ኑሮ እንደየ ዘመኑና እንደየ ሁኔታው ይለያ ያል።አንዳንድ ዘመን የተባንና ደስታ ሆኑ ህዝቦች በሀሴት ይኖራሉ።በሌላው ዘመን ደግሞ ችግሮች፤ በሽታዎችና ጦርነቶች አጋጥመው ሰዎች ህይወታቸውን በብዙ ውጣውረድና በሰቆቃ ለመግፋት ይገደዳሉ።ከሰሞኑ የተከሰተውም የኮሮና ቫይረስ ወይም በሳይንሳዊ አጠራሩ ኮቪዲ 19 የዓለምን ህዝብ አኗኗር ቀይሮታል። እንደጣሊያን በመሳሰሉ የቫይረሱ ስርጭት በተንሰራፋባቸው ሀገሮች ደግሞ ህይወት ሙሉ ለሙሉ መልኳን ቀይራለች።እንደወትሮው ከሰው ጋር መገናኘት፤ የሚወዱትን ቤተዘመድ መጠየቅ፤ ወደ መዝናኛ ስፍራዎች ማቅናት፤ መማርና መስራት ሁሉ የቅርብ ጊዜ ትዝታዎች ሆነዋል።በመንገዶችም ላይ ሰውን ማየት ብርቅ ሆኗል።የሰው ልጅ እንደብርቅዬ እንስሳ ከጎጆው ክትት ብሏል፡፡
የኮሮና ቫይረስ ዓለም ላይ ድንጋጤን ፈጥሯል።የሁሉም እንቅስቃሴ የተገደበ፤ አንዱ አንዱን በጥርጣሬ እንዲያይ ያደረገና ህይወትን ከተለመደው ገጽታዋ ውጪ እንድትሽከረከር ያደረገ የዘመናችን ክፉ ክስተት ነው።ለአብነትም በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ሰዎች በኮሮና ቫይረስ ምክንያት ያጋጠማቸውን በመጠኑ እንቃኝ፡፡
የቢቢሲዋ ጋዜጠኛ በኬንያ
ጋዜጠኛ ፊራፎሊ ዱጋሳ የቢቢሲ ኦሮምኛ ባልደረባ ስትሆን ለእረፍት ካቀናችበት ኢትዮጵያ ወደ መኖሪያዋ ናይሮቢ ኬንያ የተመለሰችው መጋቢት 7 /2012 ነበር። ፊራፎሊ ናይሮቢ ከደረሰችበት ሰዓት ጀምሮ ስላሳለፈቻቸው ሁለት አስጨናቂ ተከታታይ ቀናት እንደሚከተለው ለቢቢሲ አጋርታለች።
በናይሮቢው ጆሞ ኬንያታ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ የደረስኩት ከሰዓት 9፡30 ሲል ነበር። መንገደኞች የሰውነት ሙቀት ልኬት እየተደረገላቸው ነው። እኔም ሙቀቴን ለመለካት ተሰለፍኩ።
የሰውነት ሙቀቴ 37.7 ዲግሪ ሴሌሺየስ ሆኖ ተገኘ። ይህ ከሚጠበቀው በላይ ነበር። ከሌሎች ተለይቼ እንድቆይ ተደረኩ። ይህም ጭንቀትን ፈጠረብኝ።
‘’በበሽታው ተይዤ ይሆን? ስል እራሴን እጠይቃለሁ”። የሁለት ዓመት የእህቴን ልጅ አስይዤው ይሆን? በኢትዮጵያ ያሉ ወላጆቼን እና ጓደኞቼን ለቫይረሱ ተጋላጭ አድርጌያቸው ይሆን? እያልኩ በጣም ተጨነኩ።
ብዙ በቆየሁ ቁጥር ጭንቀቴ እና ፍርሃቴ እየጨመረ መጣ። የአየር ማረፊያ ሰራተኞች ወደ እኔ እንዳይጠጉ ተነገራቸው። መንገደኞችም አተኩረው ይመለከቱኝ ነበር።
ናይሮቢ ከደረስኩ ከአራት ሰዓታት በኋላ፤ በአምቡላንስ ወደ ኢምባጋቲ ሆስፒታል ተወሰድኩ። ይህ ሆስፒታል የኬንያ መንግሥት በኮሮና ቫይረስ የተያዙ ወይም የተጠረጠሩ ሰዎችን ለይቶ ለማቆየት እና ለማከም ያዘጋጀው ሆስፒታል ነው።
