የቬንዙዌላው ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ አገራቸው ከአሜሪካ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ማቋረጧን አስታውቀዋል፡፡ በካራካስ የሚገኙ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችም በ72 ሰዓታት ውስጥ አገሪቱን ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል፡፡ ማዱሮ ውሳኔውን ያሳለፉት ሁዋን ጉዋይዶ የተባሉት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ራሳቸውን የቬንዙዌላ ፕሬዝደንት አድርገው የሰየሙት አሜሪካ ባቀነባበረችው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ እንደሆነ ከገለፁ በኋላ ነው፡፡
ማዱሮ ከፕሬዝደንታዊ ቤተ-መንግሥት በተላለፈ መልዕክታቸው የአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲ ከአሜሪካ ጋር በመመሳጠር መንግሥታቸውን ለመገልበጥ ማሴሩን ተናግረዋል፡፡ ‹‹ቬንዙዌላን ከዋሺንግተን ዲ.ሲ በሚተላለፍ ትዕዛዝ ለመምራት ታቅዶ እየተሰራ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ለቬንዙዌላ ክብር ለመሰዋት ዝግጁ የሆኑ ብዙ ሀገር ወዳድ ሰዎች ስላሉ ያን ማሳካት አይቻልም›› በማለት በብስጭት ተናግረዋል፡፡
ከፕሬዝደንት ማዱሮ መግለጫ ቀደም ብሎ የአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት ሁዋን ጉዋይዶ በበኩላቸው በካራካስ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎቻቸው በተሰበሰቡበት የቬንዙዌላ ጊዜያዊ የሽግግር ፕሬዝደንት እርሳቸው እንደሆኑ አውጀዋል፡፡ በፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ ላይ የትችት ናዳ ያዘነቡባቸው ጉዋይዶ፣ ቬንዙዌላ ከገባችበት ምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ እንድትወጣ የሚያስችል ‹‹የሽግግር መንግሥት›› እንደሚያ ቋቁሙም ቃል ገብተዋል፡፡
ጉዋይዶ በርካታ ደጋፊዎችን እያገኙ መምጣታቸው ለቬንዙዌላ ፖለቲካ አዲስ ቅርፅ እየሰጠው ነው፡፡ የሰውየው ‹‹ጊዜያዊ የሽግግር ፕሬዝደንት እኔ ነኝ›› አዋጅ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲን ከኒኮላስ ማዱሮ መንግሥት ጋር ተመጣጣኝ ሕዝባዊ ድጋፍ ያለው ነገር ግን መንግሥታዊ እንቅስቃሴዎችን የሚያስፈፅምበት ኃይል የሌለው ተገዳዳሪ ቡድን እንደሆነ አድርጎ እንዲያስበው በር ከፍቷል፡፡
ጉዋይዶ ‹‹ጊዜያዊ የሽግግር ፕሬዝደንት እኔ ነኝ›› ብለው ካወጁ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ፕሬዝደንት ማዱሮ የቀውሱ ሁሉ ጠንሳሽ ናት ብለው የሚወቅሷት የልዕለ ኃያላኗ አሜሪካ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ጉዋይዶ የቬንዙዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝደንት ስለመሆናቸው እውቅና ሰጥተዋል፡፡ ፕሬዝደንት ትራምፕ በመግለጫቸው ‹‹የቬንዙዌላ ሕዝቦች በኒኮላስ ማዱሮ አስተዳደር ላይ ያላቸውን ተቃውሞ በጀግንነት ገልጸዋል፡፡ ነፃነታቸውን ጠይቀዋል፤የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ድምፃቸውን አሰምተዋል፡፡ ጉዋይዶ የሚመሩት የቬንዙዌላ ብሔራዊ ጉባዔ (National Assembly) በቬንዙዌላውያን የተመረጠ ብቸኛው ሕጋዊ የመንግሥት አካል ነው›› ብለዋል፡፡
