
በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ በኢትዮጵያ ግብጽና ሱዳን መካከል በአሜሪካና በዓለም ባንክ ታዛቢነት ሲካሄድ በነበረው ድርድር መልኩን ቀይሯል። አሜሪካ የታዛቢነት ሚናዋን ወደ ጎን በመተው ለግብጽ በመወገን በኢትዮጵያ ላይ ጫና ማሳደር መጀመሯን ተከትሎ ኢትዮጵያ በመጨረሻው ዙር ድርድር ላይ ሳትሳተፍ መቅረቷ ይታወሳል።
ኢትዮጵያ ያልተሳተፈችበትን የመጨረሻ ዙር ድርድር ተከትሎ በግድቡ ውሃ አሞላልና በኦፕሬሽን ዙሪያ ሶስቱ ሀገራት ከስምምነት ሳይደርሱ ‹‹የግድቡ ውሃ ሙሌት እንዳይጀመር›› የሚል መግለጫ የአሜሪካ የግምጃቤት ሚኒስቴር አውጥቷል። ኢትዮጵያ አሜሪካ ያወጣችው መግለጫ ተገቢነት የጎደለውና ለግብጽ ያደላ በመሆኑ ተቀባይነት እንደሌለው የኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጠው መግለጫው አስታውቋል። የአሜሪካ ግምጃ ቤት ሚኒስቴር ያወጣው መግለጫ በርካታ ኢትዮጵያዊያንን ያስቆጣም ነበር።
ግብጽ ሴራዋ ቢከሽፍባትም ዛሬም መሯሯጧን ቀጥላለች። በቅኝ ግዛት ዘመን በተፈረመው ስምምነት የምታገኘው ‹‹የአባይ ውሃ መጠን መቀነስ የለበትም›› በሚል አቋሟ እንደጸናች ነው። የአረብ ሀገራትን ከጎኗ አሰልፋ ታሪካዊ የምትለውን የውሃ መብቷን ለማስጠበቅ በኢትዮጵያ ላይ ጫና በማሳደር ላይ ትገኛለች።
የአረብ ሊግ በኢትዮጵያ ላይ ጫና እንዲያሳድር ባቀረበችው ጥያቄ መሰረት ሰሞኑን ሊጉ ለግብጽ የሚያደላ መግለጫ አውጥቷል። ግብፅ የህዳሴ ግድብን ጉዳይ ከሶስትዮሽ ጉዳይ ይልቅ ዓለም አቀፋዊ አጀንዳ ለማድረግ እየተሯሯጠች መሆኑን የተመለከተችው ኢትዮጵያም ተመሳሳይ ነገር ግን ዲፖሎማሲያዊ እርምጃዎችን መውሰድ ጀምራለች። በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ያለውን አለመግባባት ለመፍታት የአፍሪካ ህብረት እንዲያደራድራት የህብረቱ ሊቀመንበር ለሆኑት የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎዛ ጥያቄ አቅርባለች።
ሲሪል ራማፎዛም የኢትዮጵያን ጥያቄ ተቀብለዋል። በተጨማሪም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ለተለያዩ ሀገራት መሪዎች ማብራሪያ በመስጠት ላይ ነች። ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ እና የቀድሞ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ ለአፍሪካ እና ለአውሮፓ ሀገራት ማብራሪያ የመስጠትና የማግባባት ስራ በመስራት ላይ ይገኛሉ። በግድቡ ላይ ግብጽ እያካሄደች ያለችውን እንቅስቃሴ አስመልክቶ የኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ከአልጄዚራ ጋር ቃለ ምልልስ አድርገዋል።
ቃለ ምልልሱ ስለ ግድቡ የውሃ አሞላል፤ የሱዳን ሚና፤ ኢትዮጵያ የአሜሪካ የግምጃ ቤት ሚኒስቴር ያወጣውን መግለጫ ውድቅ ማድረጓ በአሜሪካና ኢትዮጵያ ግንኙነት ላይ ሊያሳድረው የሚችለው አሉታዊ ተፅዕኖ እንዲሁም የአረብ ሊግ ያወጠው መግለጫ በአረቡ በኢትዮጵያ ግንኙነት ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ተዳሷል። ከአልጄዚራ የተረጎምነውን ቃለ ምልልስ ለውድ አንባቢዎቻችን እንደሚከተለው አቅርበነዋል። መልካም ንባብ።
አልጄዚራ፡- ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን የአረብ ሊግ የግብጽን አቋም እንደሚደግፍ የሚያረጋግጥ መግለጫ ማውጣቱ ይታወቃል። መግለጫው በኢትዮጵያና በአረብ ሊግ መካከል ባለው ግንኙነት ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር ይመስልዎታል?
