ከዘጠኝ ዓመታት በፊት በቱኒዚያ የተጀመረው የአረብ ሀገራት ህዝቦች ተቃውሞ በወቅቱ የበርካታ መንግስታትን መንበር አናግቶ ነበር። በቱኒዚያ አንድ ስራ አጥ ወጣት ራሱን በእሳት ካቃጠለ በኋላ ሁሉም በየመንግስቶቻቸው ላይ ተቃውሟቸውን ማሰማት ቀጠሉ። እያለ እያለም በርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ እና የሰሜን አፍሪካ አረብ አገራትን ያመሰው የህዝቦች ቁጣ በየቦታው ተቀሰቀሰ። ቆየት ብሎ «የአረብ ፀደይ» የሚል ስያሜ የተሰጠውና አብዛኛውን የአረብ ሊግ አባላት የአንድ ሰሞን ራስምታት የነበረው አመጽ የየአገራቱን መሪዎች አንድም ለሞት አንድም ለስደት የዳረገ ነበር።
በዜጎቻቸው አምባገነን የተባሉ በርካታ አገዛዞችም ተገርስሰው በሌላ አስተዳደር ተተክተው እየሰሩ ይገኛል። ለአብነት የቱኒዚያው አል አቢድኔ ቤን አሊ ከስልጣናቸው በግድ እንዲለቁ በመደረጋቸው በሳኡዲ አረቢያ በስደት ላይ ናቸው። የግብጹ ሆስኒ ሙባረክም በህዝብ ግፊት ከስልጣናቸው እንዲለቁ ከተደረገ በኋላ ፍርድ ቤት ለፍርድ ቤት በቃሬዛ ተሽከርካሪ ተኝተው ሲንከራተቱ ነበር። ካሁን አሁን ህመማቸው ጠንቶባቸው ለሞት አበቃቸው እየተባለ ሲጠበቅ በ90 ዓመታቸው የሰቆቃ ጊዜ እያሳለፉ ይገኛል። የሊቢያው ሞሃመድ ጋዳፊም አይነኬው ወንበራቸው በህዝቡ ተቃውሞ ሲናጋ ጉድ ያላለ አልነበረም። እርሳቸውም የወርቅ ሽጉጥ ባለቤት ቢሆኑም በሊቢያ ሲርጥ ከተማ በዋሻ ውስጥ ሞተው ተገኙ። ገዳዮቹ ደግሞ የአገራቸው የሽግግር ካውንስል ታጣቂ ሃይሎች ነበሩ። የሶሪያው መሪ አልአሳድም ከፍተኛ የህዝብ አመጽ ቢነሳባቸውም በተቀናቃኞቹ የአሜሪካ እና ሩሲያ ሽኩቻ ምክንያት እስካሁን ስልጣናቸውን አልለቀቁም። ማን ያውቃል አንድ ቀን እርሳቸውም የሌሎቹ እጣ ፋንታ ይደርሳቸው ይሆናል።
የአረብ ፀደይ አመጽ ካለፉት ከዓመታት በኋላ ህዝባዊ አመጽ በኢትዮጵያም በርትቶ ነበር። በተለይ ባለፈው አራት እና አምስት ዓመታት ከፍተኛ የወጣቶች ተቃውሞ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች ላይ ተስተናግዷል። የኋላ ኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ ተተክተው ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ባይደረግ ኢትዮጵያም ወደ አስከፊ ችግር ልትገባ እንደምትችል አመላካች ምልክቶች ነበሩ። ተረኛዋ ኤርትራ ነች ያሉ በርካታ ሰዎች በኢሳያስ አፈወርቂ በሚመራው የኤርትራ መንግስት ላይ ጣታቸውን ሲቀስሩ ግን ያልተጠበቀ ነገር ተከሰተ። ዶክተር አብይ አህመድ በጠነሰሱት የሰላም ስምምነት ምክንያት ኤርትራ ከጎረቤት አገሮቿ ጋር ወደ ተሻለ ሰላማዊ ግንኙነቷ መመለስ ጀመረች። በአውሮፓ እና አሜሪካ በሚገኙ የምስራቅ አፍሪካ የፖለቲካ ተንታኞች የተገመተው የኤርትራ ህዝብ አመጽ ሳይሳካ ቢቀርም ጉዳዩ ፊቱን ወደ ሱዳን አዙሯል።
