እአአ 2018 ተጠናቅቆ 2019 ገብቷል፤ በአመቱም ውስጥ በርካታ ሁነቶች ተከናውነዋል። ከተከናወኑትና በከፍተኛ ደረጃ ሲያነጋግሩ ከነበሩት ጉዳዮች መካከል በኩባ ስልጣን ከካስትሮ ቤተሰብ እጅ መውጣቱ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ በሩሲያ አራተኛው ዙር የፕሬዚዳንት ፑቲን ምርጫ፣ የአሜሪካው ትራምፕ ዳግም ምርጫ (mide-terme election)፣ የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ የቻይናና አሜሪካ የንግድ ጦርነት፣ የሰሜን ኮሪያ ከኒውክሌር ጦር መሳሪያ ጋር በተያያዘ የነበረው እሰጥ አገባ፣ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ከፍተኛ እድገት ከመመዝገቡ ጎን ለጎን የሳይበር ወንጀል መበራከቱ እጅግ ጥቂቶቹ ናቸው።
አመቱ በህዝቦች ዘንድ የፈጠረው ስሜት፣ ያሳደረው ተጽእኖ፤ ከፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና መልካም አስተዳደር አኳያ ምን ምን ሁነቶች ተከናውነዋል፤ መጪው 2019 ከ2018 ምን ተረከበ? የሚሉት በዚህ ጽሁፍ ለትውስታ ያህል ገረፍ ገረፍ የሚደረጉ ናቸው። የአለምን ፖለቲካ ከምትዘውረው አሜሪካ እንጀምር።
ሲኤንቢሲ ያነጋገራቸው አሜሪካዊው የፋይናነስና ኢንቨስትመንት ስትራቴጂስት ሌዊስ ዎከር እንደሚሉት ከሆነ ላለፉት ሁለት አስርት አመታት ግብይቱ (ስቶክ ማርኬት)ን ከበድ ከበድ ያሉት ስጋቶች ማለትም የንግድና ገበያው ጦርነት፣ የግብር ስርአት/ጫና እና የመሳሰሉት ገጥመውት ቆይቷል። እነዚህ የሚወገዱ ከሆነ በ2019 በግብይት ስርአቱና አጠቃላይ ኢኮኖሚው ላይ ከፍተኛ ለውጥ ይመጣል።
እንደ ፎርበሰዶትኮም ያነጋገራቸው ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ከሆነ 2018 ጥሩ ጥሩ ሃሳቦች የነጠፉበት፣ አሰሪ ያልሆኑ ህጎች የበዙበት ሆኖ ነው ያለፈው፤ በ2019 እነዚህ ሁሉ ማነቆዎች ተፈትተው የተሻለ ነገር፤ በተለይ በኢኮኖሚው ዘርፍ እናያለን ብለን ተስፋ እናደርጋለን ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። አስተያየት ሰጪዎቹ ዘርዘር አድርገው ከተናገሩት መረዳት እንደተቻለው የንግድና ኢኮኖሚው ሁኔታ ተቀዛቅዟል፤ አመቱ ኪሳራ የበዛበት፤ ትርፍ የራቀበት ሆኖ ነው ያለፈው።
ሌላው ከዚሁ ከፋይናንስና ኢኮኖሚው ጋር በተያያዘ በተጠናቀቀው አመት የተስተዋለው ሁነት ከጣራ በላይ የወጣው ዝርፊያ ነው።
ደረጃው ይለያያል እንጂ ሙስናው የትም ነው፤ የትም በመሆኑ ከአጠቃላይ 7 ነጥብ 616 ቢሊዮን (2018) የአለም ህዝብ ስድስት ቢሊዮን የሚሆነው ሙስና በተንሰራፋባቸው አገራት ውስጥ ነው የሚኖረው፡፡ 2019 ከ2018 ከተረከባቸው ከባድ ከባድ ሀላፊነቶችና ፈተናዎች አንዱና ውስብስቡ ይሄው ሙስናና አጃቢዎቹ መሆናቸው በስፋት እየተነገረ ይገኛል። ዓለማችንም በሙስና፤ በተለይም አንዱ ዘርፍ በሆነው በገንዘብ ማሸሽ ብቻ በየዓመቱ ከ600 ሚሊዮን እስከ 1.5 ትሪሊዮን ዶላር እያጣች መሆኗን ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናልን የመሳሰሉ ተቋማት ማስታወቃቸው የሚዘነጋ አይደለም።
