
በተሰሩ ከፍተኛ የንቅናቄ ስራዎች ተቀዛቅዞ የነበረው ህዝባዊ ተሳትፎ ቀድሞ ወደነበረበት ሁኔታ እየተመለሰ እንደሚገኝ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።
የጽህፈት ቤቱ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ኃላፊ አቶ ሀይሉ አብርሃም በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደተናገሩት፤ ለህዳሴ ግድቡ ግንባታ የህዝቡ መዋጮ ተቀዛቅዞ የነበረው ከሀምሌ 2010 ዓ.ም እስከ ታህሳስ ወር 2011 ዓ.ም ድረስ ነበር።
በግድቡ ግንባታ ላይ ተነስተው በነበሩ ጉዳዮች ምክንያት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ተቀዛቅዞ ነበር። ከታህሳስ ወር 2011 ዓ.ም በኋላ ግን ህዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪው ፅህፈት ቤት በመላ አገሪቱ የተለያዩ መድረኮችን በማካሄድ ለህብረተሰቡ በቂ መረጃ የመስጠት ስራ ሰርቷል።
በዚህም አበረታች የሆኑ ውጤቶች የታዩ ሲሆን፤ አሁንም ድረስ ለህብረተሰቡ ስለ ግድቡ ግንባታ አጠቃላይ ሁኔታ ግንዛቤ እየተሰጠ ይገኛል።
በተያዘው በጀት ዓመትም በርካታ መድረኮች የተከናወኑ ሲሆን፤ የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ዘጠነኛ ዓመት በማስመልከት የምሁራን፤ የወጣቶችና የህፃናት ግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች መሰራታቸውን ገልፀዋል።
በሌላ በኩል፤ በህዳሴ ግድብ ዙሪያ ይደረግ በነበረው ድርድር የአሜሪካን ጣልቃ ገብነት አግባብ አለመሆኑን በምሁራን
ውይይት መነሳቱና ግልጽ መደረጉ ህብረተሰቡን እንዳነቃቃው አስረድተዋል።
እንደ አቶ ሀይሉ ገለጻ፤ በአዲስ አበባ የሚገኙ ወጣቶች የህዳሴ ግድቡ ያለበት ደረጃ አስመልክቶ ሙሉ ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል። ማብራሪያው ኢትዮጵያ እያደረገችው ባለው የዲፕሎማሲ ስራ ላይም ያተኮረ ነው።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ የብሄር ብሄረሰቦች ዋንጫ አዲስ አበባ የሚገኝ በመሆኑ፤ ዋንጫውን በየክልሎቹ በማዞር ገቢ ለማሰባሰብ እቅድ ተቀምጧል።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ የእግር ኳስ ውድድርም በቅርቡ የሚጀምር ሲሆን፤ የእግር ኳስ ጨዋታው አቅም ያላቸው ክልሎችም የሚያዘጋጁት እና የሚገኙበት ይሆናል። ይሁን እንጂ፤ በአገራችን በተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ምክንያት ለጊዜው እንዲዘገይ ተደርጓል።
የ“8100 A” አጭር የፅሁፍ መልዕክት በስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ 20 ሚሊዮን ብር ያስገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ በመጥቀስ፤ እስካሁን ከ365 ሺህ በላይ ሰዎች አጭር መልዕክት መላካቸውን ጠቁመዋል።
የመንግስት ሰራተኞችም ለግድቡ እስካሁን ድረስ ከደመወዛቸው እያዋጡ ሲሆን፤ አዳዲስ ሰራተኞች በፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ መልኩ ለግድቡ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
አዲስ ዘመን መጋቢት 14 /2012
መርድ ክፍሉ