
ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ብዙ ጊዜ እንጨቃጨቃለን። የምንጨቃጨቅበትን ምክንያት ልንገራችሁና ማን ትክክል እንደሆነ ፍረዱ።
ምግብ ለመብላት ወይም አንድ ሁለት ለማለት ስንገባ፤ አዲስ ቤት (ገብተንበት የማናውቅ) ከሆነ ዋጋ ይጠይቃል። እኔ ደግሞ በመጠየቁ እናደዳለሁ። ‹‹ፋራ ነህ እኮ! ቢያንስ ‹ሜኑ አምጡልኝ› ይባላል እንጂ እንዴት የእያንዳንዱን ምግብ ዝርዝር እየጠራህ ዋጋ ትጠይቃለህ?›› እያልኩ እናደድበታለሁ፡፡
እሱም በበኩሉ ፋራው እኔ እንደሆንኩ በቁጣ ይወርድብኛል። ዋጋ መጠየቅን የመሰልጠን ምልክት ነው የሚያደርገው፤ በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ስግብግብነትና ማጭበርበር በሚበዛበት፣ ሥርዓት በሚገባ በማይከበርበት ሀገር ዋጋ መጠየቅ የግድ ነው ብሎ ያምናል።
የምግብና መጠጥ ዋጋ ዝርዝሩን አያምነውም፤ በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየዕለቱ ዋጋ ስለሚጨምር ወቅታዊ መረጃ አይኖረውም ብሎ ነው የሚያምን። በዚያ ላይ የምግብ ዝርዝሩ ላይ ያሉት ምግቦች ስለማይኖሩ፤ በቀጥታ ያለውን ጠይቆ አስተናግጇ ስትነግረው እዚያው ላይ እያከታተለ ዋጋውን ይጠይቃል። እኔ ደግሞ ‹‹አስፎገረኝ›› በሚል ስሜት እንደማፈር ብዬ ትኩረቴን ወደሌላ አደርጋለሁ።
በነገራችን ላይ ይህን የሚያደርገው ሲጋብዝ ብቻ አይደለም፤ ሲጋበዝም ጭምር ነው። ‹‹የትኛውም ሀብታም ይጋብዘኝ፤ አይገባውም የምለው ቤት ውስጥ የተጋነነ ዋጋ መክፈል የለበትም›› ነው የሚለው። ዋጋውን ካላመነበት ካልወጣን ይላል። እዚህ ግባ ለማይባል አገልግሎት የማይገባ ዋጋ እየከፈልን እኛ ነን ያበላሸናቸው ብሎ ያምናል።
ለዚህ ትዝብት መነሻ የሆነኝ ይሄው ጓደኛዬ ራት እንብላ ብሎኝ ከአንድ ባር እና ሬስቶራንት ገብተን ነው። በእውነቱ የገባንበት ቤት ያን ያህል ትልቅ የሚባል ቤት አይደለም፤ በየመንገዱ ከሚገኙት አነስተኛ ሆቴሎች አንዱ ነው።