ይህ የዘመኑ ፈተና ስር ሰዶና ተንሰራፍቶ የሚገኘው በተለይ ከሰሀራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገራት መሆኑን ከዚሁ ከትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል ከአለም ባንክ ጥናት መረዳት የተቻለ ሲሆን፤ ምእራብ አውሮፓ፣ ማእከላዊ ኢስያ እና ሌሎቹም ጋ ሙስናው የጦፈ መሆኑ አረጋግጧል።
ሰሞኑን ኤፍቲዶትኮም ድረገጽ እንደዘገበውና አዲስ ዘመን እንዳስነበበው አፍሪካ በዓመት በተለያዩ ስርቆቶች 148 ቢሊዮን፤ በህግ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ሁለት ትሪሊዮን ዶላር ታጣለች። ከ2002 እስከ 2006 በየአመቱ ከ859 ቢሊዮን እስከ 1ነጥብ06 ትሪሊዮን ዶላር ያጣችው አፍሪካ በ2008 ብቻ 1ነጥብ8 ትሪሊዮን ዶላር ተዘርፋለች፤ ይህም ከእያንዳንዱ አፍሪካዊ 989 ዶላር የተወሰደበት መሆኑን ያሳያል። እንደግሎባል ፋይናንሻል ኢንተጊሪቲ ጥናት የአፍሪካ መንግሥታት ችግሩን ለመፍታት ያላቸው ቁርጠኝነነት እጅጉን አናሳ ነው።
ጥናት ከተደረገባቸው ከ28 ሀገራት መንግሥታት 18ቱ ምንም ዓይነት ርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ አይደሉም፤ ወንጀሉም ከቁጥራቸው ውጪ እየሆነ ይመስላል። ከዚህ አንጻር እአአ በ2019 እነዚህ ሁሉ ችግሮች ይፈታሉ ተብሎ በተስፋ እየተጠበቀ ይገኛል።
በተለይ 2018ን “የጸረ-ሙስና አመት” እንዲሆንና በአጠቃላይ አህጉሪቱ ተግባራዊ እንዲሆን ከወሰነው አፍሪካ ህብረት ብዙ ይጠበቃልና በ2019 ችግሩ መፍትሄ ይበጅለታል ተብሎ ቢታሰብና፤ ተስፋም ቢደረግ የሚገርም አይሆንም።
ሌላው በአመቱ ውስጥ በአስከፊነቱ የተመዘገበው የሰብአዊ ቀውስ ጉዳይ ሲሆን ቀውሱ ያስከተለው ቁሳዊ ውድመትም በቀላሉ የሚታይ ሆኖ አላለፈም። ዳሰሳችን በወፍ በረር ነውና ለጊዜው ሰብአዊ ቀውሱን ብቻ ጠቅለል አድርገን እንመለከት።
በቅርቡ ፎርብስ እና ዩዝፎርሂዩማን ራይትስዶትኮም እንደዘገቡትና የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ በዚሁ ጋዜጣ ላይ እንደጠቀሰው 286 ሚሊዮን ህጻናት ሰብአዊ መብታቸው ተገፎ ለስቃይና መከራ፤ 300ሺህ የሚሆኑ ደግሞ በእርስ በርስ ጦርነትና ግጭት ምክንያት ለጉልበት ብዝበዛ፣ ከ600 እስከ 800ሺህ የሚደርሱ ሰዎች ለስደት ተዳርገዋል፡፡ የህዝብ ቁጥራቸው 250ሺህ በሆኑ ከተሞች 100 በመቶ የዘረፋ ተግባራት ይካሄዳል፤ የነዋሪዎች መብት ያለማቋረጥ ይጣሳል፡፡ የአሁኑ 2018 ዘመን የአለማችን ገጽታ ይህን ይመስላል፡፡ ግፉ በዚህ የሚያቆም ሳይሆን ይቀጥላል።