ሱዳን በዳቦ ዋጋ ጭማሪ መነሻ ካለፉት ሳምንታት ጀምሮ ስትታመስ ቆይታለች። ነገሩ ከቀን ወደ ቀን እየከረረ ሄዶ አሁን ላይ መንግስት እርምጃ በመውሰዱ የበርካቶች ህይወት እየተቀጠፈ ይገኛል። ከትናንት በስቲያ የሱዳን መንግሥትን የኢኮኖሚ እርምጃዎች መዳከም ተቃውመው አደባባይ የተገኙ ሰዎችን ለመበተን ያሰበው የመንግስት ጦር በወሰደው እርምጃ ያልተደሰቱ በርካቶች ከፖሊሶች ጋር ተጋጭተዋል። የሱዳን ተፎካካሪ ፓርቲዎች እስካሁን የተገደሉ ሰዎች 22 ይደርሳሉ ብለው ሳምንት መግለጫ ቢያወጡም የሱዳን መንግስት በበኩሉ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከተጠቀሰው በታች ነው በማለት ሲከራከር ቆይቷል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ እስከአሁን 37 ሰዎች በተቃውሞ ወቅት መገደላቸውን ይፋ አድርጓል።
የአገሪቷን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚከታተሉ ተቋማት ባወጡት መረጃ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት በሱዳን ከነበረው የሸቀጦች ዋጋ አሁን ላይ በእጥፍ መጨመራቸውን እየገለጹ ይገኛል። የዋጋ ንረቱ እስከ 70 በመቶ መድረሱን ደግሞ የዘገቡ መገናኛ ብዙሃን በርካታ ናቸው። ተቃውሞውን ለማብረድ ደግሞ መንግስት በርካታ የተፎካካሪ አመራሮችን እና የተለያዩ ዜጎችን በስፋት እያሰረ እንደሚገኝ የቢቢሲ ዘገባ ያመላክታል።
የቢቢሲዋ ጸሃፊ ዛይናብ ሞሃመድ ሳሊህ እንደምትገልጸው፤ ለሶስት ዓስርት ዓመታት የዘለቀው የአልበሽር የስልጣን ዘመን የታከታቸው ዜጎች የከፋ ተቃውሞ እያሰሙ ነው። በርካታ ሱዳናውያንም ገንዘባቸውን ከባንክ በማውጣት ቤታቸው ውስጥ እያስቀመጡ ይገኛል። ምክንያቱም ገንዘባቸውን በባንክ ያስቀመጡ ሰዎች እንዲሰጣቸው በሚጠይቁበት ወቅት ካዝናው ባዶ መሆኑ እየተነገራቸው ነው። ገንዘብ በሚኖርበት ወቅት ደግሞ ለመውሰድ የሚደረገው ሰልፍ ለሰዓታት ነው። ለዳቦ ገበያው የሚሰለፈው ሰው ደግሞ ከሱቆች አልፎ አውራ ጎዳናዎች ላይ ደርሷል።