አቶ ገዱ፡- በመጀመሪያ ለቃለ መጠይቁና ለተሰጠኝ እድል አልጄዚራን አመሰግናለሁ። የኢትዮ- አረብ ግንኙነት በታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ በየጊዜው በሚለዋወጠው የግብጽ አቋም እና ልዩነቶች ተጽዕኖ የማያሳድርበት ዘላቂ እና በታሪክ የተፈተነ ግንኙነት ነው። በአፍሪካውያን እና በአረቦች መካከል ያለው ግንኙነት እስከማይለያዩ ድረስ ጠንካራ፣ በጽኑ መሰረት ላይ የተገነባ እና እንዳይነጣጠል ሆኖ የተጋመደ ነው። የአረብ ሊግ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ
ጉዳይ ላይ የያዘው አቋም እነዚህን ግንኙነቶች አይጎዳውም። ሆኖም የበርካታ ሀገራት ስብስብ የሆነው ቀጣናዊ ድርጅት እንዲህ አይነቱን ውሳኔ ማውጣት አልነበረበትም ብለን እናምናለን። የአረብ ሊግ በመካከለኛው ምስራቅ እና በአፍሪካ ቀንድ መካከል ሰላም ለማምጣት እንዲሰራ ይጠበቃል። ጥቂት የማይባሉ የአረብ ሊግ አባል ሀገራት በግጭትና ቀውስ ውስጥ ናቸው። በየመን ወደ ፍርስራሽነት ተቀይራለች፤ ሶሪያዊያን እየተሰቃዩ ነው፤ ሊቢያም ቀውስ ውስጥ ነች። ሊጉ ሌላ ቀጣናዊ ቀውስ ሊያስከትሉ የሚችሉ መግለጫዎችን ከመስጠት ይልቅ እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችል መፍትሄ የሚሆን የውሳኔ ሀሳብ ማስተላለፍ ነበረበት።
በተለይ ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ ኢትዮጵያና የአረቡ ዓለም ታሪካዊና ባህላዊ ትስስርን የምንጋራ፤ ኢትዮጵያ ለእስላምና የመጀመሪያ ቤት በመሆን ያገለገለች፤ የአረቡን ዓለም እና ከሰሃራ በረሃ በታች ያለውን አፍሪካ የማገናኘት ሚና እየተጫወትን ነው። ከዚያም ባሻገር ከሱዳን እና ከግብፅ ህዝቦች ጋር ለዘመናት ህይወት ተጋርተናል። አባይ ከኢትዮጵያ ወደ ታችኞቹ ተፋሰስ ሀገሮች እንዲፈስ ያደረገው የፈጣሪ ፈቃድ ነው።
አንድ ነገር ላረጋግጥልህ እወዳለሁ ከሶስቱ ሀገራት ፍላጎት የሚተርፍ ውሃ በአባይ ወንዝ ውስጥ አለ፤ ይህን ውሃ በአግባቡ ልንጠቀመው ይገባል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ውሃ የምናከማቸው ከሐምሌ እስከ ነሐሴ ባለ ዝናባማ ወቅት ብቻ ነው። ምክንያታዊ ሆነን ካሰብን በተቻለን አቅም ከፍተኛ መጠን ያለው ሀይል ለማመንጨት ከፍተኛ መጠን ያለው ውሃ ወደ ታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ማፍሰስ አለብን። እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ግድቡን በታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ላይ ጉዳት እንደሚያደርስ መግለጽ ግልፅ ፕሮፓጋንዳ ነው።
