በ2019 በአፍሪካ በኢንቨስትመንት ለመሳተፍ ለሚፈልጉ የተሻሉ የተባሉ አስር ሀገራት በቅደም ተከተል በማስቀመጥ አፍሪካ ዶት ኮም በድረ ገጹ አስነብቧል። እነዚህ ሀገራት ቀልጣፋ የኢንቨስትመንት አገልግሎት ከማቅረብ ዝቅተኛ ታክስ እስከማስከፈል የተለያዩ አማራጮችን ያቀረቡ ሲሆን፣ በዚህ መስፈርት ከተመረጡት መካከል ኢትዮጵያ በአምስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ድረ ገጹ በምንጭነት የዓለም አቀፉን የገንዘብ ተቋም አይ ኤም ኤፍንና የዓለም ባንክ ያወጧቸውን መረጃዎች በምንጭነት ተጠቅሟል።
ለኢንቨስትመንት ተመራጭ በመሆን በመጀመሪያ ደረጃ የተቀመጠችው ላለፉት አስራ ዘጠኝ ዓመታት በየዓመቱ የስድስት በመቶ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገበች ያለችው ሩዋንዳ ናት። ሀገሪቱ ባለፈው ዓመት በአካባቢው ከፍተኛ የኢንቨስትመንት እንቅስ ቃሴ ማስመዝገብ ችላለች። የዓለም ባንክ ሪፖርት እንደሚያመለክተው ሀገሪቱ ከ16 ዓመት በፊት የተጠናከረ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ከጀመረች ጊዜ አንስቶ ጠንካራ ለውጥ እያስመዘገበችም ትገኛለች። ለዚህ ውጤት ካበቋት ሥራዎቿ መካከልም ቢሮክራቲክ የነበረውን የቢዝነስ መዋቅር ወደ ኤሌክትሮኒክስ መቀየር፣ ለተጨማሪ እሴት ታክስ የተለየ የኮምፒውተር ፕሮግራም አገልግሎት ማዘጋጀት፣ ከነጻ የሶፍት ዌር ጋር ማቅረብ፣ ግብር ከፋዮች ይሄንን ተጠቅመው የፈለጉበት ቦታ መረጃ ማግኘትና መገልገል የሚችሉበትን ሁኔታ መፍጠሯ መሆኑ ተጠቅሷል።
ኢንቨስትመንት ለሚጀምሩ ብድር በማመቻቸት ባላት ተመራጭነት የሁለተኛነት ደረጃን የያዘችው ሁለተኛዋ ሀገር የምስራቅ አፍሪካዋ ኬንያ ናት። የዓለም ባንክ ሪፖርት እንደሚያመለክተው በሁለት ዓመት ውስጥ ሀገሪቱ አጠቃላይ የንግድ ሥራ እንቅስቃሴን በተመለከተ 31 ተግባራትን አከናውናለች። ከነዚህም መካከል አንደኛው ለኢንቨስትመንት ብድር አገልግሎት የሚገኝበትን መንገድ ለማላላት ህግ ማውጣት ሲሆን፤ በተጨማሪም መንግሥት ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ጋር በጥምረት በመሆን በስሩ ላሉ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ዘመናዊ ኤሌክትሮኒክስ አገልግሎቶችን ለማቅረብ ተስማምቷል። ይህም ተገልጋዮችን ከምዝገባ ጀምሮ የቀጥታ አገልግሎት በመስጠት ክፍያን ለማከናወንና ሰርተፍኬትን ለመቀበል የሚያስችል በመሆኑ እስካሁን የነበረውን የተንዛዛ ሥርዓት ቀለል የሚያደርገው መሆኑ ተጠቁሟል።
እንደ ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ሪፖርት የሀገሪቱ ኢኮኖሚ የስድስት ነጥብ አንድ በመቶ እድገት እያስመዘገበ እንደሚቀጥል ተተንብዮል። የዓለም ባንክ ግምት ደግሞ በአምስት ነጥብ ስድስት በመቶ እድገቱ እንደሚቀጥል ያሳያል። ሀገሪቱ በምስራቅ አፍሪካ ጠንካራ የመረጃና ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ፣ የፋይናንስ እንዲሁም ትራንስፖርት አገልግሎት ማእከል ሆና እንደምትቀጥል ሁሉም ይስማማሉ።