የኢኮኖሚ ተንታኞች እንደሚሉት የህዝቡ የባንክ አመኔታው መቀነስ በቀጣይ የአገሪቷ ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚያሳድር ይታመናል። የገንዝብ እጥረት ከተከሰተም የወጪ እና ገቢ ምርቶች መጠን ሊቀንስ ስለሚችል የባሰ የምርት ዋጋ ጭማሪ እንዳይፈጠር ያሰጋል። እያንዳንዱ ሰው ገንዘቡን ከባንክ አውጥቶ በየቤቱ በሚያስቀምጥበት ወቅት የዝርፊያ እና ወንጀል ፈጻሚዎች ቁጥር ሊበረታ ይችላል። የሆነ ሆኖ ነዋሪዎች በባንክ ያስቀመጡትን ገንዘብ በማውጣት እጃቸው ላይ እየያዙ ነው። ይህ እንቅስቃሴ ከቀጠለ መንግስት ህዝቡን ሊያረጋጋ የሚችልበትን መንገድ መፈለግ እንደሚገባው ባለሙያዎቹ ይገልጻሉ።
በተለይ የብር ኖቶችን በተለያዩ ባንኮች በማስቀመጥ እና ሰዎች በሚፈልጉበት ወቅት እንዲወስዱ የሚያስችል አመኔታን ማዳበር ካልቻለ በአጭር ጊዜ ውስጥ ባንኮች ባዷቸውን ሊቀሩ ይችላሉ። ጉዳዩ የሚመለከተው የሱዳን ማዕከላዊ ባንክ ለችግሩ ጊዜያዊ መፍትሄ ማዘጋጀት ይኖርበታል። ከስድስት ወር በፊት 40 የሱዳን ፓውንድ በአንድ የአሜሪካን ዶላር የሚመነዘር ቢሆንም አሁን ላይ በጥቁር ገበያው አንዱ የአሜሪካን ዶላር 76 የሱዳን ፓውንድ እየተሸጠ መሆኑን የቢቢሲ ዘገባ ያመላክታል።
ምንጊዜም የምርት ዋጋ መናር ሲከሰት ዜጎች በርካታ ገንዘብ ለሸመታ ስለሚያስፈልጋቸው የባንኮችን በር ከበፊቱ በበለጠ ማንኳኳታቸው አይቀርም። በመሆኑም አንድም የዋጋ ንረቱን መቆጣጠር በሌላ በኩልም የጥቁር ገበያውን ተጽእኖ መቀነስ ይኖርባቸዋል። የአገሪቷ የኢኮኖሚ ቀጣይ አቅጣጫ በህዝቦቿ እና በመንግስታቸው ትብብር እንዲሄድ ካልተደረገ አክሳሪ እንደሚሆን ባለሙያዎች እየተነበዩ ነው። በመሆኑም የአልበሽር መንግስት መሰረታዊ ፍጆታ እቃዎች ላይ ያለውን የዋጋ ንረት ጋብ ማድረግ የሚያስችሉ አማራጮችን መውሰድ ይጠበቅበታል።
የሱዳን መንግስት የወጪ መብዛትን ለመቀነስ በነዳጅ እና ዳቦ ላይ ያደርግ የነበረውን ድጎማ ማንሳቱን ተከትሎ እያንዳንዱ የመሰረታዊ ፍጆታ እቃዎች ላይ የዋጋ ማሻቀብ አስከትሏል። ግሽበቱን ተከትሎ ለሶስት ሳምንታት የዘለቀው አመጽ መነሻው አትባራ በተባለችው ምስራቃዊ የሱዳን ከተማ ነው።
በሌላ በኩል አልበሽር ለመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪ እንደሚያደርጉ እና የዋጋ መናሩን እንደሚቆጣጠሩ ቃል ገብተዋል። አለመረጋጋቱ ከቀጠለም እንደሶሪያ መሆናችን አይቀርምና ለራሳችሁ ስትሉ ተጠንቀቁ ሲሉም መግለጫ ሰጥተዋል። ይሁንና የአገሪቷ የኢኮኖሚ መዳከም የአሜሪካን ማዕቀብ እና የነዳጅ ምርት መቀነስ ከጀመረ ስምንት ዓመታት አልፈዋል። ሶስት አራተኛውን የነዳጅ ዘይት ምርት ይዛ የተገነጠለችው ደቡብ ሱዳን ከተለየቻቸው በኋላ ሱዳን ገቢዋ ቀንሷል።