በሆስፒታሉ ኮሪደሮች ሳልፍ ሰዎች ሲስሉ እሰማ ነበር። አፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል እንዳደረኩ በብርድልብስ ተጠቅልዬ ተኛሁ። ማክሰኞ እኩለ ቀን ላይ ምርመራ ተደረገልኝ። የምርመራው ውጤት እስኪመጣ መጠበቅ ግድ ነው። በጣም አስጨናቂ ነበር።
በዚህ መካከል የኬንያ መንግሥት በኮሮና የተያዙ ሦስት ተጨማሪ ሰዎች መገኘታቸውን ይፋ አደረገ። ይህ ለእኔ በጣም አስደንጋጭ ነበር። ምክንያቱም በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡት ሰዎች የሚገኙት እኔ ባለሁበት ሆስፒታል ውስጥ ነው።
ማን ያውቃል በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጡ ሰዎች ጋር ንክኪ ተፈጥሮ ይሆናል። ምርመራውን ካደረግሁ ከ24 ሰዓታት በኋላ ውጤቱ መጣ። ረቡዕ ከሰዓት ላይ ዶክተሮች መጥተው የምርመራው ውጤት ኔጌቲቭ ወይም ቫይረሱ እንደሌለብኝ ነገሩኝ።
ይህ ትልቅ እፎይታ ነበር። ቤተሰቦቼ እና ጓደኞቼ ጋር ደውዬ እንዳይጨነቁ ነገርኳቸው። በጣም ተደሰቱ። ከሆስፒታሉ ለመውጣት በጣም ተቻኮልኩ።
ከሆስፒታሉ ወረቀት ካልተሰጠ ከቅጥር ግቢ መውጣት እንደማይቻል ሲነገረኝ፤ በግቢ ውስጥ ሆኜ መጠበቅ ጀመርኩ።
ወደ ሆስፒታሉ ህንጻ የመግባት ፍላጎት አልነበረኝም። መሽቶ እንኳ ከሆስፒታሉ የሚሰጠውን ማረጋገጫ ስጠብቅ የነበረው ከህንጻው ውጪ ሆኜ ነበር።
በመጨረሻም ዶክተሩ ምንም እንኳ ከቫይረሱ ነጻ መሆኔ ቢረጋገጥም ለ14 ቀናት በቤት እራሴን ለይቼ መቆየት እንዳለብኝ እና ሰዎችም ሊጎበኙኝ እንደማይችሉ አስረድተውኝ ወደ መኖሪያ ቤት ገባሁ።
ህይወት በጣሊያን
ጣሊያን በኮሮና ቫይረስ ከተጠቁት የዓለም ሀገራት ቀዳሚዋ ነች።ይህ ዘገባ እስኪጠናከርበት ድረስ ሰባት ሺህ የሚጠጉ ዜጎቿን በበሽታው ተነጥቃለች።በዚህም ምክንያት በመላ ሀገሪቱ ዜጎች ከቤታቸው እንደይወጡ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል።ወትሮ በድምቀታቸው የሚታወቁት የጣሊያን ከተሞች መድረ በዳ ሆነዋል። የሚንቀሰቀቀስ ነፍስ የለም።በአጠቃላይ በኮሮና ቫይረስ ምክንያት ህይወት በጣሊያን ውስጥ ምን እንደሚመስል ቶቢያስ ጆንስ የተባለ ጣሊያናዊ እንደሚከተለው ይተርክልናል፡፡
ጣሊያናውያን የተለየ ባህሪ ያላቸው ህዝቦች ናቸው። ማህበራዊ ህይወት የሚያውቁ፣ ተጫዋቾች፣ ተግባ ቢዎች፣ ደስተኞችና በተስፋ የተሞሉ ብዬ ብናገር የሚገልጻቸው ይመስለኛል። ይህ ግን የኮሮና ቫይረስ በሀገሪቱ ውስጥ ተከስቶ በርካታ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት ከማብቃቱ በፊት ነው። ከዚያ በኋላ ካላችሁኝ ደግሞ በደፈናው ጣሊያናውያን ማንነታቸው ሙሉ በሙሉ ተቀይሯል። ዝምተኞች፣ ጨፍጋጎች፣ ደስታቢሶች፣ ገለልተኞችና ተስፋቢሶች ሆነዋል፡፡