በሦስተኛ ደረጃ ተመራጭ የሆነችው ሀገር ጋና በ2016 የተደረገውን የመንግሥት ለውጥ ተከትሎ መንግሥት ከነዳጅ ዘይትም ሆነ ከእርሻ እንቅስቃሴ ውጪ ያለውን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት የነጻ ኢኮኖሚ ሥርዓት ዘርግቷል። በጋና ወርቅ፣ ዘይትና ኮካ ለኢኮኖሚው የ47 ቢሊዮን ዶላር ምንጭ ናቸው። ሀገሪቱ በ2010 ነዳጅ አምራች መሆኗን ተከትሎ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተከታታይ እድገት ማስመዝገብም ችላለች፡፡ በአሁኑ ወቅት እየተሠራበት ያለው የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጥም ከወረቀት ውጪ ወደ መሆን ተሸጋግሯል። ጋና በ2015 የ918 ሚሊዮን ዶላር ብድር ከተፈራረመች ጀምሮ መንግሥት የሚያካሂደው የጠንካራና ዘላቂ የኢኮኖሚ ግንባታ ለአይ ኤም ኤፍ የሚመለሰውን ገንዘብ በጊዜ ለመጨረስ ታሳቢ ያደረገ መሆኑ ተገልጿል። የዓለም ባንክ የንግድ ሥራ ሪፖርት እንደሚለው ከሆነ ግን ጋና ከዚህ በበለጠ የገቢ ንግዷን የተሳለጠ ማድረግ ይጠበቅባታል።
ከዓለም ትልቋ የካካዎ ላኪ የሆነችው ሀገር ኮትዲቯር በኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የተረጋጋ የፖለቲካ ሁኔታ በመፍጠሯ አበረታች ለውጥ እያሳየች ትገኛለች። ሀገሪቷ በቀላሉ ኢንቨስትመንት ለማከናወን ከሚመረጡ አስር የዓለም ሀገራት ተርታም ገብታለች። ባለፉት ሁለት ዓመታት ፈቃድ ለማግኘት የሚወስደውን ጊዜ በመቀነስ እንዲሁም ለታክስ ከፋዮችና ለብድር ተጠቃሚዎች ኤሌክትሮኒክስ አገልግሎት ማቅረብ ችላለች። ባለፈው ዓመት ታክስን በተመለከተ የቀጥታ አገልግሎት ማቅረብ መጀመሯን የዓለም ባንክ አስቀምጧል። በኮትዲቯር ግብርና ተኮር የሆነው ኢኮኖሚ በሚቀጥሉት ዓመታት የ7 በመቶ እድገት እንደሚያሳይም ይጠበቃል።
በአምስተኛ ደረጃ የተቀመጠችው ወደብ አልባዋና 100 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ኢትዮጵያ ራሷን የአፍሪካ የማኑፋክቸሪንግ መናኸሪያ እያደረገች እንደምትገኝ በሪፖርቱ ተቀምጧል። የሀገሪቱ መንግሥት ኢንቨስት መንትን ለመሳብ የታክስ ማበረታቻ በማድረግ ለኢንቨስትመንት የሚያገለግሉ መሰረተ ልማቶች ግንባታ በማካሄድ ላይ ይገኛል። ሀገሪቱ ሠራተኞች በተመጣጣኝ ክፍያ የሚገኙባት መሆኗ ተመራጭ እንደሚያደርጋት ተጠቅሷል። በተጨማሪም መንግ ሥት በስፋት የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በመገንባት ላይ መሆኑና በአሁኑ ወቅት ስድስት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ተጠናቀው የቀረቡ ሲሆን፤ በመላው ሀገሪቱ በመገንባት ላይ የሚገኙት ተጨማሪ ዘጠኝ ፓርኮችም በቅርቡ ሥራ የሚጀምሩ መሆናቸው ሌላው ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ አገር የሚያደርጋት መሆኑ ተገልጿል።
