በተፈጥሮ ሀብቷ ትታወቃለች፡፡ በአልማዝ፣ ወርቅ፣ ታንታለም፣ እና በመሳሰሉት የከበሩ ማዕድናት ባለጸጋ ናት፡፡ በአሁኑ ወቅት ለስማርት የሞባይል ቀፎዎች እና ለኤሌክትሪክ መኪናዎች በግብዓትነት የሚያገለግሉ ወሳኝ ማዕድኖች በስፋት ይገኙባታል፡፡ ለዓለም ገበያ ከሚቀርበው የኮባልት ማዕድን ሁለት ሦስተኛውን(2/3) የምታቀርበውም ይህችው ሀገር ናት፤ አፍሪካዊቷ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፡፡
ሀገሪቱ የቱንም ያህል ታዲያ በሀብት ማማ ላይ ብትቆም/ብትገኝም፣ ዜጎቿን መታደግ ሳትችል ግማሽ ምእተ ዓመት አልፏል፡፡ አንዱ መሪ ሌላውን እየገደለ እና እየገለበጠ ጡንቻውን ሲያሳይባትና ዜጎቿን ለእርስ በእርስ ጦርነት፣ ለእልቂት፣ ረሀብ ወዘተ ሲዳርግ የቆየባት በመሆኗም ትታወቃለች፡፡ ስር የሰደደ ሙስና፣ የተመጣጣነ ምግብ እጥረት፣ ሴት ልጆቿ በአስገድዶ መድፈር ክፉኛ የሚሰቃዩባት ሀገር ናት፡፡
ቀድሞ ዛየር በመባል ትታወቅ የነበረችውና የምዕራብ አውሮፓን ያህል ስፋት ያላት ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ከቤልጂየም ቅኝ ግዛት ነጻ ከወጣች እአአ ከ1960 አንስቶ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ተደርጎባት አያውቅም፡፡ ይልቁንም በመፍንቅለ መንግሥትና አንዱ ሌላውን በመግደል ነው የመሪነት ሥልጣን ሲጨበጥባት የኖረችው፡፡
ለአብነት፣ የሙቡቱ ሴሴኮን መንግሥት በመገልበጥ እአአ በ1997 ወደ ፕሬዚዳንትነት የመጡት የፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ አባት ላውሬንት ካቢላ፤ በ2001 መገደላቸውን ተከትሎ ወደ ፕሬዚዳንትነት የመጡት ልጃቸው ጆሴፍ ካቢላ ሀገሪቱን ለ18 ዓመታት መርተዋል፡፡ በካቢላ አስተዳደር ሀገሪቱ ወግ ወጉን በመያዝ እአአ በ2006 እና በ2011 ሁለት ምርጫዎችንም አካሂዳለች፡፡ ይሁንና ምርጫዎቹ ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ እንዲሉ የጆሴፍ ካቢላን ፕሬዚዳንትነት ከማጽናት ባለፈ የኮንጎሊዞችን የዴሞክራሲያዊ ምርጫ ጥማት ለማርካት የፈየዱት የለም፡፡
ከዚህ ይልቅ ምርጫዎቹን ተከትሎ በተቀሰቀሱ ደም አፋሳሽ አመጾች ሀገሪቱ ልጆቿን ተቀምታለች፡፡ መረጋጋት የሌለባት ሀገርም ሆናለች፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥም ሆና ግን የሀገሪቱ ህዝብ ተስፋ ሳይቆርጥ የዴሞክራሲያዊ ምርጫ ጥማቱን ለማርካት በቀጣይ የሚካሄደውን ምርጫ በጉጉት ሲጠበቅ ቆይቷል፡፡
ይሁንና የፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ የፕሬዚዳንትነት ዘመን እአአ በ2016 ቢያበቃም፣ ምርጫው ሳይካሄድ ሁለት ዓመታትን አሳልፎ ከስንት ውዝግብ በኋላ ለሶስተኛ ጊዜ ባለፈው ታህሳስ ወር መጨረሻ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫው መካሄዱ ይታወሳል፡፡ ሆኖም ከኢቮላ ወረርሽኝ መቀስቀስና ከሌሎች የምርጫ ሥነሥርዓት መጓደሎች ጋር ተዳምሮ ብዙዎች የምርጫውን ሂደትና ጤናማነት እንዲሁም ውጤቱን እንዲጠራጠሩት ማድረጉን ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ በዚህ ጥርጣሬ ውስጥ ያለው የምርጫ ሂደት ውጤትም በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ይፋ ሳይደረግ የቆየው የመጀመሪያው የምርጫው ውጤት ባለፈው ሳምንት ይፋ መደረጉ ይታወሳል፡፡
በውጤቱ መሰረትም በምርጫው የተቃዋሚው የዴሞክራሲና ማህበራዊ ፕሮግረሲቭ ህብረት ፓርቲ መሪ የ55 አመቱ ፌሊክስ ቲሺሴኬዲ አብላጫ ድምጽ በማግኘት አሸንፈዋል፡፡ የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ኮሚሽነር ኮምይሌ ናንጋ ባለፈው ሀሙስ ይፋ እንዳደረጉትም፣ ፌሊክስ ቲሺሴኬዲ ድምጽ ከሰጡት የሀገሪቱ ዜጎች የ38ነጥብ5 በመቶውን ድምጽ ማግኘታቸውን ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በዘገባቸው አመልክተዋል፡፡
በዚህ የምርጫ ውጤት ፌሊክስ ቲሺሴኬዲ ድምጽ ለመስጠት ከተመዘገበው ህዝብ የሰባት ሚሊዮኑን፣ በምርጫው ቅድመ ግምት እንደሚያሸንፉ ሲጠበቁ የነበሩት ሌላው የተቃዋሚ መሪ ማርቲን ፋዩሉ 6ነጥብ 4ሚሊዮኑን እንዲሁም የጆሴፍ ካቢላ ፓርቲ ተወዳዳሪ አማኑኤል ሻዶው 4ነጥብ4 ሚሊየኑን ድምጽ አግኝተዋል፡፡
ይህ የመጀመሪያ ደረጃ ውጤት በአስር ቀናት ከተረጋገጠ ሚስተር ቲሺሴኬዲ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ነጻነቷን ከቤልጂየም ከተቀዳጀች እአአ ከ1960 ወዲህ በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡ የመጀመሪያው መሪ ያደርጋቸዋል፡፡ ላለፉት 18 ዓመታት ሀገሪቱን በፕሬዚዳንትነት የመሩት ካቢላም ስልጣናቸውን በሰላማዊ ሽግግር ያስረክባሉ፡፡
ቲሺሴኬዲ በፓርቲያቸው ዋና መሥሪያ ቤት ለደጋፊዎቻቸው በሰጡት መግለጫ ጆሴፍ ካቢላ ከዚህ በኋላ በተቀናቃኝነት እንደማይታዩ ይልቁንም በሀገሪቱ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ውስጥ የለውጥ አጋር እንደሚሆኑ አስታውቀዋል፡፡ ድህነትን መዋጋት ቅድሚያ የሚሰጡት ተግባር መሆኑንም አረጋግጠዋል፡፡
ካቢላም በአጸፋው በከፍተኛ አማካሪያቸው ባርናቤ ኪካያ ቢን ካሩቢ በኩል የምርጫውን ውጤት መቀበላቸውን አስታውቀዋል፡፡ አማካሪው ‹‹የእኛ እጩ ባለማሸነፉ ቅር ተሰኝተናል፤ የኮንጎ ህዝብ ግን የሚፈልገውን መርጧል፤ ዲሞክራሲ አሸንፏል » ሲሉ የምርጫውን ውጤት በጸጋ መቀበላቸውን ለሮይተርስ መግለጻቸውን የዘጋርድያን ዘገባ አመልክቷል ፡፡
የካቢላ አማካሪ ይህን ይበሉ እንጂ የምርጫው ውጤት በተለያዩ ወገኖች ዘንድ የተለያየ ስሜት ማሳደሩን ቀጥሏል፡፡ ተቺዎች ካቢላ በምርጫው ውጤት ውስጥ በእጅጉ መፈትፈታቸውን እያመለከቱ ይገኛሉ፡፡ ካቢላ እንደ ሩሲያው ፕሬዚዳንት ፑቲን አይነት ፊልም ሰርተዋልም ይሏቸዋል፡፡ ፑቲን በአንድ የምርጫ ወቅት በድጋሚ መመረጥ እንደማይችሉ ሲያውቁ በዚያም በዚያም ብለው ሜድቬዴቭን ወደ ፕሬዚዳንትነት እንዳመጧቸው፣ ቀጥለውም ራሳቸው መምጣታቸውን ጠቅሰው፣ ካቢላም ይህን ለመደግም መሞከራቸውን ተናግረዋል፡፡ በማእካላዊ አፍሪካ በርካታ መጻህፍትን በመድረስ የሚታወቁት ክሪስ ቤርዎትስ፣ ግን ኮንጎ ሩሲያ አይደለችም፤ ካቢላም ፑቲን ናቸው ብዬ አላስብም ሲሉ የካቢላን አካሄድ አብጥልጥለውታል፡፡ የሀገሪቱ የምርጫ ህግም ካቢላ ከዚህ በኋላ ወደ ፕሬዚዳንትነት እንዲመጡ የሚፈቅድ አለመሆኑን ዘገባዎቹ ይጠቁማሉ፡፡