ህይወት በዝምታና በአርምሞ ተሞላች ሆናለች።ሙሉ ለሙሉ ከቤታችን እንዳንወጣ ጥብቅ ትዕዛዝ ከመንግስት የተላለፈው በጸደይ ወራት አጋማሽ በመሆኑ እንደ ቀድሞ አበቦችን ማዛ ማጣጣምና በውበታቸውም መፍነክነክ ምኞት ሆኗል።እየሆነ ያለውን ልክ እንደ እስር ቤት በአንድ ጠባብ ክፍል ውስጥ ተቀምጦ ከመመልከት ውጭ አማራጭ የለም።በአርምሞ የሚወርደው ብናኝ ሰው አልባ በሆኑ ባዶ መሬቶች ላይ ሲያርፍ ይታያል።በቫይረሱ ስጋት ምክንያት ህጻናት ወደ ትምህርት ቤት እንዳይዱ በመደረጉ እቤት ውስጥ ያገኙትን ሁሉ ይጭራሉ።እንደልብ መውጣትና መግባት የለመደው ህጻናቱ እግር በአንዲት ክፍል ውስጥ ተለጉመው ለመቀመጥ ተገደዋል፡ ፡መሰልቸቱ ባስ ሲልባቸውም ማንጎራጎር ይጀምራሉ፤ ከወዲያኛው ቤት ውስጥ ያሉ ህጻናትም ይቀበላሉ፤ ከሩቅ ያሉትም ህጻናት ተመሳሳይ ብሶቶችን ያሰማሉ፤ ‹‹አይዞሽ ጣሊያን እናታችን ደህና ትሆኛለሽ፤ ሁሉም ነገር ይስተካከላል›› የሚሉ የህጻናት የተስፋ ድምጾች ሞገዱን ይሞሉታል፡፡
የአዋቂዎቹ ግን የተለየ ነው።በተስፋ መቁረጥ ውስጥ መሆናቸውን የሚያ መላክቱ ድምጾችና ጭቅጭቆች ይሰማሉ። መነጫነጮችና ተስፋ ማጣቶች ይደመጣሉ።ብሶት በሁ ሉም ቤት ይነበባል።በየሰዓቱ በጣሊያን የሚደርሰውን የሞት መጠን የሚዘግቡ የመገናኛ ብዙሃን በርካታ ናቸው።ትኩረታቸው ሁሉ ጣሊያን ሆናለች። አንዳንዶቹ ዘገባ ያስፈራል።የሟቾች ቁጥር በመበርከቱ የመቀበርያ ቦታ እጥረት ማጋጠሙን የተመለከቱ መረጃዎች እየተላለፉ ነው።የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ ሞት የእያንዳንዳችንን ቤት እንደሚያንኳኳ እርግጠኞች ሆነናል።በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትራችን ጆሲፔ ኮንቴ ‹‹ምድር ላይ ያለውን ሁሉ ሞከረን ፤ አልተሳካልንም፤ እንግዲህ የቀረን ወደ ፈጣሪ ማንጋጠጥ ነው›› የሚለውን መልዕክት ካስተላለፉ በኋላ ተስፋችን ሁሉ እንደጉም በኖ ጠፍቷል። የሚንቀሳቀሰው በቀቢጸ ተስፋ የተሞላው በድን አካላችን ብቻ ነው፡፡
ከጎረቤቴ አንድ ለቀሶ ድምጽ ይሰማል።ለወትሮው ሳቂታና ተግባቢ የነበረችው የ85 ዓመቱ አዛውንት ባለቤት ሚስተር ሬንዞ ካርሎስ ባለቤት ድምጽ መሆኑን አላጣሁትም።የደጓን ጎረቤቴን ድምጽ እንዴት ልጣው። ከአለቃቀሷ በዚሁ በኮሮና ቫይረስ ምክንያት በጠና ታመው የነበሩት ባለቤቷ ማረፋቸውን ለመገመት አልተቸገርኩም። ባለቤቷ እሷንና አምስት ልጆቻቸውን ትተው ማግለያ (ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች ለብቻ የሚቆዩበት ቦታ) ከገቡ ቆይተው ነበር።ምስኪን አቶ ሬንዞ በባለቤታቸውና በልጀቻቸው ጨክነው ይህችን ዓለም ተሰናበቷት፡፡
