ሰዎች “ሙዚቃ ሳዳምጥ ነው የሚቀለኝ”፤ “ሙዚቃ ስሰማ ነው ቶሎ ቶሎ ስራ የምሰራው”፣ ወዘተ ሲሉ እንሰማለን። ይሄም የሚያሳየው ምን ያህል ሰዎች ላይ ሙዚቃ ተጽዕኖ እንዳለው ነው። ሙዚቃ ብዙ የስነ-ልቦናዊ ጥቅሞች እንዳሉት ይታመናል። አንዳንድ ጥናቶችም እንደሚያመለክቱት ስራ እየሰሩ በበስተጀርባ ሙዚቃ መክፈት የአንድ ሰውን የእሳቤ ክህሎት ይጨምራል። ሙዚቃ ማዳመጥ ውጥረትም ለመቀነስ ይረዳል።
እንደ ግለሰቡ ቢለያይም የሚወዱትን ሙዚቃ ማዳመጥ ዘና ለማለት እንደ አንድ መሳሪያ ያገለግላል። አንድ ሙዚቃ ለውጥረት ይረዳል ስንል እንደ ሙዚቃው አይነት እና አድማጩ በሙዚቃ መደሰትን ይጠይቃል። የምንወደውን ሙዚቃ ስናዳምጥ አእምሮአችን “ዶፓሚን” የተባለውን ሆርሞን በማመንጨት ውጥረትን ይቀንሳል። በተጨማሪም የተሻለ የመነቃቃት ስሜትን ይፈጥራል።
አንዳንድ ሰዎች ደግሞ ሙዚቃ እያዳመጡ ሲያጠኑ በትምህርታዊ ፈተናዎች ላይ በተሻለ ሁኔታ እንደሚሰሩ ይታያል። ትኩረታቸውን እንደሚስብ እና ያዳመጡትን ሙዚቃ ካነበቡት ነገር ጋር በማያያዝ በበለጠ ደረጃ ማስታወስ መቻላቸውም የውጤታማነታቸው ምክንያትም እንደሆነ ብዙ የስነ-ልቦና ጥናት ውጤቶች ያስረዳሉ። ሙዚቃ በማህደረ ትውስታ (Memory) ላይ መልካም ተጽዕኖ ቢኖረውም ውጤቱ ግን እንደ ግለሰቡ ሊለያይ እንደሚችልም እነዚህ ጥናቶች ያሳያሉ።
ሙዚቃን በተለይም ረጋ ያሉትን አንዳንድ ሰዎች ለእንቅልፍ ሲጠቀሟቸው ይስተዋላል። የሙዚቃ ሳይኮሎጂም ይህን ልምድ ሳይንሳዊ በሆነ መልኩ የሚደግፈው ሲሆን ከእንቅልፍ ጋር የተያያዙ የጤና እክሎችንም ለማከም ቀላልና ውጤታማ የሆነ ዘዴም እንደሆነ ያሳያል። ሙዚቃ በተጨማሪ የተነሳሽነት ስሜትን ለማምጣት ይጠቅማል። አንዳንድ ስራዎችን ስንሰራ ወይም ከመስራታችን በፊት ሞቅ ያሉ ሙዚቃዎች ስናዳምጥ እንደ ‘ሚያነቃቁን እና ስራ እንድንሰራ የበለጠ አነሳሽነት እንዳላቸው ይታያል።
ሰዎች የሚያዳምጡት ሙዚቃ ስብዕናቸውን የሚያሳይ ወይም የሚያንፀባርቅ በመሆኑ አብዛኛውን ጊዜ የሙዚቃ ምርጫቸው ሰዎች ሲያጣጥሉባቸው ደስተኞች አይሆኑም። ከስብዕናቸው ጋር ከመገናኘትም ባሻገር ሰዎች የሚያዳምጡትን ሙዚቃ በወቅቱ ከሚሰማቸው ስሜትም ጋር በማያያዝ እንደ ንግግር ይጠቀሙበታል። የምንሰማቸው የተለያዩ የዘፈን ዓይነቶች የኛን ለነገሮች ያሉንን አመለካከት የመቀየር ሃይል አላቸው። እያንዳንዱ ሰው ነገሮችን የሚመለከትበት መንገድ አለው። እናም አንዳንድ ሰዎች የራሳቸውን ስሜት በግጥሞቻቸው ወይም በመሳሪያቸው በሚጫወቱት ዜማ በሚገልጹበት ጊዜ ከዚያ የአስተሳሰብ መንገድ ጋር እንስማማለን። ይህም ማለት አሳዛኝ ዘፈኖችን ስናዳምጥ እናዝናለን፣ የሚያነቃቃ ሙዚቃ ስናዳምጥ ደግሞ ደስተኝነት ስሜት ይሰማናል።