የአሸናፊነት ግምት ተሰጥቷቸው የነበሩት የሌላኛው የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ማርቲን ፋዩሉ የምርጫውን ውጤት ከእውነታው ጋር የማይጣጣም ሲሉ ማጣጣላቸውን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡ ‹‹የኮንጎ ህዝብ ይህን የማጭበርበር ድርጊት በፍጹም አይቀበለውም፤ ፌሊክስ ቲሺሴኬዲን 7 ሚሊየን ህዝብ አልመረጠውም፤ ይህን ህዝብ ከየትስ ሊያገኝ ይችላል?›› በማለት የምርጫውን ውጤት እንደማይቀበሉት አስታውቀዋል፡፡
ፈረንሳይም የምርጫውን ውጤት አለመቀበሏን ለፋዩሉ ድጋፍ እንደምታደርግ በማረጋገጥ አስታውቃለች፡፡‹‹በምርጫው ውጤት ላይ ግልጽነት ሊኖር ይጋባል፤ ውጤቱ ከሚጠበቀው በተቃራኒ ነው›› ሲሉ የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬስ ሌ ደሪያን ለበቢሲ የዜና ምንጭ አስገንዝበዋል፡፡ ሚስተር ፋዩሉ ኮሮጆ መገልበጡን በመጥቀስ፣ በአካባቢው ቁልፍ ሚና ያላትን የፈረንሳይን ድጋፍ እየጠየቁ መሆናቸውን ያመለከተው አልጀዚራም ይህንን የቢቢሲን ዘገባ አጠናክሮታል፡፡
40ሺ ታዛቢዎችን በማሰማራት ስለምርጫው ውጤት ተጨባጭ መረጃ እንዳላት የምትጠቅሰው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን፣ ይፋ የተደረገው ውጤት እሷ ካደረጀችው መረጃ ጋር በፍጹም የተራራቀ ነው እያለች ትገኛለች፡፡የቢቢሲው ተንታኝ ፈርጋል ኬአኔ በኮንጎ ከቆየው የፖለቲካ ሁኔታ አንጸር ሲታይ የትኛውንም ውጤት በጸጋ መቀበል እንደሚያዳግት ይናገራል፡፡
የአባታቸውን ፓርቲ የወረሱት ቲሺሴኬዲ የ55 ዓመቱ ቲሺሴኬዲ ሀገር ለመምራት የሚያስችል ምንም ልምድ እንደሌላቸው በመጥቀስ፣ የአባታቸውን ያህል ተክለ ሰውነት የላቸውም›› ሲሉ ይተቿቸዋል፡፡ የፌሊክስ ቲሺሴኬዲ ፓርቲ የዴሞክራሲ እና ማህበራዊ ተራማጅ ህብረት የቀድሞ ዋና ጸሀፊ ቫልንታይን ሙባኬ ለዘጋርዲያን በሰጡት አስተያየት ይህንኑ ነው ያረጋገጡት፡፡ ሙባኬ አባትዬው የሀገሪቱ ታላቅ ሰው እንደነበሩ በመጥቀስ፣ ቲሺሴኬዲ ግን በእዚህ በኩል ውስንነት እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡
የመጀመሪያው የምርጫ ውጤት ይፋ በሆነ በአስር ቀናት ውስጥ ፓርቲዎቹ አሉን የሚሏቸውን ቅሬታዎች ማቅረብ የሚችሉበት የህግ አግባብ አለ፡፡ ማርቲን ፋዬሉም ጉዳዩን ለፍርድ ቤት ማቅረባቸውን የአልጀዚራ ዘገባ ይጠቁማል፡፡ የፋዩሉ የምርጫ ዘመቻ መኮንን ፊዴሌ ባባላ ለጋዜጠኞች ፤ ፋዩሉ ከመራጩ ህዝብ የ62 በመቶውን ድምጽ ማግኘታቸውን በመጥቀስም ነው ክስ የመሰረቱት ፡፡