አልጄዚራ፡- በህዳሴ ግድብ ምክንያት ጦርነት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚል ስጋት አለ። በዚህ ጉዳይ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
አቶ ገዱ፡- በግድቡ ወይም በአባይ ወንዝ ምክንያት ጦርነት አይኖርም። ምክንያቱም ከጦርነት ምንም ትርፍ የለም። ኢትዮጵያ አባይ ከምድሯ እንደሚፈልቅ ብታውቅም የሱዳን እና የግብፅ ፍላጎት እንዲሁ ሊጠበቅላቸው ይገባል የሚል እምነት አላት። ለሶስቱ አገራት ህዝቦች ሕይወት የሚሰጥ አባይ በተፋሰሱ ለሚኖሩ ለሁሉም ህዝቦች የህይወት መድህን ሆኖ ይቆያል።
ኢትዮጵያ ሁሉም የናይል ወንዝ ተፋሰስ ሀገራት ከናይል ወንዝ ውሃ ፍትሃዊ ተጠቃሚ መሆን እንዳለባቸው ታምናለች። እኛ ሰላም ፈላጊ ነን፣ እኛ የምንፈልገው ነገር ግድቡ በሌሎች ላይ ጉዳት ሳያስከትል ድርሻችንን ለማግኘት ብቻ ነው። ከመጀመሪያው ጀምሮ ሁሉንም የግድቡን ዲዛይኖች ለሱዳን እና ለግብጽ አስተያየት እንዲሰጡበት አስገብተናል። ከአባይ ወንዝ ለኢትዮጵያ ያለው ማንኛውም አይነት ጥቅም የምታገኝ ከሆነ የግብፅን ፍላጎት የሚጻረር መሆኑን የሚገልጽ የሚዲያ ዘመቻ አስተውለናል።
ኢትዮጵያ ከወንዙ የምትጠቀም ከሆነ የግብፅ ህዝብ በውሃ ጥም እንደሚሞት አድርጎ የፕሮፓጋንዳ ስራ በመስራት የግብፅን ህዝብ በማሳሳት እውነቱን ለምን ያዛባሉ? ለምን የግብፅ ህዝብ ከጎረቤቶቻቸው ጋር እንዲጋፈጡ ይገፋፋሉ? የግብጽ ሚዲያዎች ስለ ህዳሴው ግድብ ሁሉንም ዝርዝር ነገሮች ያውቃሉ፤ ውሃው ኤሌክትሪክ ካመነጨ በኋላ ውሃው በሙሉ ወደ ወንዙ ይመለሳል። እንደ ድሮው ወደ ግብጽ ይፈሳል።
የግብፅ ድምጸት የሚያመለክተው ኢትዮጵያዊያን የናይል ውሃን በጭራሽ እንዳይጠቀሙ፤ ስለመጠቀም እንኳ እንዳያስቡ የሚከለክል ነው። ይህ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው እና ፍትሃዊ አይደለም። በተመሳሳይም ግብፃውያን የኢትዮጵያዊያንን የልማት ፍላጎቶች ከግምት ውስጥ አለማስገባታቸው እና የኢትዮጵያን ህዝብ በዘላለማዊ ድህነት ውስጥ እንዲቆዩ መፍረድ ሰብአዊ አይደለም። ግድቡ በግብጻዊያን ላይ ምንም አይነት አሉታዊ ተፅዕኖ እንደማያሳድር እያወቁ ይልቁንም ለግድቡ ግንባታ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማበርከት ፋንታ በኢትዮጵያዊያን ላይ ፍትሃዊ ያልሆነ የመገናኛ ብዙኃን ዘመቻ ማካሄድ እና የግብፅን ህዝብ ለማሳሳት መርጠዋል። ይህ የተሳሳተ ብቻ ሳይሆን ጭካኔ የተሞላበት አካሄድ ነው።
አልጄዚራ፡- ሱዳን ኢትዮጵያና ግብጽ ወደ ድርድሩ እንዲመለሱ ጥሪ አቅርባለች። በዚህ ላይ አቋምዎ ምንድነው?
