አንድ ጊዜ መሶበወርቅ፣ወርቆች ወደ ተሰበሰቡበት ሄደና “እናትና አባቴ ወርቆች ናቸው፤ እኔም ወርቅ ነኝ” አለ፤ በዚህ ጊዜ ወርቆች በመደናገጥ “አንተ ግዙፍ ነህ፣ ምንህም እኛን አይመስልም” ይሉታል። እሱም “ስሜ እንኳ መሶበወርቅ ነው ከስሜ እንደምታዩት የወርቅ ዘር ነኝ” ብሎ ተከራከረ። በዚህ ጊዜ ወርቆች ተማከሩና “እንግዲያውስ የእኛ ዘር ከሆንክ ዕሳት ጋር እንሂድ፤ ከዛም እንደኛ ሸንቃጣ ሁን” አሉት። መሶበ ወርቅም አላቅማማም አብሯቸው ሄደ።
ዕሳቱ ጋር ደርሰው ወርቆቹ ሲዋኙ ምስኪኑ መሶበወርቅ ግን ዕሳቱ በልቶት ተቃጥሎ ነደደ። ለቅሶ ለመድረስ የመሶበወርቅ ዘመዶች ሲመጡ ለካ ስሙ እንጂ የወርቅ ዘር ያስመሰለው እሱ የነ ሰበዝ እና የነ አክርማ ልጅ ነበር።
እኛ ኢትዮጵያውንም አንዳንድ ጊዜ ያልሆንነውን ሆነን እንታያለን። እኛ በሽታ አይነካንም የምንለው ነገር እንደ መሶበወርቅ ለመንደድ እንዳይሆን ልንጠነቀቅ ይገባል። “የፈጣሪ ሀገር ነን” የሚል ትምክህትም ከዕሳት አያወጣም፤ ሁሉም ሀገር በፈጣሪ የተሠራ መሆኑ እርግጠኛ ሆነን ሳለ በከንቱ ተረት ታብየን መኩራራት ከመሶበወርቅ ታሪክ አለመማር ነው፤ ስንቱን ስሙ ገደለው ተብለን የትውልድ መተረቻ ከመሆንም አንድንም፤ ይልቅ ህይወት በምርጫ የተሞላች ናትና ተገቢውን ውሳኔ ብንወስን ይበጃል።
እርግጥ ነው ለአብዛኞቻችን ቤት መቀመጥ አይመቸንም፤ የስንቱስ ቤት ለማደሪያ ለመዋያነት ይሆናል? ደግሞም በዚህ የሩጫ ዘመን መቀመጥ እውነትም አያሳምንም፤ ግን የእከሌን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም ነውና ነገሩ በሌሎች አገራት ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ እና ስቃይ በሀገራችን እንዳይደገም ኃላፊነታችንን እንወጣ። ምክንያቱም ብልህ ሰው ከሌሎች ይማራል። “ሰነፍ ሰው ደግሞ በራሱ ህይወት ዋጋ ከፍሎ ይማራል።” ተብሎ ተነግሮናልና።
ሌላው ደግሞ ወርቅ በዕሳት ተፈትኖ ወርቅነቱ እንደሚመሰከር ሁሉ ጠንካራ ሰዎችም እያንዳንዱን መጥፎ ነገር ለጥሩ ዕድል በመጠቀም ጥንካሬውንም፣ ብልሃቱንም ይገልፃል።
ስለዚህ አሁን ዓለም ያለችበትን ድባብ (ወሸባ) መግባት (Quarentine) ወይም በቤት መቀመጥ ለጥሩ ዕድል መጠቀሚያነት ማድረግ እንችላለን። ለማንበቢያ፣ ማሰቢያ፣ መፃፍያ እና ለሌሎችም። ክፉ ቀን ያልፋል፣ ፅኑ ሰዎች ግን ያልፉታል (ዶ/ር ሮበርት ኤች. ሹለር) በአገራችንም ለክፉ ቀን እና ለወንጭፍ ድንጋይ ዝቅ ማለት የኖርንበት ልማድ ነው።
እየኖርን ነው ማለት ህይወት አለን ማለት ሊሆን ይችላል። ግን ትርጉም ያለው ህይወት ማለት የነፍስን ጥሪ መስማት ከራስ አልፎ ለሌላውም መኖርም ጭምር ነው። ታድያ መብላት፣ መጠጣት እና መዋለድ እውነት ይህ ብቻ ትርጉም ያለው ህይወት ነው? ይሄንን እንስሳትም አያደርጉትም?
