“ባሌ ሮቤ ኢንዴምና” ባሌ ገበሬው ገብስ፤ እግዜር ንጹሕ አየር የዘራበት ምድር፤ በደቡብ መካከለኛው ኢትዮጵያ፣ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኝ ዞን ነው። «ማን ይናገር የነበረ ማን ያርዳ የቀበረ» ይባል የለ!? ስለ ባሌ በክልሉ ተወልደው አድገው ተምረው ያለፉባት ብዙ ናቸው። ታዲያ እኛም ከኖሩ ከተማሩ እና ስለ ክልሉ ዙሪያ ገብ የሚያውቁ ሊነግሩን ማብራሪያ ሊሰጡን ከወደዱ ግለሰብ ጋር ቆይታ አድርገናል፡፡
ዶክተር ሄኖክ ስዩም ይባላሉ፤ በአንድ የመንግሥት መስሪያ ቤት ኃላፊ ሆነው ያገለግላሉ። ስለ ባሌ ተፈጥሯዊ መስህቦች አንዳንድ ነገሮች እንዲሉን ጠየቅናቸው፡፡ ዶክተሩ ዞኑ ካለው የተፈጥሮ ሀብት ይልቅ ንግግራቸውን የጀመሩት በኦሮሞ ህዝብ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ስፍራ የሚሰጣቸው እና በኦሮሞ ህዝብ የፖለቲካ ትግል ታሪክ ውስጥ አሻራቸውን ያኖሩትን ጄኔራል ዋቆ ጉቱን በማንሳት ነው፡፡ «ባሌ ቆራጥ እና ጀግና ህዝብ ያለባት ዞን ስትሆን እንደ ጄኔራል ዋቆ ጉቱን የመሰለ ያፈራች የፖለቲካም ትግል የተጀመራባት ዞን ናት»ይላሉ፡፡
ዶክተር ሄኖክ ስለባሌ ተፈጥሯዊ መስህቦች ሲያስቃኙን ስለ ባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ አስቀደመው ይናገራሉ፡፡ ፓርኩ የተመሰረተው በአሁኑ ወቅት በፓርኩ ውስጥ የሚገኘውና ከ40 ዓመት በፊት የተቋቋመው የዲንሾ ሎጅ መነሻ ሆኖት ነው። በወቅቱ አንድ የውጭ ሀገር ባለሀብት በጎች ለማርባት ተፈቅዶለት በጎች እያረባ እንደ ቢሮና ማደሪያ ይገለገልበት እንደነበር ያወሳሉ፡፡
በአጋጣሚ በግ አርቢው የደጋ አጋዘን፣ የሚኒሊክ ድኩላንና ሌሎችም ብርቅዬ እንስሳቶችን በማየቱ ይሄ ነገር ፓርክ ሊሆን ይችላል በሚል ለመንግሥት ሪፖርት በማድረግና መንግሥትም ያለውን ነገር በማጣራት በ1962 ዓ.ም እንደ ፓርክ ሊከለል ችሏል፡፡ በ1960ዎቹ አካባቢ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገራችን ከተቋቋሙት ሦስት ፓርኮች አንዱ ለመሆን በቃ።
ዶክተር ሄኖክ ስዩም “ኢጆሌ ባሌ”ም አይደሉ! የፓርኩን ስፋት፣ ከመሀል ከተማ ያለውን ርቀት… ብቻ ምን አለፋችሁ ፓርኩን ጥንቅቅ አድርገው ያቁታል፡፡ እናም ስለ ፓርኩ ይህን አሉን። «ፓርኩ ከአዲስ አበባ በ400 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሲገኝ ስፋቱ 2ሺ165 ስኩየር ኪሎ ሜትር ነው፡፡
4 ሺ 377 ጫማ የሚረዝመውና ከኢትዮጵያ በከፍታው ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው የቱሉ ዲምቱ ተራራን ጨምሮ የአፍሮ አልፓይን ከፍተኛ ቦታዎች በዚህ ፓርክ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ የባሌ ተራሮች ከፍተኛ አካባቢ በተለያዩ መንገድ የተፈጠሩ ሀይቆች፤ እርጥበት አዘል መሬቶች፣ የእሳተ ጎሞራ ቅሪቶችን አቅፎ የያዘ ነው፡፡» ይላሉ፡፡
ዶክተር ሄኖክ ይናገራሉ፤ ፓርኩን ልዩ የሚያደርገው የተፈጥሮ አቀማመጡ አፍሮ አልፓይታን (ቀዝቃዛና ውርጫማው) አካባቢ አንድ ሺ ኪሎ ሜትር ስኩየር በአፍሪካ የመጀመሪያው ፕላቱ መኖሩ፣ በኢትዮጵያ በከፍታው በሁለተኛ ደረጃ የሚገኘው የቱሉ ዲምቱ ተራራ በመገኘቱ፣ ስደተኛና በአካባቢው የሚቆዩ በርካታ አእዋፍ መኖራቸው፤ በኢትዮጵያ ትልቁና ወደ ሰባት ሺህ ኪሎ ሜትር ስኩዌር የሚሸፍ ሆኖ ‹‹የሐረና ደን›› በውስጡ በመገኘቱ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ
ፓርክ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በዓለም ቅርስነት ጊዜያዊ መዝገብ ውስጥ ተካትቷል።
ከዚህም ሌላ ከ1ሺ600 በላይ የሚሆኑ ልዩ ልዩ ዓይነት ዕፅዋቶች፣ 78 ዓይነት አጥቢ የዱር እንስሳት፤ 280 የአእዋፍ ዝርያዎች በፓርኩ ተጠልለው ይገኛሉ፡፡
ከእነዚህም መካከል 32 ዓይነት ዕፅዋቶች፣ 31 የሚጠጉ ብርቅዬና ድንቅዬ የዱር እንስሳትና ወደ ስድስት የሚጠጉ ዕፅዋት በብሔራዊ ፓርኩ ካልሆነ በስተቀር በሌላው ዓለም ፈጽሞ አይገኙም፡፡ በባሌ ተራሮች ፓርክ ከሚገኙት 78 አጥቢ የዱር እንሰሳት 17 የሚሆኑት በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ ናቸው፡፡ ሦስቱ ደግሞ በዚህ ፓርክ ውስጥ ብቻ የሚገኙ ብርቅዬ እንሰሳት ናቸው፡፡
ታዲያ ዶክተሩ እንደሚሉት ፓርኩ ለሳይንስና ቴኮሎጂ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው በደረታቸው የሚሳቡ ልዩ ልዩ እንስሳትና መንቆረርቶችን አቅፎ ይዟል፡፡ ቡና እና በኢትዮጵያ ውስጥ ለባህል መድኃኒትነት የሚውሉ 40 ከመቶ ዕፅዋቶችም ይገኙበታል፡፡ በእፅዋት እና በእንሰሳት ብዝሃ ህይወት መበልፀግ ደረጃ ፓርኩ ከዓለም 34ኛ ከአፍሪካ ደግሞ 12ኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን አንስተዋል፡፡
የባሌ ብሔራዊ ፓርክ በ“Bird lite International” በዓለም ከሚገኙ አስፈላጊ የአዕዋፍ መኖሪያ ቦታዎች ጎራ ተመድቧል፡፡ በፓርኩ ከ280 በላይ የአዕዋፍ ዝርያዎች ሲኖሩ ሰባቱ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ ናቸው፡፡ እንደ ዓለም አቀፍ የወፎች ድርጅት ሪፖርት ከሆነ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ የአፍሪካ አራተኛው ‹‹በርዲንግ ሳይት›› ተብሎ ተመዝግቧል፡፡
በባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ዋቢ ሸበሌ፣ ዌብ፣ ዱማል፣ ያዶትና ወልመል የተሰኙ ወንዞች ይፈሳሉ፡፡ በፓርኩ ከሚገኙ የዱር እንስሳት መካከል ቀይ ቀበሮ፣ ኒያላ፣ አጋዘንና ሌሎችም ይጠቀሳሉ። በዚህ ላይ ፓርኩ አስደናቂ የተራራ እይታዎች፣ ልዩ ስሜት የሚፈጥሩ ደኖችና የውሃ አካላትን ይዟል፡፡ ወደ ፓርኩ የሚጓዙ ቱሪስቶች የፓርኩን ተራራዎች በእግር በመውጣት የማይረሳ ጊዜ ያሳልፋሉ፡፡
በፓርኩ የሚገኙ የዳንካ፣ ዌብና ሻንያ ወንዞች እና ልዩ ልዩ የውሃ አካላት ዓሣ በማጥመድ ለሚዝናኑ ጎብኝዎች የተለየ የእርካታ ምንጮች መሆናቸውን ዶክተር ሄኖክ ይገልጻሉ። ዓሣ ለማጥመድ ግን ከፓርኩ አስተዳደር ፈቃድ ማግኘት የግድ ይሆናል፡፡
ሌላኛው የባሌ ዞን ድምቀት የተፈጥሮ ስጦታ የሆነውና በአፍሪካ ካሉ ትላልቅ ዋሻዎች አንዱ የሶፍ ኡመር ተፈጥሯዊ ዋሻ መገኛ መሆኑ ነው፡፡ 15 ነጥብ1 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ይህ ዋሻ በኢትዮጵያም ረጅሙ እንደሆነ ይነገርለታል፡፡ ዋሻው በጊዜያዊ የዓለም ቅርስነትም ተመዝግቧል፡፡