አለም ባንክና አለም አቀፍ የስራ ድርጅት (ILO) እንዳስታወቁት በአሁኑ ሰአት 60 በመቶ የሚሆኑት የአፍሪካ ወጣቶች ስራ አጥ ናቸው፤ ትምህርት የለም፤ ስራ የለም፡፡ የአለም ጤና ድርጅት ተደጋጋሚ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት በአፍሪካ ጤናም የለም። ይህ በያያዝነው አመት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው መፍትሄ ሊፈለግለት የሚገባ ስለመሆኑም ሪፖርቶቹ ያሳስባሉ፡፡
በ23 አገራት የሚገኙ 39 ሚሊዮን ህዝቦች በከፍተኛ የምግብ እጥረት ስር ወድቀዋል፤ ይህም ራሱን የቻለ ልዩ ትኩረት የሚፈልግ በመሆኑ በ2019 በሚገባ ሊሰራባቸው መፍትሄ ሊበጅላቸው ከሚገቡት መካከል አንዱ ነው፡፡እአአ 2019 ከ2018 የተቀበለው ሌላውና ዘግናኙ ሁነት ጦርነት ነው።
በመካከለኛው ምስራቅ ጋብ ሊል ያልቻለው ጦርነት፤ በተለይም በየመን፣ ሶሪያ፣ ኢራቅ እና ፍሊስጤም፤ በደቡብና መካከለኛው እስያ (አፍጋኒስታን፣ ማይነማር እና ባንግላዲሽ) ያለው የርስ በርስ ግጭት፤ በመካከለኛው እና ምስራቅ አፍሪካ (ደቡብ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ኮነጎ፣ ቡሩንዲ፣ ሱዳን . . .) የሚታየው የሰዎች መፈናቀልና አሳሳቢ የጸጥታ ችግር፤ መፍትሄ ያጣው ግጭትና አለመረጋጋት በምእራብና ሳህል (ሰሜን-ምስራቅ ናይጄሪያ፣ ቻድ፣ ኒጀር፣ ሴኔጋል፣ ማሊ፣ ሞሪታኒያ እና ቡርኪና ፋሶ)፤ በምስራቅ አፍሪካ (ሶማሊያ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬኒያ እና ኡጋንዳ) ያለው ድርቅና ያስከተለው ረሀብ፤ በደቡባዊ አፍሪካ (ዚምባቡዌ፣ ሞዛምቢክ እና ማዳጋስካር) የሚታየው የአየር ንብረት መዛባት፤ በላቲን አሜሪካና ካሬቢያን (ጉዋተማላ እና ሀይቲ) የተከሰተው ያልተጠበቀ ንፋስና ደረቃማነት፤ የሴቶች የፍትህና እኩልነት ጥያቄዎች – በተለይ በአፍሪካ፤ በ2018 ካጋጠሙና የአለም መነጋገሪያ ከነበሩት መካከል ቀዳሚዎቹ ናቸው። ሁነቶቹ ባብዛኛው ወደ2019 የተሸጋገሩ ሲሆን አፋጣኝ መፍትሄንም የሚሹ ጉዳዮች ናቸው።
ከተጀመረበት እአአ 2013 አንስቶ ከ380 ሺህ እስከ 400 ሺህ ዜጎች የተቀጠፉበት የደቡብ ሱዳን ጦርነት 20 ሺዎቹ ያለቁት በዚሁ በተጠናቀቀው አመት ነው (አጠቃላይ ህዝቧ 10 ሚሊዮን ነው)። ከዕልቂቶች ሁሉ የከፋው እልቂት የደረሰው የ18 ሚሊዮን ህዝብ መኖሪያ በሆነችው ሶሪያ ምድር ሲሆን፤ እአአ ከ2011 ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የእርስ በርስ ጦርነት አገሪቱ ከ500 እስከ 600 ሺህ የሚሆኑ ዜጎቿን በሞት ተነጥቃለች። (ከነዚህ ውስጥ 19ሺ666 ሺዎቹ የሞቱት በዚሁ (ከእስካሁኖቹ የጦርነቱ አመታት በሙታን ቁጥር ትንሹ ተብሎለታል) በተጠናቀቀው አመት ነው።) ምንም እንኳን 2019 ከ2018 የተረከበው ይህን ሁሉ ሲሆን ሁሉም በዚሁ በያዝነው አመት የመጨረሻ መፍትሄ ያገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ሌላው እአአ በ2018 በከፍተኛ ደረጃ የትኩረት ነጥብና መወያያ አጀንዳ የነበረው፤ በቅርቡ ቡድን 20 ጉባኤ ላይ ሲያወዛግብ የቆየው በአለም አቀፍ ደረጃ 815 ሚሊዮን ሰዎች ከድህነት ወለል በታች መኖራቸው፤ እነዚህን ለመታደግና ዘላቂ የምግብ ዋስትናን ለመረጋገጥ በየአመቱ 30 ቢሊዮን ዶላር የሚያስፈልግ መሆኑ፤ ይህንንም ለማድረግ፣ በተለይ ለአፍሪካ አገራት (በተለይም ከሰሀራ በታች ላሉት) ድጎማ ለማድረግና ብድር ለመስጠት ቃል የገቡ ቱጃር አገራት ቃላቸውን አለማከበራቸውና በአፍሪካ ሙስናና ብልሹ አስተዳደር መንገሱ፤ ይቀንሳል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረው የስራ አጡ ቁጥር ባለፉት ተከታታይ አምስት ወራት በተደረገ ተከታታይ ጥናት በ4ነጥብ1 በመቶ እየጨመረ የመምጣቱ ጉዳይ ወደ 2019 የተንከባለሉና አስቸኳይ መፍትሄን በመጠባበቅ ላይ ያሉ ጉዳዮች ናቸው። አሁን ደሞ ወደ ጤናው መንደር እንብረር (በረራችን አንድም ገጽ፤ እንዲሁም ጊዜ ስለሌለን ነው)።
በ2018 በካንሰር 9ነጥብ6 ሚሊዮን፣ ሲጋራ በማጨስ 5 ሚሊዮን፣ 1ነጥብ7 ሚሊዮን ህዝብ በኤችአይቪ/ኤድስ አልቋል።
ከላይ ያየናቸው ችግሮች ባንድም ይሁን በሌላ ኢትዮጵያን ይመለከታሉ፤ ያንን ስንል ግን ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው አመት ምንም ስራ አልሰራችም ማለት አይደለም፤ ከራሷም አልፎ ለአለም ምሳሌ የሚሆን ስራ ሰርታለች። በተለይ የኢትዮ-ኤርትራን ድንበር ውዝግብ መፍታቷ፣ ከተቃዋሚዎች ጋር ስምምነት መፍጠሯ (በተለይ ከኦጋዴን ነጻ አውጪ ጋር)፣ የጠ/ሚ/ር ሀይለማርያም ደሳለኝ በፈቃደኝነት ከስልጣን መልቀቅ፣ በካቢኔ አወቃቀር ወቅት ለስርአተ-ጾታ ተመጣጥኖ ልዩ ቦታን መስጠቷ እና በመሳሰሉት ክንውኖች በመልካም ተሞክሮነት የአለሙ መነጋገሪያ ሆና መሰንበቷ አይዘነጋም።
የተጠናቀቀው አመት ከላይ በፈጣንና አጭር ዳሰሳ የተመለከትናቸውን ዋና ዋና ሁነቶች አስመዝገቦ አልፏል። ከቀናት በፊት የገባው 2019ም በራሱ ምንም ማለት አይደለም፤ ከጊዜ ቀመርነት ያለፈ ምንም አይነት ፋይዳ የለውም። ፋይዳ ሊኖረው የሚችለው በአግባቡ ሊጠቀምበት የሚችል አካል ሲኖር ነው። ይህ ደግሞ በቀጥታ የሚመለከተው አለምን እየመሯት ያሉትንና ተጽእኖ ፈጣሪዎችን ነው። የነሱ ብርታት ለህዝብ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር፣ ለአለም ሰላም . . . የብረት ምሰሶ ነው፤ ድክመታቸው ደግሞ ከዚህ ተቃራኒ።
ጽሁፋችንን የጀርመኗ መሪ መርኬል አዲሱን አመት አስመልክተው ንግግር ባደረጉት ወቅት ባነሱት ፍሬ-ሃሳብ እናጠቃለው፤ የአየር ለውጥን፣ ስደትን፣ ሽብርተኝነትን የመሳሰሉ አለም አቀፍ ጉዳዮችን ለመፍታት አለም አቀፍ ትብብር የግድ ያስፈልጋል፤ ለራሳችን ስንል እነዚህን ችግሮች ማስወገድ አለብን፤ ይህ ደሞ ሊሳካልን የሚችለው የሌሎችንም ፍላጎት መረዳት ስንችል ብቻ ነው። ይህ ካልሆነ አለም አለማችን መሆኗ ቀርቶ ዳግም፤ ልክ እንዳሳለፍነው 2018 ሀዘናችን መሆኗ አይቀርም። ያ እንዳይሆን ሁሉም እጅ ለእጅ ተያይዞ ሊሰራ ይገባል እንላለን።
አዲስ ዘመን ጥር 1/2011
ግርማ መንግሥቴ