ከአንድ ውጭውም ውስጡም ሰው የበዛበት ሆቴል ገብተን እንደተቀመጥን አስተናጋጇ መጥታ በትህትና ‹‹ምን ልታዘዝ›› አለችን። የሚበላ ጠይቀናት ያሉትን ምግቦች ነገረችን። ይሄው ልማደኛ ጓደኛዬ እንደ ልማዱ ዋጋ ጠየቀ። ለአንድ ምግብ ዝቅተኛ የሚባለው ዋጋ 300 ብር ነው። በፍጹም እዚህ ቤት ውስጥ በዚህ ዋጋ አንበላም ካልወጣን አለ፤ እኔም እንደተለመደው በ‹‹እንፎገራለን›› ስሜት ብለማመጥ ሊሰማኝ አልቻለም፤ ትቶኝ ተነሳ። እኔም ተነሳሁ። በዙሪያችን የነበሩ ሰዎች አተያይ የግርምትና የትዝብት ነበር። ‹‹ምን ዓይነት ፋራዎች ናቸው›› እያሉ ይሆናል።
እዚያ ቤት ውስጥ ዝቅተኛ ዋጋ 300 ብር መሆኑን ካየሁ ወዲህ ግን ያ ጓደኛዬ ትክክል መሆኑን አመንኩ። እውነትም እኔ ነበርኩ ፋራ። እንደዚህ ዓይነት መረን የለቀቀና ይሉኝታ የለሽ ቤት ውስጥ ይሉኝታ አያስፈልግም። የፈለጋቸውን ይበሉ ጥሎ መሄድ መብት ነው። የውሃ መድፊያ የሌለው መጸዳጃ ቤት ይዘው እኮ ነው በዋጋ መቆለል ብቻ የቤታቸውን ደረጃ ከፍ ያደረጉ የሚመስላቸው።
ይህንን ስል ለእነርሱም ኑሮ መወደዱ ጠፍቶኝ አይደለም! ከዘይት ጀምሮ ሁሉም የምግብ ግብዓቶች መጨመራቸው ጠፍቶኝ አይደለም። ዳሩ ግን መረን የለቀቀ ስግብግብነትም ስላለ ነው። እንደ መጸዳጃ ያሉ መገልገያዎችን ለማስተካከል እንኳን ወጪ አያወጡም። የአንዳንዶቹ እንጀራ ሽታው ብቻ የጨጓራ ህመም የሚቀሰቅስ ነው። ጥራት ላይ ትኩረት ከማድረግ ይልቅ፤ ትኩረት የሚያደርጉት ግብዓቶችን በቅናሽ ገዝተው በከፍተኛ ዋጋ መሸጥ ላይ ነው።
አዲስ አበባ ውስጥ አንድ የሚገርመኝ ነገር፤ አንድ አካባቢ ባሉ ቤቶች በተመሳሳይ ደረጃና በተመሳሳይ የምግብ ጥራት ላይ ሆነው የዋጋ ልዩነታቸው ግን በተለምዶ ‹‹ማዘር ቤቶች›› የሚባሉት ውስጥ ምሳ ያበላል።
ብዙ ጊዜ እንደምናስተውለው የዋጋ ልዩነት የሚታየው በቤቶች ደረጃ እንጂ በምግብ ይዘት ልዩነት አይደለም። ርግጥ ነው ትልቅ ደረጃ ያለው ቤት ሲገነባ ብዙ ወጪ አስወጥቷል፤ የኪራይ ከሆነም ኪራዩ ውድ ነው። ይህ ስለሚታወቅ መሰለኝ ትልቅ ደረጃ ያለው ቤት ውስጥ የዋጋ መወደድ ብዙም አይገርምም።
ግን የቤቱ ማሸብረቅ ለተመጋቢው ምን ጥቅም አለው? ወደ ሰውነቴ የሚሄደው የቤቱ ቀለም ነው ወይስ ምግቡ ነው? ይህን ያልኩበት ምክንያት በትልልቅ ቤቶች ውስጥ የምግቡ መጠን አነስተኛ ስለሚሆን ነው። ጥብስ ታዝዞ፤ በትንሽ ሳህን መረቅ ይሞላና በዚያ መረቅ ውስጥ የሚዋኙት ቲማቲምና ሽንኩርት፤ እና አንዳንድ ሥጋዎች ናቸው። እነዚህ ቤቶች ግን በደረጃቸው ልክ የሚመጥን ምግብ ቢያቀርቡ ለቤታቸው ክብር አይሻልም ነበር ወይ?