ውጥረት እና ጭንቀት
በዚህ አስከፊ (አስቸጋሪ) ወቅት እራሳችንን መንከባከብ እና ከበሽታ መጠበቅ ወሳኝ መሆኑን መገንዘብ ይኖርብናል።ይሄም ሲባል አካላዊ ጤንነታችን ላይ ብቻ ሳይሆን ማተኮር ያለብን የአዕምሮ ጤናችንንም በተገቢው ሁኔታ መጠበቅ ላይ ትኩረት ልናደረግ ይገባል። የአዕምሮ ጤንነታችን በቀላሉ በተለያዩ ምክንያቶች ሊረበሽ ይችላል። በተለይ ህይወታችን ላይ ትልቅ ተጽዕኖ የሚያሳድር ወይም የጤና ሁኔታችንን አደጋ ላይ የሚጥል አዲስ ሁኔታ በሚኖርበት ጊዜ በበለጠ ሁኔታ ተጋላጭ ልንሆን እንችላለን።
ብዙ ሰዎች በዚህ አይነት ጊዜ ላይ ውጥረት እና ጭንቀት በሚያመጣ ሀሳብና ስሜት ይዋጣሉ። ይሄንን ደግሞ በተገቢው መንገድ መቆጣጠር ወይም መፍታት ካልተቻለ የከፋ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል። እነዚህ ስሜቶች በበሽታው እያዛለው በሚል ፍርሀት፣ ስለሚወዱት ሰው ጤና በመጨነቅ፣ ከጓደኞች ጋር መገናኘት አለመቻል፣ የወደፊት ዕቅዶች ላይ መሰናክል ይሆናል ብሎ በማሳብ፣ ይህ ክስተት (ወረርሽኝ) መቼ ይሆን የሚያበቃው በሚል ውዝግብ እና በመሳሰሉ ሀሳቦች የሚመጡ ናቸው።
እያንዳንዱ ሰው በዚህ የከፋ ጊዜ ላይ የሚሰማቸው የውጥረት/የጭንቀት መጠን እና የምላሽ ዘዴ አንድ አይደለም። በአብዛኛውን ጊዜ ወረርሽኝ በሚከሰትበት ወቅት ለጭንቀት እና ውጥረት በበለጠ ደረጃ ተጋላጭ የሚሆኑት መካከለኛ እና ከዛ በላይ እድሜ የሆኑ፣ ቀድሞም ከአዕምሮ ጋር የተያያዘ ህመም ያለባቸው፣ ከበፊት ጀምሮ አስከፊ በሽታ የነበረባቸው፣ በዚህ አይነት ጊዜ ላይ በበሽታው የተጠቁ ህዝቦችን የሚረዱ እና የመሳሰሉት ናቸው።
እነዚህ የሚከሰቱት ለውጦች የተለያዩ ደስ የማይሉ ስሜቶችን በአንድ ጊዜ እንዲሰማን ሊያደርጉ ይችላሉ። ይሄም ቤት ውስጥ ሆነን በቀላሉ መሥራት በምንችላቸው ነገሮች ልንቆጣጠራቸው እንችላለን። እነሱም በየግለሰቡ ፍላጎት ላይ ተመርኩዘው የሚሰሩ ናቸው። ለምሳሌ፡- ቤት ውስጥ ስፖርት በመሥራት ሊሆን ይችላል፣ ለጓደኛዎት ወይም ለዘመድ በመደወል ሊሆን ይችላል፣ ከቤተሰብ ጋር ጨዋታዎችን በመጫወት ሊሆን ይችላል፣ ውጥረቱ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ለባለሙያ ደውሎ በማናገር ሊሆን ይችላል እና የመሳሰሉት ነገር ግን የሚሰማን ስሜቶችን ችላ ካልን ከጊዜ ወደ ጊዜ ያለውን ችግር እንዲባባስ ሊያደርግ ይችላል። በዚህ ምክንያት ቀደም ሲል ከነበረው በበለጠ ደረጃ ጉዳት በማድረስ ግለሰቡን ለሌላ የከፉ ችግሮች ተጋላጭ ያደርገዋል።
ካለፈው ምን እንማር?