ሙዚቃ ማዳመጥ ወይም መጫወት በሰው ላይ ያለው ተጽዕኖ ትልቅ በመሆኑ እሱን መሰረት ያደረገ የስነ-ልቦና ህክምና ተፈጥሯል። ሙዚቃን መሰረት ያደረገ ሕክምና የአንድ ቡድንን ወይም የግለሰብን አካላዊ፣ ስሜታዊ፣ አስተሳሰባዊ እና ማህበራዊ ፍላጎቶችን ለመግለጽ ይጠቅማል። ዜማ ማዳመጥ፣ መሣሪያ መጫወት፣ ከበሮ መምታት፣ ዘፈኖችን መፃፍ ወ.ዘ.ተ. ያሉ የተለያዩ ተግባራት ለጤና ጠቀሜታ አላቸው።
የሙዚቃ ህክምና አእምሮአዊ፣ አካላዊ፣ ባህርያዊ ሁሉንም ገጽታዎችን ይነካል። ሙዚቃ ለአእምሮ ትኩረትን ሊሰጥ ይችላል፣ እናም ስሜታችንን ሊቀይር ይችላል፣ ይህ ደግሞ በተራው በባህርይው ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል።
የሙዚቃ ሕክምና ለብዙ ነገሮች ውጤታማ ነው። ሙዚቃ በአእምሮ ውስጥ የንግግር ቦታዎችን ያነቃቃል በሂደትም ንግግርን ለማዳበር ሊረዳ ይችላል። በአንጎል ውስጥ በማተኮር ኃላፊነት ያላቸውን አካባቢዎች በማነቃቃት ትኩረትን ይጨምራል። አዕምሮ ውስጥ ያሉትን ከስሜት ጋር የተገናኙ ሥርዓተ-አካሎችን አሰራር ያቀላጥፋል፣ ግንኙነቶችን ያጠናክራል፣ እንዲሁም ለማሳየት የሚከብዱ ስሜቶችን ለመግለጽ ይረዳል።
ጥር በርካታ መንፈሳዊና አለማዊ ተግባራት የሚከበሩበት ወቅት ሲሆን፤ ለኛ 5ኛ የሆነው ጥር ለባህር ማዶዎቹ ደግሞ የአዲስ አመት የመጀመሪያ ወራቸው በመሆኑ ለሁለታችንም የደስታ ወቅት ስለሆነ ያመሳስለዋል። ከዛ ውጪ ከቀን አቆጣጠር አኳያ ያለው ልዩነት ያው እንደተጠበቀ ነው።
በላቲን “ጃኒሪያየስ” በመባል በጃኑስ አምላክ ስም የሚጠራው የጥር ወር “የሰርገኞች ቀን” በሚል ባህላዊ ስያሜው የሚታወቅ ሲሆን ከወርሀ የካቲት ጋር በመግጠም የሰርግ ሂደቱን ከፍ እንዲል የሚያደርጉና የወራቶቹን ሁሉ አማካይ ቦታን የያዙ ናቸው።
የሩሲያን የወራት ስያሜ፣ አመጣጥና ትርጓሜ በተመለከተ የተጠኑ ጥናቶች “የጥር ወርን ሰማይ በጥልቀት ይመልከቱ እና ስሙን ሙሉ በሙሉ የሚያጸድቅ መሆኑን ይገነዘባሉ።” የሚል አስተያየት አስፍረው እናገኛለን። ምናልባት ይህ ብያኔ ከእኛ ጋር ምን ያህል ይሄዳል/አይሄድም የሚለው ሌላ ጉዳይ ሆኖ የሚገናኙበት ጉዳይ የለም ማለት ግን አይቻልም።