ሀገሪቱ ታሪካዊ የፖለቲካ ሽግግር ካደረገችና የለውጡን መሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን ከሾመች በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢኮኖሚውን ለግሉ ዘርፍ የበለጠ ክፍት እንዲሆን አድርገዋል። በዚህም በመንግሥት ቁጥጥር ስር የነበሩትን እንደቴሌ ኮሚዩኒኬሽን፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የኢትዮጵያ ንግድ መርከብና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅትን በዝቅተኛ ድርሻ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ባለሀብቶች ለማስተላለፍ ፈቅደዋል። ይህን ተከትሎ አይ ኤም ኤፍ ሀገሪቱ በ2019 የ ስምንት ነጥብ አምስት በመቶ እድገት በመጓዝ ከአህጉሪቱ ፈጣን እድገት እንደምታስመዘግብ ያለውን ትንበያ አስቀምጧል። የሀገሪቱ ኢንቨስትመንት ኮሚሽንም ከተለያዩ አካላት ጋር በመሆን ኢንቨስተሮች በሀገሪቱ ስለኢንቨስትመንት ያሉትን አጠቃላይ መረጃዎች የሚያገኙበትን የቀጥታ ኦን ላይን የኢንተርኔት አገልግሎት መስጠት መጀመሩም ተቀምጧል። ይሄ እንቅስቃሴዋ ለ2019 ለኢንቨስትመንት ምቹ ሀገር ሆና እንድትመረጥ አድርጓታል።
ትንሿ ደሴትና አነስተኛ ገበያ ያላት በኢንቨስተሮች ብዙም ቦታ ሳይሰጣት የኖረችው አሁን ግን በስድስተኛ ደረጃ የተቀመጠችው ሀገር ደግሞ ሞሪሽየስ ናት። የሞሪሽየስ መንግሥት ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በተከታታይ የሠራው ሥራ ውጤት አምጥቶለት ሀገሪቱ በዓለም ባንክ ለኢንቨስትመንት ምቹ ከሆኑ የዓለም ሀገራት ተርታ 20ኛ ላይ መቀመጥ ችላለች። ሞሪሽየስ የተረጋጋ የፖለቲካ ሁኔታ ያለባት የነፃ ኢኮኖሚ ሥርዓት የምትከተል ስትሆን፣ ዝቅተኛ ታክስ በመክፈል በተረጋጋና ስጋት በሌለበት ሁኔታ ለመሥራት ለሚፈልጉ ኢንቨስተሮች ተመራጭ ሀገር ሆናለች። ሀገሪቱ ባለፈው ዓመት ነጻ የንግድ ስምምነት ከቻይና ጋር በመፈራረም ከአፍሪካ የመጀመሪያዋ ስትሆን በተመሳሳይ ከምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ካሉ የንግድ ተቋማትም ጋር ነጻ የንግድ ስምምነት አድርጋለች።
በሚያማልለው የባህል እንቅስቃሴዋና ዓይን በሚስበው ሥነ ምህዳሯ የምትታወቀው ሞሮኮ በሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ሞሮኮ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለኢንቨስትመንት በፈጠረቻቸው ምቹ ሁኔታዎች ሳቢ እየሆነች በመምጣት የአውሮፓ ሀገራት የአፍሪካን ገበያ ከሚያዩበት መድረክ አንዷ ለመሆን በቅታለች። ከ1211 እስከ በ2019 ሀገሪቱ ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን በተከታታይነት በመፍጠር ከሚመረጡ ሀገራት ደረጃ ከነበረችበት 114ተኛ ወደ 60ኛ ለመቅረብ በቅታለች፡፡ በሀገሪቱ የቱሪዝምና ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ኢኮኖሚውን የሚመራው ሲሆን፣ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ በተሽከርካሪና አውሮፕላን ኢንዱስትሪውም ከፍተኛ ትርፍ የሚያስገኝ እንደሚሆን ይጠበቃል።
