሚሰብር ተግባራት ይፈጽም እንደነበር ወይዘሮ አዛለች ያስረዳሉ፤ አሁን ግን እድሜ ለመንግስት የሚሉት ወይዘሮ አዛለች አደባባይ መውጣት እንደቻሉ የስራ ውጤቶቻቸውም በአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እንዲሁም የከተማው ከንቲባ ታከለ ኡማ በመጎብኘታቸው እንዳስደሰታቸው ይናገራሉ።
ወይዘሮዋ አሁንም ይናገራሉ ከሚደርስባቸው የመገለል እና ከተሰጣቸው ስም የተነሳ ጫካ ተደብቀው በማይመች ሁኔታ ሲሰሩ እንደነበር አስታውሰው አሁን ቀን ወጥቶ በሰው ከመጎብኘት እስከ ሚዲያ ሽፋን ማግኘታቸው በዋጋ ሊተምኑት የማይችል ሀሴት እንደፈጠረላቸውም ገልጸዋል።
አሰራር
በመጀመሪያ ለስራ የሚያስፈልጉ ግብዓቶች ከያሉበት ማሰበሳብ ይጀመራሉ፤ የመጀመሪያው ነገር ጭቃ ነው፤ ይህ ጭቃ ተቆፍሮ የሚወጣ እና ለሸክላ ስራ የሚሆን የተመረጠም የጭቃ ዓይነት ነው።ተቆፍሮ የሚወጣው ጭቃ ቢያንስ ለአንድ ሳምንት የሚያገለግል መሆን አለበት፤ በመቀጠል ገል መገዛት አለበት ይህም መርካቶ ይህንኑ የሚሸጡ ሰዎች አሉ፤ መርካቶ በመሄድም ገሉ ይገዛል፤ ቀጥሎም ገል ማድቀቂያ በተለምዶ ሙቀጫ ይዘጋጃል ገሉ በዚያ እስኪሊም ድረስ ይወቀጣል፤
ገሉን እና ጭቃውን በማዋሃድ ይቦካል፤ የተወሰነ ጸሐይ እንዲነካው ከተደረገ በኋላም ተመልሶ ውሃ እያርከፈከፉ በማቡካት ለሚፈለገው ምርት ዓይነት እየተቀነሰ የተለያዩ ቅርጽ በማውጣት ይሰራል።ታዲያ ቅርጹ ተሰርቶ እንዳለቀ መጥበስ ወይም ማቃጠል የመጨረሻው እና አድካሚው ስራ ነው፤ ይህ የማቃጠል ስራ ኩበት ገዝቶ እሳት አቀጣጥሎ እያንዳንዱን የተሳራውን የሸክላ ምርት እሳቱ ላይ በማድረግ እያዟዟሩ ማቃጠል ያስፈልጋል፤ ታዲያ በዚህ መካከል በእሳቱ ወላፈን መቃጠል በጭሱ ለከባድ ለዓይን ህመም መጋለጥ የሽክላ ሰሪ እናቶቹ የእለት ተዕለት ትግላቸውም ኑሮአቸውም ነው።
የ“እንስራ” የሸክላ ማዕከል አንዱ የቀረፈው ችግር ይህንኑ ነው፤ እናቶቹ በምቹ ቦታ ይሰራሉ፤ ግብዓቱ እዚያው ማዕከል ድረስ ይመጣላቸዋል፤ ማቃጠያም በኤሌክትሪክ የሚሰራ ዘመናዊ የሆነ ተዘጋጅቶላቸዋል፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ገዢዎቻቸውም ቢሆኑ እዚያው ማዕከል እየመጡ እየወሰዱላቸው ነው።እነዚህ እናቶች በማዕከሉ ስራቸውን በሚያከናውኑበት ጊዜም ልጆቻቸው እንዳያስቸግሯቸው የልጆች ማቆያ በማዕሉ የተሰራ ሲሆን ልጆች እዚያ እየተጫወቱ ምግባቸውን በማዕከሉ እንዲመገቡ እየተደረገ ነው።ለዚህም የወረዳው ሴቶች እና ህጻናት ቢሮ ከፍተኛ ድጋፍ ማድረጉንም ሰምተናል።ወይዘሮ አዛለች “አሁንማ አለም ነው !” እንዳሉት የታዘብኩትም ይህንኑ ነው።
ችግር