አቶ ገዱ፡- ሱዳን ጎረቤት ሀገር ነች፤ አቋሟም ግልፅ ነው። ሱዳናዊያን አንዳንድ የሚያሳስባቸው ጉዳዮች ነበሯቸው። እነዚያን ሱዳናዊያንን የሚያሳስቡ ጉዳዮችን እኛ ፈተናል። በብዙ ጉዳዮች ላይ ስምምነት ላይ ደርሰናል። እናም ሁላችንም ከአባይ ወንዝ እኩል እና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ማግኘት የምንችልበትን ራዕይ ከሱዳን ጋር እንጋራለን። ሱዳን በግብፅ እና በኢትዮጵያ መካከል የሚታየውን የሀሳብ ልዩነቶችን በማቀራረብ ረገድ ቁልፍ ሚና ትጫወታለች።
በሱዳን እና በግብፅ መካከል ያለው ዋነኛው ልዩነት ሱዳን በናይል ፍትሃዊና በእኩል አጠቃቀም ላይ የምታምን ሲሆን ግብፅ ደግሞ የታሪካዊ መብቴ ብላ የምታምነው ውሃው በማንም እንዳይነካባት ምኞት አላት። የጥርጣሬ ከባቢ እንዲጨምር በሚያደርገው የአረብ ሊግ የአቋም መግለጫ ላይ ሱዳን አልፈርምም ማለቷ የሚያስመሰግናት ነው። የሱዳን አቋም የተመሰረተው አባይ ለተፋሰሱ ሀገራት የግጭት ምንጭ ሳይሆን ተፋሰሱ የትብብር ምንጭ መሆን አለበት በሚል መርህ ላይ ነው። ለሱዳናዊያን ለሰላምና አብሮነት ድጋፍ ስላላቸው እናመሰግናለን እናም እኛም እንደግፋቸዋለን እንዲሁም ከጎናቸው እንቆማለን።
አልጄዚራ፡- ግድቡም ውሃም የእኛው ነው ብለዋል። ታዲያ ከግብፅ እና ከሱዳን ለምን ተጣሉ?
አቶ ገዱ፡- በተግባር ኢትዮጵያ የዓባይ ምንጭ ናት። ሆኖም ለወንዙ በምናበረክተው ልክ ምንም ጥቅም አላገኘንም። ከታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጋር መተማመንን ለመገንባት ውይይቶችን ስናካሂድ ቆይተናል። ምንም እንኳን ይህ ሉዓላዊ ፕሮጀክት ቢሆንም፤ ምንም እንኳን ግብጽ ለግድቡ አስተዋጽኦ ማበርከት የነበረባት ቢሆንም፤ እኛ ለማሳመን ጥረት ስናደርግ ቆይተናል። እኛ የምንገነባው ችግረኛ በሆኑ ወገኖቻችን በሚበረከተው ድጋፍ ነው።
በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን 65 ሚሊዮን ህዝባችን ያለ መብራት እየኖረ ነው። እስኪ አስብ ግብጻዊያን ለአንድ ሳምንት የኤሌክትሪክ ሀይል ቢያጡ እንዴት ሊሆኑ ይችላሉ። መልዕክታችን ግልጽ ነው። የአባይ ወንዝ የመጠቀም ተፈጥሮአዊ መብታችንን ማደናቀፍ ተቀባይነት የለውም። እናም እኛ ለየትኛውም ጫና አንንበረከክም።
በታችኛው ተፋሰስ አገራት ላይ ጉዳት እንዳያስከትል ለመከላከል ግድቡን በደረቅ ወቅት ለመሙላት እና ሃይል ካመነጨ በኋላ ከፍተኛ መጠን ያለው ውሃ ከግድቡ ወደ ታችኛው ተፋሰስ እንዲወርድ ተስማምተናል። እነሱ ያንን ሁሉ በደንብ ያውቃሉ፣ ግን አሁንም ህዝቦቻቸውን በኢትዮጵያ ላይ ለማነሳሳት መርጠዋል። በአባይ ተፋሰስ አገሮች መካከል በትብብር መርህ ላይ የተመሠረተ አዲስ ራዕይ ማቋቋም እንፈልጋለን። እኛ የግብፅን አሳሳቢ ጉዳዮች እናውቃለን። በእርግጥ ኢትዮጵያ የግብጽን ህዝብ የመጉዳት ዓላማ የላትም። ኢትዮጵያ ድህነትን ከኢትዮጵያ ለማስወገድ ጥረት እያደረገች የግብጽ ህዝብ እንዲደኸይ አትፈልግም።
አልጄዚራ፡- ስለዚህ ፣ የመርሆዎች ስምምነት እና የዋሺንግተን ውይይቶች ዕጣ ፈንታ ምንድነው?