ጥር በእኛ ብቻ ሳይሆን በብዙዎችም ይወደዳል። በመሆኑም ይመስላል ከሌላው ሁሉ አልፈው ለአገራቸው መጠሪያ ስም እስከማድረስ የዘለቁት፤ በፖርቹጋልኛ “ሪዮ ዴ ጄኔሮ” የሚለው ስም “የጥር ወር” ማለት መሆኑን፤ “ፈጣሪ ዓለምን በስድስት ቀናት ውስጥ ፈጠረ፣ በሰባተኛው ቀን ደግሞ ሪዮ ዲ ጄኔሮን ፈጠረ” በማለት የሚያምኑት ብራዚላዊያን ዋናና ውብ ከተማቸውን ሪዮ ዴ ጄኔሮ (1763 እስከ 1960) ሲሉ መሰየማቸው እያወራንለት ስላለው ጥር ወርና አለም አቀፍ ይዞታው ጥሩ ማሳያ ነው።
በጥንቱ የሩሲያ አፈታሪክም “ባለ ሁለት ፊት ያለውን አምላክ ጃኒስን ለማስደሰት፣ ሁለተኛውን የክረምት ወር በክብሩ ስም – ‘ጥር’ ወይም ‘ክፍል’ ብለው ሰየሙት።” የሚል መኖሩም ጥር በእኛ ብቻ ሳይሆን በሌሎች በርካቶችም ተወዳጅና ተመራጭ እንደሆነ ያመለክታል።
በስኮትላንድ ውስጥ ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የ“የመጀመሪያው እርምጃ” በመባል የሚታወቀው ልማድ እስካሁን ተጠብቆ ቆይቷል። በስኮትላንድ ከእኩለ ሌሊት በኋላ፣ ወንዶች ወደ ሴት ጓደኞቻቸው፤ ሴቶችም ወደ ወንድ ጓደኞቻቸው በመሄድ ይተዋወቃሉ፡፡ ወደ እኛ ስናመጣው በጥምቀት በአል እለት ካለው “ሎሚ የመወራወር …” ባህል ጋር አንድ ነው ባይባልም ርቀቱ ብዙ ነው ማለት ግን አይሆንም።
ጥርን ከሁሉም የተለየ ከሚያደርጉት አንዱ ደማቁና በልዩ ሁኔታ የሚከበረው የጥምቀት በአል (ነጮቹ አስፍተውት “African Epiphany/የአፍሪካ ኤፒፋኒያ” ነው የሚሉት) በአሉን በ”የሰው ልጅ ወካይ የማይዳሰስ ባህላዊ ቅርስ”ነት በዩኔስኮ ለማስመዝገብ ሲደረግ የነበረው ጥረት መሳካቱና በአለም ትልቁ የአደባባይ ላይ በአል በመሆን የአለም ቅርስ ለመሆን የበቃበት ወቅት መሆኑ ነው።
ከጥንት ጀምሮ የሰላም፣ የፍቅር፣ የአንድነትና ወንድማማችነት ተምሳሌት በመሆን እዚህ የደረሰው የጥምቀት በአል ከሀይማኖታዊና መንፈሳዊ እሴቱ ባሻገር ለእያንዳንዳችን የመንፈስ ኩራትን የሚያጎናፅፍ፤ የአገራችንን መልካም ገፅታ የሚገነባ መሆኑም እውቅናውን ካገኘ ወዲህ በውጪ ሚዲያዎች ሳይቀር እየተነገረለት ይገኛል።
እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ በ30 አመቱ በመጥምቁ ዮሀንስ እጅ በዮርዳኖስ ባህር የተጠመቀበትን እለት የሚያስታውስ፤ በየአመቱ ጥር 11 ቀን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ባለችበት ሁሉ (ውጪም ጭምር) የሚከበረው የጥምቀት በአል ከሀይማኖታዊነቱ ባልተናነሰም ባህላዊና ማህበራዊ ገፅታንም የተላበሰ መሆኑ ደግሞ ከሁሉም ክብረ በአላት ለየት ያደርገዋል። እነዚህና ሌሎች ፋይዳዎቹ ከግምት ውስጥ ገብተውለትም ህዳር 2012 አ/ም በዩኔስኮ እውቅና አግኝቶ በመመዝገብ ከእኛም አልፎ የአለም ቅርስ ሆኗል።
በጥምቀት ከመንፈሳዊው ጎን ለጎን ማህበራዊና ሰዋዊ ጉዳዮችም ይከናወናሉ። ታቦት ይታጀባል፤ ይዘመራል፤ ወረብ ይወረባል። በእግረ መንገድም ማወቅ፣ መተዋወቅ፤ መተጫጨት አለ። ሎሚ ይወረወራል (በዘንድሮ ሎሚ – ኪሎ 70 ብር በገባበት ካልተባለ በቀር)። ከተሳካ ጉዞ ወደ ትዳር ይሆናል ማለት ነው። በየአካባቢውም:-
ሀይ ሎጋ
ሀይ ሎጋው ሽቦ
ይባላል፤ ይጨፈራል፤ ይበላል፤ ይጠጣል። ጎጆ ይወጣል።
ጥር በአብዛኛው የአገራችን ክፍሎች ያለው ትርጉምና ለጥራዊያን የሚሰጠው ስሜት ተመሳሳይ ነው። ብዙም ስራ የማይበዛባቸውና ዘና የሚባልባቸው ወራት ቢኖሩ አንዱ ይሄው ጥር ወር ነው። በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ዘንድ (የመንግስት ሰራተኛ አልተባለም) ይህ ወር ኪስ ሙሉ ነው፤ ወጪ አይፈራም። “ካለ ምን አለ” እንደሚባለው ይመነዘራል። መዝናናት እስከ ጥግ ድረስ ነው። በተለይ ትናንሽ የገጠር ከተሞች የድምቀታቸው ጣራ በዚሁና ግራና ቀኝ ባሉት ወራት ነው።
ከአመቱ በአምስተኛ ወር ላይ የሚገኘው ጥር በኢትዮጵያ ባሕረ ሐሳብ (የዘመን አቆጣጠር) መሠረት የበጋ የመጀመሪያው ወር ሲሆን፤ በርካታ ሁነቶችና ኩነቶችን የሚያስተናግድ ለየት ያለ ወር ነው። ከሚያስተናግዳቸው ሀይማኖታዊና ማህበራዊ ክብረ በአላትና ሌሎች ሁነቶች መካከል ጥምቀት፣ አስተሪዮ ማሪያም እና ሰርግ ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
በሁሉም የሃገሪቱ ክፍሎች በሚከበረው በዚህ በአል የተለያዩ አገራት ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ-ክርስቲያን፣ አምባሳደሮች፣ ጎብኚዎች፣ ጋዜጠኞች … በሚገኙበት እንደሚከበር ይታወቃልና ዘንድሮም ከእስከዛሬው በላይ ደምቆ እንደሚከበር ይጠበቃል።
ባጠቃላይ፤ ጥራዊያን (በጥር ወር የሚጋቡ፣ የሚተጫጩ፣ መንፈሳዊም ይሁን አለማዊ፣ ሀይማኖታዊም ባህላዊ፤ ለሙሽሪትም ይሁን ለሙሽራው) ወሩ የሰላም የጤና፣ የደስታ፣ የፍቅርና የአብሮነት እንዲሆንልን እንመኛለን።
አዲስ ዘመን ጥር 1/2012