በማዕከሉ የሚገኙት እናቶች ስለተደረገላቸው ድጋፍ ከአመሰገኑ በኋላ የሚጎሉ ነገሮች እንዳሉ አንስተዋል። በመጀመሪያ ያነሱት የዕቃ ማስቀመጫ መጋዘን አንዱ ነው፤ ይህም የየራሳቸውን ንብረት በአግባቡ ከማስቀመጥ ባለፈ የግቢውን ንጽህና ለመጠበቅ እንደሚረዳም ጠቁመዋል።ሌላኛው ደግሞ የማቃጠያ ማነስ ሲሆን የመጡትም ዘመናዊ ማቃጠያዎች በቶሎ ወደ ስራ እንዲገቡላቸው ጠይቀዋል።ሌላኛው እና ዋነኛው ብለው እናቶች ያነሱት የንግድ ትስስሩን ነው፤ እርግጥ ነጋዴዎቹ እና አንዳንድ ግለሰቦች ማዕከል እየመጡ እየገዙአቸው መሆኑ ደስ ቢያሰኛቸውም ደላሎች እና በመሐል ያሉ ነጋዴዎች የሚጠቀሙትን ያክል እየተጠቀሙ እንዳልሆኑ እና ይህም የሚመለከተው አካል ችግሩን ቀርፎላቸው ከገዚዎቻቸው ጋር በቀጥታ የሚገኛኙበት መንገድ እንዲከፈትም ጥያቄ አቅርበዋል።
ምስጋናና መልዕክት
የማዕከሉ ጊዜያዊ አስተባበሪ አቶ ሰለሞን እንዳሉት በመጀመሪያ የከተማውን ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማን ቦታ ከመስጠት ባለፈ እናቶችን በማረታታት ላደረጉት ከፍተኛ አስዋጽኦ በጣም ማመሰገን እንደሚገባ ገልጸዋል።ሌላኛው ክፍለ ከተማው እንዲሁም ወረዳውን ሊመሰገን እንደሚገባው አቶ ሰለሞን ገልጸዋል።ሌላኛው በማዕከሉ የህጻናት መቆያ በማደራጀት እንዲሁም ሞግዚት እና ምግብ አብሳይ በመቅጠር በሸክላ ስራ ላይ የተሰማሩ እናቶች ስራቸው ላይ ብቻ እንዲያተኮሩ በማድረግ ልጆቻቸው በንጽህና እንዲያዙላቸው ላደረጉትም የከተማው አስተዳደር ሴቶች እና ህጻናት ቢሮ ሊመሰገኑ እንደሚገባ አቶ ሰለሞን ተናግረዋል።
አቶ ሰለሞን አክለው በማዕከሉ የሚገኙ እናቶች አገር በቀል ባህላዊ እውቀት እና ጥበብ የያዙ በአገርም ደረጃ ከፍተኛ ታሪክ መስራት የሚችሉ በተለይ አሁን የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመከተል ድህነትን በማጥፋት ረገድ የራሳቸውን ሚና የሚጫወቱ ናቸው።ስለዚህም እነዚህን እናቶች መጎብኘት እና መደገፍ ትልቅ ለውጥ ያመጣል የሚሉት አቶ ሰለሞን ማንኛውም የህብረተሰብ ክፍል ከነጋዴዎች ከሚገዛ ይልቅ በአፍንጮ በር አካባቢ ከናጄሪያ ኢንባሲ ከፍ ብሎ በሚገኘው ማዕከል እየመጣ ቢገዛ አንደኛ የዋጋ ቅናሽ ያገኛል ሁለተኛ እናቶቹንም እንደሚያበረታታ ጠቅሰው ሌላው ደግሞ ህብረተሰቡ ለራሱ ባህል ትኩረት እንዲሰጥ ያስችለዋልም ብለዋል።
እኛም እንዲህ ያሉ አገር በቀል እውቀቶች ለሚሰጣቸው ትኩረት እያመሰገንን ሌሎችም የተደበቁ ጥበቦች እንዲወጡ እንዲደገፉም እናሳስባለን።ኢትዮጵያ የሰላም፣ የመቻቻል እና የብልጽግና አገርነቷ ይቀጥላል።መልካም ሰንበት!
አዲስ ዘመን ሐምሌ 19 ቀን 2012 ዓ.ም
በአብርሃም ተወልደ