አቶ ገዱ፡- አባይ ድንበር ተሻጋሪ ወንዝ ስለሆነ እና አጠቃቀሙ በትብብር መርሆዎች ላይ የተመሠረተ መሆን አለበት ብለን ስለምናምን የመርሆዎች ስምምነት በ2015 ፈርመናል። የመርሆዎች ስምምነቱ የትብብር ማዕቀፍ ነው። በታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ላይ ጉልህ ጉዳት በማያስከትል መልኩ ግድቡን የመገንባት መብታችንን ይደግፋል።
ለወደፊቱ ሊነሱ የሚችሉትን ሁሉንም ችግሮች በሶስትዮሽ ውይይቶች ለመፍታት የሚረዱ መመሪያዎችን አቅፎ የያዘ ነው። ማዕቀፉን በመጠቀም ልዩነቶችን በውይይት መፍታት ይቻል ነበር። ጉዳዩን አለም አቀፍ አጀንዳ ለማድረግ የመረጠችው ግብፅ ናት። ለእኛ የሶስትዮሽ ድርድር በጣም የተሻለው እና በተሟላ በተስማማነው የመርሆዎች ስምምነት ውስጥ የተቀመጡት መርሆዎች ብቸኛው መውጫ መንገድ ሊሆን ይችላሉ።
አልጄዚራ፡- ተቃውሞ ቢኖርም፣ የመጀመሪያ ዙር የውሃ ሙሌት እና ሙከራ በቀጣይ ሐምሌ ወር ይካሄዳል?
አቶ ገዱ፡- በሦስቱ ሀገራት መካከል በሚካሄዱ ድርድሮች ሁሉም ችግሮች ሊፈቱ እንደሚችሉ እናምናለን። በእርግጠኝነት እኛ ግድቡን በዕቅዳችን መሰረት እንጨርሰዋለን። የውጭ ጣልቃ-ገብነት እኛ ከንግግሮች አለመገኘትን ያስከትላል።
የአሜሪካ የግምጃ ቤት መግለጫ አሜሪካን ከታዛቢ ወደ አሸማጋይ በመጨረሻም የመፍትሄ ሀሳቦች አፍላቂ አድርጓታል ብለን እናምናለን። አሜሪካ በግብፅ ጥያቄ በታዛቢነት እንድትሳተፍ ያደረግነው። አሜሪካ በታዛቢነት እንድትሳተፍ ግብጽ ያቀረበችውን ሀሳብ በመልካም እምነት እና የበለጠ መተማመን ለመገንባት በማሰብ ነው የተቀበልነው። አሁን ግን የአሜሪካ ሚና ከተስማማንባቸው ጉዳዮች ውጭ መሆኑን ተመልክተናል። አሁንም አሜሪካኖች እንደታዛቢ ሆነው ለመቀጠል ከፈለጉ መልካም ነው። መቀጠል ይችላሉ። ነገር ግን ሉዓላዊነታችንን እና ሀብታችንን የመጠቀም መብት የሚጎዳ ምንም አይነት ነገር አንቀበልም።
ኢትዮጵያ የራሷ እሴቶች እና መርሆዎች ያሉዋት አገር ናት። አሜሪካ ለግብጽ፣ ለኢትዮጵያ እና ለሱዳን ወዳጅ የሆነች ሉዓላዊ ሀገር ነች። የየትኛውንም ሀገር ሉዓላዊነት የመጋፋት መብት የላትም። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጉዳይ በቀላል መግለጫ ብቻ ሊፈታ አይችልም። ሁሉንም ጉዳይ በድርድር ለመፍታት እንፈልጋለን። የግብፅን ስጋት እንረዳለን፣ ግን እኛ ሕዝቧ ተገቢ ባልሆነ ፍርሃትና ሽብር ውስጥ እንዲወድቁ አንፈቅድም።
አልጄዚራ፡- ግድቡ በግብፅ ውስጥ የውሃ ጥም እና ርሃብ ሊፈጥር ይችላል በሚለው ስጋት ላይ ምን አስተያየት አልዎት?