በነገራችን ላይ ይሄ ነገር የአገልግሎት ሰጪዎች ብቻ ሳይሆን የተጠቃሚውም ችግር ነው። የተወደደ ነገር እንወዳለን። ‹‹ሐበሻ የረከሰ አይገዛም›› የሚባል አባባል አለ። ደረጃው ከርካሽ ዕቃዎች በታች ቢሆን እንኳን የተወደደ ነገር ነው የምንወደው። ‹‹ክብር›› የምንለው ነገር አለ። በምንጠቀመው ዕቃ ወይም በምንመገበው ምግብ መጠንና ጥራት ሳይሆን በቤቱ ደረጃና በዋጋው ውድነት ነው ክብራችንን የምንገልጸው።
ከ10 ዓመታት በፊት ይመስለኛል ኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ‹‹እሁድ መዝናኛ›› ፕሮግራም ላይ ያየሁት ትዝ አለኝ። ‹‹ታዋቂነት እና መዘዙ›› በሚል ርዕስ የቀረበ ነበር። ታዋቂ ሰዎች ታዋቂ በመሆናቸው የሚገደቡትን ገደብ እየተናገሩ ነበር፡፡
አርቲስት ሥዩም ተፈራ መንገድ ዳር የሚሸጥ ፓስቲ በጣም እወዳለሁ አለ። ይህን ፓስቲ ግን በነፃነት መብላት አይችልም ነበር። ሲበላ ያየው አላፊ አግዳሚ ሁሉ በግርምት ይመለከተዋል። በእነዚህ ሰዎች አስተሳሰብ ፓስቲ የሚበላው በምርጫና በፍላጎት ሳይሆን በድህነት ነው። አርቲስት ሥዩም ምን ቸገረኝ ብሎ ነው ፓስቲ የሚበላ እያሉ ነው። እነዚህ ሰዎች ከባድ የሥጋ ምግቦች መዘወተር እንደሌለባቸው ሐኪሞች የሚሉትን እንኳን ሰምተው አያውቁም ማለት ነው። አርቲስት ሥዩም አርቲስት ስለሆነ ብቻ ከሳምንት ሳምንት ከዕለት ዕለት ቁርጥ፣ ፒዛ፣ በርገር…. ሊበላ አይችልም። ለጤናም የሚመከረው ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ ያሉ ምግቦችን መቀያየር ነው።
በተመሳሳይ ሌሎች ታዋቂ ሰዎችም በዚያ ፕሮግራም ላይ ሲናገሩ የነበረው አነስተኛ ቤቶች ውስጥ ሲገኙ ብዙ ሰው በግርምት ይመለከታቸው እንደነበር ነው። በእውነቱ ይሄ ኋላቀር አስተሳሰብ ነው። አንድ ሰው ሀብታም ስለሆነ ብቻ ባለ ኮከብ ሆቴል ብቻ እየመረጠ ሊሄድ አይችልም። በባሕላዊ መንገድ የሚዘጋጁና በአነስተኛ ቤቶች ውስጥ ያሉ ምግቦችም ያስፈልጉታል።
አሁን በኮሪደር ልማት ምክንያት አብዛኞቹ ቢነሱም በተለምዶ ‹‹ማዘር ቤቶች›› የሚባሉ ምግብ ቤቶች አሉ። በአዲስ አበባ በአንዳንድ ጎዳናዎች ዳርቻ የምናያቸው የኮንቴነር ቤቶች ማለት ነው። ለምሳሌ አምስት ኪሎ ከየካቲት 12 ሆስፒታል ጀርባ ያሉት ማለት ነው። እነዚህ ቤቶች ውስጥ የሚሠራ ፍርፍር እና ሽሮ ባለአምስት ኮከብ ሆቴል ውስጥ ከሚሠራ ሽሮ የበለጠ ይጣፍጣሉ። ምክንያቱም አሠራራቸው ለአብዛኛው ሐበሻ ቅርብ ነው።
ዳሩ ግን እነዚህ ቤቶች ውስጥ መታየት የችግር ማሳያ ስለሚመስላቸው ብዙ የማይገቡ ሰዎች ይኖራሉ። ሥነ ልቦናም ጭምር ነው። ለምሳሌ፤ ከአንድ ዓይነት ግብዓት፣ በአንድ የምግብ አዘጋጅ፣ አንድ ቦታ ተዘጋጅቶ፤ አንደኛው ወደ ትልቅ ሆቴል፣ አንደኛው ደግሞ መንገድ ዳር ወዳለች ትንሽ ቤት ተወሰደ እንበል። ለአንድ ቀብራራ ነኝ ባይ ሁለቱንም አቅምሶ ‹‹የትኛው ይሻላል›› ቢሉት ትልቅ ሆቴል ውስጥ ያለውን ሊመርጥ ይችላል።
መነሻዬ ከአንድ አነስተኛ ሆቴል ውስጥ ያየሁት የዋጋ መጋነን ነው። ምንም እንኳን የዋጋ መጋነን በሀገር አቀፍ ደረጃ አጀንዳ ቢሆንም፤ ዳሩ ግን እኛም ቀብራራነቱን እናበዛዋለን። የተወደደ ነገር ነው ትልቅ የሚያደርገን የሚመስለን። መለኪያችን የምንመገበው ምግብ ወይም የምንገለገልበት ዕቃ ጥራት እንጂ የዋጋው ውድነት መሆን የለበትም!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ረቡዕ ግንቦት 13 ቀን 2017 ዓ.ም