የቢቢሲዋ ተንታኝ እንደምትለው፤ ጥያቄዎች አሁን ላይ የኦማር አልበሽር መንግስት ይነሳልን ወደሚል ተቃውሞ ተቀይሯል። ወደ አደባባይ የሚተመው ህዝብም የአረብ ጸደይ አመጽ ወቅት ይስተጋቡ የነበሩ መልዕክቶችን ይዞ እየወጣ ይገኛል። የካርቱሙ ተቃውሞ አልበሽር ወደ ስልጣን ከመጡ ጀምሮ ያልታየ ትልቁ ተቃውሞ ሆኗል። በተቃውሞ ከተከሰተው ግድያ በተጨማሪ ደግሞ ተቃውሞውን የዘገቡ ጋዜጠኞች መታፈን እና ከፍተኛ ድብደባ እየደረሰባቸው ነው።
አሜሪካ፣ ብሪታንያ፣ ኖርዌይ እና ካናዳ ደግሞ የሱዳን ጉዳይ እንዳሳሰባቸው በመግለጫቸው አስፍረዋል። በመግለጫቸው እንዳሉት በሱዳን ያለው የሰብአዊ መብት ረገጣ እና የሰዎች ግድያ መቆም አለበት። በተጨማሪ ያለፍርድ የተያዙ ጋዜጠኞች፣የፖለቲካ አመራሮች እና ሌሎች መፈታት አለባቸው።
የአሶስዬትድ ፕሬሱ ሳሚ ማግዲ እንደገለጸው ደግሞ፤የ75 ዓመቱ አልበሽር የሚመሩት የሱዳን መንግስት ጉዳዩን ከመሰረታዊ ሸቀጦች ተቃውሞ ያለፈ መሆኑን በመግለጽ ከረር ወዳለ ደረጃ አድርሶታል። በካርቱም በሺዎች አደባባይ ሲወጡ በተነሳ ተቃውሞ ላይ አልሞ ተኳሾች ሶስት ወጣቶችን እና አንድ ዶክተርን በጥይት መምታታቸውን የአይን እማኞች በገለጹበት ወቅት የሱዳን መንግስት ጣቱን ወደዳርፉር ቀስሯል።
የሱዳን መንግስት በምዕራባዊው የዳርፉር ግዛት የሚገኙ የሰለጠኑ ቡድኖች ከተቃውሞው ጀርባ እጃቸው እንዳለበት እየገለጸ ይገኛል። በእስራኤል የደህንነት አካላት ስልጠና ወስደው መንግስት ላይ አደጋ ለመጣል ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል በሚል የዳርፉር ወጣቶች ታስረዋል። የወጣቶቹ ጓደኞች ግን ጉዳዩ የሃሰት ውንጀላ መሆኑን በመግለጽ በመንግስት ላይ ተቃውሟቸውን አበርትተዋል። ይህም የዳርፉርን ግጭት ይበልጥ እንዳያባብሰው ተሰግቷል።
የአልጀዚራ ዘገባ እንደሚያመለክተው ደግሞ በሱዳን አሁን ላይ የእናቶች ሰቆቃ በርትቷል። አንድ የካርቱም ነዋሪ እናት ለአልጀዚራ እንደገለጹት፤ ልጆቻቸው ከቤት እንዳይወጡ ጥንቃቄ እያደረጉ ይገኛል። ምክንያቱም ከውጭ የሚሰማው የጥይት ድምጽ እንዲቀላቀሉ አይፈልጉም። ይህ ተደማምሮ የከተማዋን እንቅስቃሴ እንዲገደብ እያደረገው ይገኛል።
የአልበሽር መንግስት ቃል አቀባይ እንዳሉት እስከአሁን ድረስ 800 የሚደርሱ ሰዎች ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ ታስረዋል። ጉዳዩ ያሳሰባቸው የተለያዩ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች የሱዳንን መንግስት እየኮነኑት ይገኛል። ይሁንና አልበሽር እ.አ.አ በ2020 የሚካሄደው የሱዳን ምርጫ እስከሚያልቅ ድረስ ቀሪ የስልጣን ዘመን እንዳላቸው በአደባባይ ወጥተው ተናግረዋል። የሚመሩት ፓርቲያቸው ደግሞ ለቀጣዩ ምርጫም እጩ አድርጎ እንደሚያቀርባቸው እየተገለጸ ይገኛል።
አዲስ ዘመን ጥር 4/2011
ጌትነት ተስፋማርያም