አቶ ገዱ፡- በመጀመሪያ ግድቡ አባይን ወደ ግብጽ ከመሄድ አይከለክልም። በተቃራኒው ግድቡ የውሃ ማጠራቀሚያ ሆኖ ሊያገለግል ስለሚችል የሱዳን እና የግብፅን ህዝብ በደረቅ ወቅት ሊያድን ይችላል። ግድቡ ውሃ ወደ ታችኛው ተፋሰስ እንዳይሄድ ለማገድ የሚገነባ አድርጎ ማቅረብ አግባብነት የለውም። እንዲህ ብሎ መረጃ ማሰራጨት ህዝብን ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ የመምራት ዘመቻ ነው። ህዝባችንን ከድህነት ለማውጣት እየገነባን ያለው ግድቡ በታችኛው ተፋሰስ የሚገኘው ህዝብ እንዲጠማ እና እንዲራብ የሚያደርግ ነው የሚል ወሬ አስደንቆናል። እነዚህ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የተከፈቱ የተደራጁ ዘመቻዎች ናቸው።
ከአካባቢው ቀውስ ትኩረትን ለመሳብ ዓላማ ይዘው የተከፈቱ የተደራጁ ዘመቻዎች ናቸው። ይህ ለሶስቱ ሀገራት ህዝብ ጥሩ አይደለም። ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚደረጉ ውይይቶች ብቸኛው መውጫ መንገድ ነው። በነገራችን ላይ ግድቡን በሦስት ዓመት ውስጥ ብቻ ውሃ መሙላት ይቻል ነበር። ነገር ግን የግብፅን ስጋት ለመቅረፍ በሰባት ዓመታት ውስጥ ለማድረግ ተስማምተናል።
ኢትዮጵያ ስላደረገችው ትክክለኛ ስምምነት የግብፅ ሰዎች ለምን አይናገሩም? ህዝባቸውን በኢትዮጵያ ላይ ለምን ያነሳሳሉ?! እኛ ምንም ጉዳት ባላደረግንበት ለምን ስማችንን ያጠፋሉ?! ኢትዮጵያ ዛሬም ሆነ ወደፊት በግብጽና በሱዳን ሕዝብ ላይ ምንም አይነት ጉዳት የማድረስ ዓላማም ሆነ ፍላገት እንደሌላት ላረጋግጥላችሁ እፈልጋለሁ፡፡
አልጄዚራ፡-አለመተማመንግብፅ የአሜሪካን ሽምግልና እንድትፈልግ ገፍቷል፤ እርስዎ የአለመተማመን ቀውስ አለ ብለው ያስባሉ?
አቶ ገዱ፡- አለመተማመን የመገናኛ ብዙኃን እና በዲፕሎማሲ ዘመቻዎች በኤጀንሲዎች በኩል ከወሰደ በኋላ የተከማቸ ውጤት ነው። እነዚህ ሁሉ መተማመንን ለማጥፋት ትልቅ አስተዋፅኦ ነበራቸው። ሆኖም አሁንም ከውይይት ሌላ አማራጭ የለም። ጉዳዩ በጣም የተወሳሰበ አይደለም እናም በሦስቱ ሀገሮች መካከል በአስተማማኝ ሁኔታ ሊፈታ ይችላል። ግብፆችን ችግሮቻችንን ከማንኛውም ሀገር በበለጠ ያውቁታል እኛም የግብፅን ስጋት በትክክል እንረዳለን ።
በእኛ ላይ ጥላቻ መስበክ እና አረቦችን በእኛ ላይ ማነሳሳት ለግንኙነታችን ጥሩ አይደለም። ከግብጽ የምንጠይቀው ኢትዮጵያ የአባይ ውሃን የመጠቀም ተፈጥሯዊ እና ህጋዊ መብት እንዳላት አምነው እንዲቀበሉ ነው። ይህ ለሁሉም የናይል ተፋሰስ አገሮች ነው።
አልጄዚራ፡- ከግብጽ ጋር ያለው ውጥረት እየጨመረ መምጣት ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ባላት ግንኙነት ላይ የሚንጸባረቅ ይመስልዎታል?