ኮሮና ቫይረስ ካለው በንክኪ የመተላለፍ ባህሪው የተነሳ የሞተን መቅበርና ማስተዛዘን የተከለከለ ነው። የሚወዱትን እና ለዘመናት በአንድ ጣራ ስር ክፉና ደጉን የአሳለፉትን ፤እኔ ነው የሚሉትን ሰው የትና እንዴት እንደተቀበረ ሳያውቁ እንዲሁ በሃዘን ተጨራምቶ መቀመጥን ያህል ልብ እንደሚነካ የተረዳሁት የዛን ጊዜ ነው።በቃ እንደዘበት ባልና ሚስት ፤ አባትና ልጆች ላይተያዩ እስከወዲያኛው ተለያዩ።ለካ የሞተን መቅበርና ማስተዛዘንም የሚቻለው ሀገር ሰላም ሲሆን ብቻ ነው።አይ ሰው፤ ሰው ከንቱ፡፡
አንዳንድ ጊዜ ለዚህ ሁሉ ጥፋት መግስትና ፖለቲከኞችን ጥፋተኛ አደርጋለሁ።በሌላ ጊዜ ደግሞ የህዝባችን ቸልተኝነትና የባለሙያዎችን ምክር አለመስማት ለዚህ ሁሉ መከራ እንደዳረገን ይሰማኛል። ከጅምሩ ጀምሮ በቀላሉ ልንከላከለው የምንችለውን የቫይረሱን ስርጭት ቸልተኞች ሆነን በራሳችን ላይ ሞት ጋበዝን፤ እልቂት አወጅን፤ የሃዘን ማቅ ለበስን። አዘውትሮ እጅ በመታጠብ፤ ባለመጨባበጥና ባለመጠጋጋት በቀላሉ በሽታውን መከ ላከል እንችል ነበር። ለምን ዘነጋን? ለምን ችላ አልን ? ምን አፈዘዘን? ጸጸት ብቻ፤ ልንመልሰው የማንችለው ጸጸት፡፡
ብዙ ተስፋ ነበራቸው፤ ነገን አልመው ዛሬ ላይ የቀሩ ኢጣላናውያን በርካቶች ናቸው።ልክ እንደ 85 ዓመቱ ሚስተር ሬንዞ ካርሎስ ልጆቻቸውን ለቁም ነገር አብቅተው ቤተሰቦቻቸውን ደስታ ለማጣጣም የተመኙ ብዙዎች ነበሩ።አዲሱ የፈረንጆች ዓመት 2020 ሲገባ ብዙዎች ፤ ብዙ ወጥነዋል፤ ብዙ አልመዋል፤ አቅደዋል።ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግን ህይወት መልኳን ቀየረች፤ ብዙዎቹ ተስፋ እንዱም በነነ።ስለነገ ሳይሆን ዛሬ ተንፍሶ ማደር ብርቅ ሆነ።ህይወት ቀልድ ሆነች፤ እንደቅጠል መርገፍ የበርካታ ጣሊያኖች ዕጣ ፋንታ ሆነ።
ህይወት በዚህ አስከፊ ሁኔታ ውስጥም ቢሆን መቀጠሉ ግድ ነው።እስትንፋስ እስኪቆረጥ ድረስ ለመኖር መንገታገት የተፈጥሮ ግዴታ ነው።ጣሊያንም ከነመከራዋ በየደቂቃው የሟቾችን ቁጥር ለዓለም እያሳወቀች ፤ ህይወትን ቀጥላለች።‹‹የምድሩን ጨርሰናል የቀረን ተስፋችን የሰማዩ ነው›› የሚለውን የጠቅላይ ሚነስትራችንን ቃል እኛም ተውሰን የምድሩን ተስፋ ማድረግ ከተውን ሰንብተናል፤ መዳናችን በላይኛው አምላክ ላይ ብቻ ሆኗል፡፡
አዲስ ዘመን መጋቢት 19 / 2012
እስማኤል አረቦ