ቀደም ሲል እንደተጠቀሰው፣ የትኛውም አይነት ወረርሽኝ ሲከሰት ውጥረት እና ጭንቀት ይሰማን ይሆናል። የእኛ ትኩረት መሆን ያለበት ግን ከቀዳሚው ወረርሽኝ ምን መማር አለብን የሚለውንና ምን ብናደርግስ ተመሳሳይ ስህተት ከመፈፀም እራሳችንንም ሆነ ማህበረሰባችንን እንታደጋለን የሚለው ላይ ነው።
የቀድሞው ወረርሽኝ እንደ ህዳር በሽታ እና ኢቦላ ሲከሰቱ የጭንቀት እና የውጥረት ስሜቶች የተፈጠሩበት ዋነኛ ምክንያቶች በበሽታው የመያዝ ከፍተኛ ዕድል ያላቸው ቅርብ የምንላቸውና የምንወዳቸውን ሰዎች ያጠቃብናል የሚል ሥጋት፣ በበሽታው የተጠቁ ሰዎች አካባቢ የምንኖር ከሆነ እንዲሁም ገና ለገና በበሽታው እንጠቃለን የሚል ሥጋት በመኖሩ ነው። ሆኖም ወረርሽኝ በሚከሰትበት ጊዜ የውጥረት እና ጭንቀት ስሜት የተለመዱ ቢሆንም ሰዎቹ ስለ ወረርሽኙ ትክክለኛና እውነታ ላይ የተመሰረተ መረጃ ካላገኙ እነዚህ ስሜቶች አሉታዊ በሆነ መልኩ እየጨመሩ ይመጣሉ።
ስለ ወረርሽኙ ትክክለኛ መረጃ ከማግኘት ጋር ጎን ለጎን ጭንቀትንና ውጥረትን እንዴት መቋቋም እንደሚቻል መንገዶችን መገንዘብና ማጤኑ ተመራጭ ነው። ይህ ካልሆነ ግን የበለጠ ሁኔታዎችንና የግለሰቦችን የአዕምሮ ጤናንም እንኳ ሳይቀር ሊያውክ ይችላል። ከላይ የተጠቀሱትን ጭንቀቶች እና ውጥረቶች የመቋቋም ዘዴዎች ግለሰቡ እና ማህበረሰቡ በእያንዳንዱ ወረርሽኝ ሊጠቀሙባቸው የሚችሉ አንዳንድ ምሳሌዎች ናቸው።
ስለዚህ በልዩነት ማሰብ መቻል አለብን። ሶቅራጥስ እንዳለው ማሰብ የሚለየው ሰውን ከእንስሳ ሳይሆን ሰውን ከሰው ነው፤ ተረባርበን ከጥፋት ራሳችንን፣ ሀገራችንን እንዲሁም መጪውን ትውልድ እንታደግ። ይሄን ጊዜ አልፎ ነበር ብለን እንድናወራው አብዝተን እናስብ። የተባልነውንም እንስማ፤ እንተግብር።
“ለመሰብሰብ ጊዜ አለው፤ ለመተቃቀፍ ጊዜ አለው፡ ከመተቃቀፍም ለመራቅ ጊዜ አለው፤” (መጽሐፈ መክብብ 3፡5)
“ወረርሽኝ ዕሳት ሲሆን ማገዶ እናንተ ናችሁ፤ ዕሳቱ ማገዶ አጥቶ ይከስም ዘንድ በተናጠል ቆዩ” (0ምር ኢብኑል አስ [ረ.0])
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 16 ቀን 2012
ሀናን ሁሴን፣ ሣራ መሐመድ፣ መልከብርሃን ብርሃኑ
(ሳይክ-ኢን-አክሽን ክለብ፤ ሳይኮሎጂ ት/ቤት፣አ.አ.ዩ)