አቶ ገዱ፡- ከአሜሪካ ጋር ያለንን ግንኙነት አይነካውም። እኛን ለማገዝ ከእኛ ጋር በድርድሩ ተሳትፈዋል። በአሜሪካኖች እገዛ መግባባት ላይ ደርሰን ቢሆን መልካም ነበር። ካልሆነ ግን ጥረታቸው ለምን አልተሳካም ብለው አሜሪካኖች ራሳቸውን ይጠይቁ ይሆናል። በመሰረቱ የግድቡ ጉዳይ የሶስቱ ሀገራት ጉዳይ ነው። አሜሪካ ጥሩ ጥረት አድርጋለች፤ ነገር ግን ግድቡ የኛን የሉዓላዊነት እና ብሄራዊ ጥቅም ነው።
አልጄዚራ፡- አንዳንዶች ከቅርቡ ጊዜ ወዲህ ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ጉዳይ እያጦዘች መምጣቷ ከሚመጣው ብሔራዊ ምርጫ ጋር ተዛመዶ አለው ይላሉ። እርሶ በዚህ ይስማማሉ? አቶ ገዱ፡- ካለፈው መስከረም ጀምሮ ግብፅ በእኛ ላይ የሚዲያ ዘመቻ ጀመረች። ለመገናኛ ብዙኃን ፍጆታ መጋለጥ በሌለባቸው ቴክኒካዊ ጉዳዮች ላይ የሶስትዮሽ ውይይት እየተካሄደ በመሆኑ የሚዲያውን ዘመቻ እንዲያቆሙ ነገርናቸው። ግብጾች በተረጋጋ መንፈስ እንዲቀመጡና እንዲነጋገሩ ጠይቀናቸዋል።
እነሱ ግን ጉዳዩን ዓለም አቀፍ አጀንዳ ለማድረግ ጥረት አደረጉ፤ እናም ጉዳዩን ወደ አሜሪካ ወሰዱት። ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ጉዳይ አላጦዘችም። ‹‹ኢትዮጵያ የአባይ ውሃ ወደ ግብጽ እንዳይፈስ ልታግድ ነው›› በሚል መሠረተ ቢስ ክስ ላይ በመመስረት ጉዳዩን ለውስጥ የፖለቲካ ፍጆታ ያዋለችውና ትኩረቱ ኢትዮጵያ ላይ እንዲሆን ያደረገችው ራሷ ግብጽ ናት። በእኛ በኩል እኛ ተቀባይነት ለሌለው ግፊት እስከምንጋለጥ ድረስ ብሄራዊ ፕሮጀክታችን ስላለበት ሁኔታ መሰረታዊ መረጃ ለህዝባችን እንኳ አልሰጠንም።
ለእኛ ግድቡ ከምርጫ በላይ ነው። ምርጫ የፓርቲ ጉዳይ ነው፣ ግድቡ ግን ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚጋሩት ሀገራዊ ጉዳይ ነው። ተቃዋሚ ፓርቲዎች መንግስትን ሊቃወሙ ይችላሉ፤ ነገር ግን በግድቡ ጉዳይ ላይ ምንም ልዩነት የለም። በሁሉም ኢትዮጵያዊያን አስተዋጽኦ የተገነባ ሀገራዊ ፕሮጀክት ነው። ግድቡ ከምርጫ እና ከፖለቲካ ስልጣን በላይ ነው። አልጄዚራ፡- የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ለዚህ ቃለ ምልልስ አመሰግናለሁ። አቶ ገዱ፡- እኔም አመሰግናለሁ
አዲስ ዘመን መጋቢት 10 ቀን 2012 ዓ.ም
መላኩ ኤሮሴ