ውጤቱን ተከትሎ አመጽ እንዳይቀሰቀስ በሚል አብያተ ክርስቲያናትና ሲቪል ማህበረሰቡ ህብረተሰቡ እንዲረጋጋ ጥሪ እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡ መንግሥትም አድማ በታኝ የፖሊስ ኃይል በየአካባቢው አሰማርቷል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤትም የሀገሪቱ ዜጎች እና የጸጥታ ኃይሎች የምርጫው ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ በሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖር እንዲሰሩ አሳስቧል፡፡
ቲሺሴኬዴ ከምርጫው ውጤት ይፋ መሆን በኋላ ለካቢላ ያላቸውን አድናቆት የገለጹበት መንገድ በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ በደግ እንዳልታየም የአልጀዚራ ዘገባ ይጠቁማል፡፡ ንግግሩ በፋዩሉ ደጋፊዎች ዘንድ ጥርጣሬን ያጫረ ሲሆን፣ ደጋፊዎቹ ከምርጫው ውጤት በስተጀርባ አንዳች ነገር አለ ብለው እንዲገምቱ አድርጓቸዋል እየተባለ ነው፡፡
የአፍሪካ የስጋት አማካሪው /ኢኤክስ ኤክስ/ ሥራ አስፈጻሚ ዳይሬክተሩ ሮበርት ቤሴሊንግ ‹‹ካቢላ የፓርቲያቸውን እጩ ወደ ስልጣን ማምጣት ውስጥ ያልገቡት በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ውግዘት እንዳይደርስባቸው እንዲሁም በህዝቡ ዘንድ አመጽ እንዳይቀሰቀስ ስለፈለጉ ነው ››ይላሉ፡፡ ከዚህ ይልቅ የሥልጣን መጋራት እንዲኖር ለማድረግ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ሁለት መክፈልን እንደመረጡ ይገልጻሉ፡፡
አንዳንድ ወገኖች ካቢላ በምርጫው እንዲወዳደሩ ያቀረቧቸው ራማዛኒ ሻዳሬይ በዚህም በዚያም ተብሎ እንዲያሸንፉ ይደረጋል ብለው ገምተው እንደነበር ዘገባው ጠቅሶ ይህ አለመሆኑም ሌላው የምርጫው ውጤት አስገራሚ እንዲሆን ያደረገ ምክንያት መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡
በምዕራብ አፍሪካ የምርምር ትንትና የኢኮኖሚ ደህንነት ክፍል ተንታኝ አዴሊን ቫን ሆቴ የምርጫ ውጤት ይፋ ሳይደረግ መቆየቱ መንግሥት ከቲሺሴኬዲ ጋር ከበስተጀርባ አንዳች ድርድር ውስጥ ገብቶ ነበር የሚያሰኝ ጥርጣሬ አሳድሮ መቆየቱን ይጠቅሳሉ፡፡
በሀገሪቱ ከቅድመ ምርጫው ጀምሮ ውጤት ከተገለጸም በኋላ የሚታየው ሁኔታ ሰፊዋን የማእከላዊ አፍሪካ ሀገር የአመጽና ቀውስ ዑደት ውስጥ እንድትቆይ ያደርጋል ያለው የዘጋርዲያን ዘገባ፣ የምርጫው ውጤት ላይ የተነሳው ውዝግብ የቀውስ ታሪክ ያልተለያት ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የተጣለው ተስፋ እንዲመነምን የሚያደርግ መሆኑንም አመልክቷል፡፡
ከየአቅጣጫው የሚወጡት ዘገባዎች ተመራጩ ፕሬዚዳንት በቀጣይ ስለሚያከናውኑትና ስለሚገጥማቸው አንዳች ነገር ከማለት ይልቅ በውዝግቡ ላይ ማተኮራቸው ቀጣዩ የዲሞክራቲክ ሪፐቡሊክ ኮንጎ እጣ ፈንታ ምን ይሆን? ያሰኛል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 7/2011
ኃይሉ ሣህለድንግል