የቀጣናው ዋነኛ ኃይሎች የሚባሉት ብራዚል፣ ኮሎምቢያ፣ ቺሊ፣ ፔሩ እና አርጀንቲናም ራሳቸውን የቬንዙዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝደንት ብለው ለሰየሙት ለሁዋን ጉዋይዶ ድጋፋቸውን ሰጥተዋል፡፡ አዲሱ የብራዚል ፕሬዝደንት ጄር ቦልሶናሮ አገራቸው ሁዋን ጉዋይዶ የቬንዙዌላ ጊዜያዊ ፕሬዝደንት እንደሆኑ እውቅና እንደምትሰጥና ቬንዙዌላውን ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለሚያደርጉት ሽግግር ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ድጋፍ እንደምታደርግ ተናግረዋል፡፡
የኮሎምቢያው ፕሬዝደንት ኢቫን ዳክ በበኩላቸው ኮሎምቢያ ከጉዋይዶ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ጀርባ እንደነበረች ጠቁመው፣ ቬንዙዌላውያን ከአምባገነን አስተዳደር ለመላቀቅ የሚያደርጉትን ትግል አገራቸው እንደምትደግፍ ተናግረዋል፡፡
የካናዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክሪስቲያ ፍሪላንድ ‹‹ካናዳ ለጉዋይዶ ሙሉ ድጋፏን ትሰጣለች፤ይህ ለቬንዙዌላና ለዜጎቿ መልካም አጋጣሚ ነው›› ብለዋል፡፡ በማኑኤል ሎፔዝ ኦብራዶር የምትመራው ሜክሲኮ ከቬንዙዌላ ጋር ያላት ግንኙነት እንደማይቀየር ስታሳውቅ፤ ኩባና ቦሊቪያ በመሪዎቻቸው በኩል ማዱሮን ‹‹እኛ ክንዳችንን ሳንንተራስ አንተን ከዙፋንህ ማንም አይነቀንቅህም›› በማለት ለሶሻሊስቱ አጋራቸው ድጋፋቸውን ገልጸዋል፡፡
ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ ግን ይህ ሁሉ እየሆነ ባለበት ወቅት ላይ እንኳ ማድረግ የመረጡት ከትልቋ የንግድ አጋራቸው ከአሜሪካ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ማቋረጥና በካራካስ የሚገኙ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችም በ72 ሰዓታት ውስጥ አገሪቱን ለቀው እንዲወጡ ማዘዝ ነው፡፡ አሜሪካ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት በላቲን አሜሪካ ቀጣና የነበራትን ጣልቃ ገብነት በማውሳት የአካባቢው ፖለቲከኞች ድጋፋቸውን እንዲሰጧቸውም ተማፅነዋል፡፡ በፕሬዝደንታዊ ቤተ-መንግሥቱ አካባቢ ለተሰበሰቡ ቀይ ለባሽ ደጋፊዎቻቸው ‹‹እነ አሜሪካን አትመኗቸው! እነርሱ ጥቅምና የቬንዙዌላን ነዳጅና ወርቅ ለመዝረፍ ያሰፈሰፈ ገደብ የለሽ ፍላጎት እንጂ ወዳጅና ታማኝነት የላቸውም›› በማለት ነግረዋቸዋል፡፡
ይሁን እንጂ አሜሪካ በውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቷ በኩል ኒኮላስ ማዱሮ የሚባል ሰው በቀድሞ የቬንዙዌላ ፕሬዝደንትነቱ ብቻ የማውቀው በመሆኑ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን የማቋረጥና የማስቀጠል ስልጣን የለውም የሚል ምላሽ ሰጥታለች፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማይክ ፖምፔዎ የቬንዙዌላ ጦር የቬንዙዌላውያንን እንዲሁም በአገሪቱ ውስጥ የሚኖሩ አሜሪካውያንን ደህንነት እንዲያስጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ በቬንዙዌላ በሚኖሩ አሜሪካውያን ላይ የደህንነት ስጋት በሚፈጥር ማንኛውም አካል ላይ አሜሪካ ተገቢ እርምጃ እንደምትወስድም አስጠንቅቀዋል፡፡ አሜሪካ ከቬንዙዌላ ጋር የሚኖራትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትም በ ‹‹ጊዜያዊው ፕሬዝደንት›› ሁዋን ጉዋይዶ በኩል እንደምታ ከናውንም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡
የቬንዙዌላ የመከላከያ ሚኒስትር ጀኔራል ቭላድሚር ፓድሪኖ ሎፔዝ በትዊተር አድራሻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፣ የአገሪቱ ጦር ኃይል ራሱን ፕሬዝደንት ነኝ ብሎ ላወጀ ሰው እውቅና እንደማይሰጥ በመግለፅ ለፕሬዝደንት ማዱሮ ያላቸውን ድጋፍ አሳይተዋል፡፡
እ.አ.አ በ2013 የቀድሞውን ፕሬዝደንት ሁጎ ቻቬዝን ሞት ተከትሎ ወደ ስልጣን የመጡትና የሩስያው ፕሬዝደንት የቭላድሚር ፑቲን አጋርና ወዳጅ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ ከአገሪቱ ጦር ድጋፍ አላቸው፡፡ ወደስልጣን የመጡትም በጦሩ ድጋፍና ይሁንታ ሲሆን ከ2017 ጀምሮ የተቀሰቀሰባቸውን ከባድ ተቃውሞ እያስታመሙ ወንበራቸውን አስጠብቀው የቆዩትም በጦሩ እገዛ ነው፡፡
ለበርካታ ዓመታት የተጠራቀሙና ስር የሰደዱ የምጣኔ ሀብትና የፖለቲካ ጥያቄዎች እንዲሁም ድንገተኛ የመንግሥት እርምጃዎች አገሪቱ በአሁኑ ወቅት እያስተናገደችው ለምትገኘው ሕዝባዊ ተቃውሞ እንደዳረጓት በስፋት ይገለፃል፡፡ ለሕዝባዊ ተቃውሞው ድንገተኛ ምክንያት (Immediate Cause) ተደርጎ የሚወሰደው ግን የሀገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እ.አ.አ በ2017 ያሳለፈው ውሳኔ እንደሆነ ይነገራል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተቃዋሚው የፖለቲካ ማኅበር የሚመራውን የአገሪቱን ኮንግረስ ስልጣን የነጠቀ ውሳኔ ማሳለፉን ተከትሎ ተቃዋሚዎች ‹‹ግልፅ የሆነ አምባገነንነት ነው›› ሲሉ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ በጥብቅ አወገዙት፡፡ ከዚያ ቀደም ብሎም በጥር 2016 ፍርድ ቤቱ ሦስት የተቃዋሚና አንድ የገዢው ፓርቲ አባላት የሆኑ ሕግ አውጪዎችን ምርጫ እንዲታገድ ማድረጉ በተቃዋሚ ፖለቲከኞች ዘንድ ቅሬታ አሳድሯል፡፡ የአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን በአገሪቱ ሊደረግ የነበረውን ምርጫ እንዲራዘም መወሰኑ ደግሞ ቅሬታው ወደ ቁጣ እንዲያድግ ምክንያት ሆነ፡፡
ይባስ ብሎም የአገሪቱ መንግሥት ዋነኛ ተቃዋሚ መሪ የሆኑትና ሁለት ጊዜ ለፕሬዝደንትነት ተወዳድረው ለጥቂት የተሸነፉት ሄንሪኬ ካፕሪልስ ለ15 ዓመታት ከፖለቲካዊ እንቅስቃሴያቸው እንዲታገዱ መንግሥት ውሳኔ ሲያሳልፍ በቋፍ ላይ የነበረው የአገሪቱ ሕዝብ ቁጣ ገንፍሎ የዋና ከተማዋ ካራካስ ጎዳናዎች በተቃውሞ ሰልፈኞች ተጥለቀለቁ፡፡
የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔና የተቃዋሚው መሪ እገዳ ለቬንዙዌላ ሕዝባዊ ተቃውሞ ድንገተኛ ምክንያት ተደርገው ተቆጠሩ እንጂ፣ ቬንዙዌላውያን ከአገዛዙ ጋር ሆድና ጀርባ ከሆኑ ሰንብተዋል ይባላል፡፡ እንዲህ እንዳሁኑ ግልፅና ሰፊ አይሁን እንጂ ሕዝቡ በመንግሥት ላይ ተቃውሞ ማሰማት የጀመረው በዚያች አገር የኑሮ ውድነት ሰማይ በነካበት ወቅት ነው፡፡ የአገሪቱ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ኮሚሽን በጥር 2017 ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት፣ የአገሪቱ የዋጋ ግሽበት 679 ነጥብ 73 በመቶ ደርሶ ነበር፡፡
የዓለም የገንዘብ ድርጅት (International Monetary Fund-IMF) በበኩሉ በዚያው ዓመት የአገሪቱ የዋጋ ግሽበት እስከ 720 ነጥብ አምስት በመቶ፣ በ2018 ደግሞ 2068 ነጥብ አምስት በመቶ እንደሚሆን ገልጾ ነበር፡፡ ይባስ ብሎም ድርጅቱ በ2019 የአገሪቱ አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት 10 ሚሊዮን በመቶ እንደሚሆን በቅርቡ ትንበያውን ማስቀመጡ ይታወሳል፡፡
ይህ የዋጋ ግሽበት የመንግሥትን ካዝና ባዶ አስቀርቶ ምግብና መድኃኒት እንኳ ከሌሎች አገራት ለማስገባት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ስለመደረሱም ተገልጿል፡፡ ቀውሱ በአገሪቱ የጤና ዘርፍ ላይ ያሳደረው ተፅዕኖ ከሁሉም የከፋ እንደሆነ ሲነገር፣ መድኃኒቶችና የሕክምና መሳሪያዎች በመንግሥት ሆስፒታሎች የውሃ ሽታ ሆነዋል፡፡ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ቬንዙዌላውያንም እየተባባሰ የመጣውን ምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ በመሸሽ እየተሰደዱ ይገኛሉ፡፡
የኒኮላስ ማዱሮ መንግሥት ግን አሁንም የአገራቸውን ቀውስ ‹‹የኢምፔሪያሊስቶች ሴራ ነው›› በማለት ቀውሱን በምዕራባውያን ላይ እያሳበቡ ነው፡፡ የአካባቢው አገራትም ተቃውሟቸውን እየገለፁ ይገኛሉ፡፡ ባለፈው መስከረም ወር ሰባት አገራት ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ በሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዲጠየቁ ለዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት (International Criminal Court_- ICC) አቤቱታ አቅርበዋል፡፡
ምንም እንኳን በርካታ የላቲን አሜሪካ አገራትና ካናዳ እውቅና እንደማይሰጡ ቀድመው ቢገልጹም፣ ፕሬዝደንት ኒኮላስ ማዱሮ ተጨማሪ ስድስት ዓመታትን በስልጣን ላይ የሚቆዩበትን የሥልጣን ጊዜያቸውን ከሁለት ሳምንታት በፊት ጀምረዋል፡፡ የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሬዝደንት ማዱሮ ተጨማሪ ስድስት ዓመታትን በስልጣን ላይ እንዲቆይ ያስችለኛል ካሉትና አሸንፌያለሁ ብለው ሁለተኛ ዙር የሥልጣን ጊዜያቸውን ሕጋዊ ሽፋን ከሰጡበት ምርጫ ራሱን እንዳገለለ ይታወሳል፡፡
አሁን ጥያቄው ‹‹እንዲህ ዓይነት ለጆሮ የሚከብድ የዋጋ ግሽበት ያላትን አገር እመራለሁ እያሉ የሚገኙትና ከጎረቤታቻቸው ከባድ ተቃውሞ የገጠማቸው ኒኮላስ ማዱሮ ከዚህ ማዕበል ይተርፋሉ ወይ?›› ነው፡፡ ጊዜ ምላሹን ይሰጣል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 17/2011
አንተነህ ቸሬ