የአፍሪካን ትልቁ ኢኮኖሚ የያዘችውና ባልተረጋጋ የፖለቲካ ስጋትና ዝቅተኛ እድገት ውስጥ የምትገኘው ናይጄሪያ በስምንተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። በአሁኑ ወቅት ናይጀሪያ ለኢንቨስትመንት ምቹ ከሆኑ ሀገራት አንድ ደረጃ ዝቅ ብትልም ሀገሪቱ በዓለም ካሉ አርባ ስድስት በተለያየ መስክ የሀብት ምጣኔ ይዞታ ካላቸው ሀገራት ተርታ እንደምትገኝ የዓለም ባንክ መረጃ ያሳያል። ይሄ እንዳለ ሆኖ ሌጎስና ካኖ ከተሞች የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ለመጀመር ተመራጭ ሲሆኑ በእነዚህ ከተሞች የንግድ ምዝገባ ለማካሄድና ለታክስ ክፍያ የተቀናጀ የቀጥታ ድህረ ገጽ አገልግሎት ተዘርግቷል።
ይሄ እንዳለ ሆኖ ወደእዚች ሀገር ለኢንቨስትመንት ለመግባት የሚፈልጉ ባለሀብቶችና ድርጅቶች በ2019 የካቲት አጋማሽ በሙሀመድ ቡሀሪና በቀድሞው ምክትል ፕሬዚዳንት አቲኩ አቡበከር መካከል የሚደረገውን ምርጫ ቢጠብቁ የሚሻል መሆኑም ተጠቁሟል።
በአፍሪካ ሁለተኛውን ትልቅ ኢኮኖሚ የተሸከመችው ደቡብ አፍሪካ በተሻለ የህግና የገንዘብ ሥርዓቷ ለኢንቨስትመንት ባላት ምቹነት በዘጠነኛነት ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡ የፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማን ሥልጣን መልቀቅ ተከትሎ ወደ መንበሩ የወጡት ራማፎሳ የጀመሩትን ኢኮኖሚውን የማነቃቃትና ወደነበረበት የመመለስ እንቅስቃሴ በቀጣዩ ምርጫ የሚኖራቸውን ውጤት ተከትሎ የሚወሰን ሲሆን፤ በ2018 በ0ነጥብ 8 በመቶ በማደግ ላይ ያለቸውን ሀገር የማንቀሳቀስ ተስፋ እንደሚኖራቸው ይገመታል። ለዚህም በመንግሥት ስር ካሉት እንደ ኢስኮም የኃይል ማመንጫና ሳውዝ አፍሪካ ኤር ዌይ ጋር ያለውን እንቅስቃሴ መፈተሽ እንደሚጠበቅም ተጠቁሟል።
በአስረኛ ደረጃ የተቀመጠች ግብጽ በምስራቅ አፍሪካ ተከስቶ የነበረውን የአረብ ቀውስ መረጋጋት ተከትሎ በ2018 በኢንቨስትመንት ምቹነት የደቡብ አፍሪካን ቦታ ለመቀበል በቅታለች። ግብጽ የኢኮኖሚ ሽግግር ፕሮግራሟን የጀመረችው አጠቃላይ ኢኮኖሚውን ለመቆጣጠርና ኢንቨስተሮችን ለመሳብ በ2016 ከአይ ኤም ኤፍ የ12 ቢሊዮን ዶላር ብድር በመቀበል፣ የገበያ ማረጋጋትና አዲስ የታክስ ሥርዓት በመዘርጋት ነበር።
ሀገሪቱ በዓለም ባንክ የ2018 የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ሪፖርት ወደ ስድስተኛ ደረጃ ብትወርድም ይሄን ተከትሎ የተለያዩ ፖሊሲዎችን የማስተካከል እርምጃ በፍጥነት በመውሰዷ በ2019 ወደ ስምንተኛ ደረጃ ከፍ ለማለት በቅታለች። ሀገሪቱ በ2017 በዘርፉ አምስት መሻሻሎችን አካሂዳለች ይሄም በሀገሪቱ ባለፉት አስር ዓመታት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከፍተኛው ነው፡፡ ከነዚህ መካከል ወደ ኢንቨስትመንት ለመሰማራት 16 ቀን ይፈጅ የነበረውን ጊዜ ወደ አስራ አንድ የማውረድና አነስተኛ ባለሀብቶችን መብት ለማስጠበቅ ያለውን የግልፅነት አሰራር የማጠናከር እርምጃዎች መውሰዷ ይጠቀሳሉ።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 27/2011
ራስወርቅ ሙሉጌታ