የሶፍኡመር ዋሻ በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ መንፈሳዊ ትርጉም የሚሰጠው ስፍራ መሆኑን ዶክተር ሄኖክ ይናገራሉ። ስያሜውን ያገኘው ሶፍ ኡመር በሚባሉ የኃይማኖት ሰው ነው፤ እርሳቸውም ዋሻውን በመጠለያነት በመጠቀም ለብዙ ዓመታት የኖሩ ሰው መሆናቸውን ነግረውናል፡፡ ወደ ዋሻው መግቢያ በድንጋይ የታጠረ ቦታ ክር ቅዱስ ኡመር ይባላል፡፡ ይኸውም ከበሮ በመምታት የሚያመሰግኑበትና የስለት ከብት በማረድ የሚበላበት ቦታ ነው፡።
የሚሳሉ ሰዎች ከታረደው በግ (ፍየል) ላይ ትንሽ ቆዳ ተቆርጠው ዋሻ ውስጥ ለፀሎት ይንጠለጠልላቸዋል። በስተቀኝ በኩል ከዋሻው ፊት ለፊት ወንዙ ውስጥ በጣም ትልቅ የሆነ የተከፈተ መሶብ ቅርፅ ያለው ተፈጥሮ የተራቀቀበት አንድ ወጥ ድንጋይ የሆነ የሶፍ ኡመር መቀመጫ አለ፡፡ የሶፍ ኡመር ዋሻ መግቢያ «ጉለንተና የውመኩ» ሲባል መውጫው ደግሞ «ሁልቃ» ይባላል፡፡ ታዲያ ዶክተሩ በልጅነታቸው በዋሻው ውስጥ መጥፋታቸውን አጫውተውኛል፡፡
ዋሻው የተለያዩና በርካታ ክፍሎች ሲኖሩት ወደ መሀል ሰፊ የሆነ ክፍል «አለይህም ፊጢሱማ አብዲ» ይባላል፤ በሶፍ ኡመር ልጅ ስም የተሰየመ ቦታ ነው፡፡ ክፍሉ (አዳራሹ) መካከል ላይ በክብ ቅርፅ ጎርጎድ ብሎ ወደ ላይ ከፍ ያለ ሲሆን ተፈጥሯዊ መሆኑ ያስገርማል፡፡ የተለያየ ገፅታዎችን በማሳየት አንዱን አድንቀን ሳንነሳ ሌላ የተፈጥሮ ገፅታን የሚያሳየን የማያልቅበት ይህ ዋሻ የሶፍ ኡመር አዳራሽ ተብሎ ወደ ተሰየመው
ዋሻ ክፍል ያሸጋግረናል፤ በዚህ ክፍል ችግር ያለባቸው ሰዎች ከሶፍ ኡመር ጋር ተገናኝተው ችግራቸውን የሚያስረዱበት ቦታ ነው፡፡
አስገራሚው ሌላኛው የዋሻ ክፍል ደግሞ ስጋጃ የተባለው ነው፡፡ ይህ ክፍል መስገጃ ሲሆን በዚህ ክፍል አራት ትልልቅ ጠፍጣፋና ሰፋፊ ድንጋዮች አሉ፤ እነዚህም የሶፍ ኡመር፣ የሼህ ሁሴን፣ የከራዮ መኮ እና የሼህ አበል ቃሲም መስገጃ ስጋጃዎች ናቸው፡፡
ሌላኛው ስጦታ ድሬህ ሼህ ሁሴን (በመጀመሪያ ስማቸው አንጅና) ኡለማ ሲሆኑ አርሲና ባሌ አካባቢ የእስልምና አስተምህሮ ያስፋፉ ነበር። ቦታው የቁራአን ትምህርት የሚሰጥበት ሲሆን በየ6 ወሩ ተማሪዎቹን ያስመርቁም እንደነበር ነግረውናል። ለተመራቂዎች ወላጆቻቸው ስንቅና ስጦታ ይዘው ይመጣሉ፡፡
በዚያው ዝየራ (ጉብኝት) ተለመደ፡፡ ሼህ ሁሴን ከሞቱ በኋላም የሳቸው ደቀ መዝሙር ቤተሰቦቻቸውና ተከታዮቻቸው ያንኑ ስርዓት ይዘው ቀጠሉ፡፡ በየ6 ወሩ የእምነቱ ተከታዮች ከ500 ሺ ህዝብ በላይ በቦታው ይገኛል፡፡ ልዩ የሚያደርገው የማንኛውም እምነት ተከታይ የሆነ በዚህ በዓል ላይ በመገኘት የዝግጅቱ ታዳሚ መሆኑ ነው፡፡
በቦታው የሚሄዱ ሰዎች የሚያገኛቸው ነገሮች አሉ። ከዚህም መካከል ምርቃት፣ እንደመድኃኒትነት የሚጠቀሙት ጀዋራ (የአካባቢውን አፈር)፣ ዘምዘም (በአካባቢው የሚገኝ ውሃ) ይሄም «ሀሮ ልኩ» የሚባል ቦታ ብቻ ነው የሚገኘው። «ሀሮ» ማለት ኩሬ ሲሆን «ልኩ» ደግሞ ዶሮ ማለት ነው፤ ዶሮ የሚጠጣው ውሃ ስለሆነ ሀሮ ልኩ ተባለ ይባላል፡፡ ውሃው ቁራአን የሚማሩበት፣ ቦርድ (ሎሂ) የተፃፈበትን ቀለም እያጠቡ መልሰው የሚፅፉበት ውሃ ስለሆነ በቁራአን ተጠምቋል ተብሎ በመታመኑ ለፈውስነት ይጠቀሙበታል፡፡
ሌላው እንደ ዶክተር ሄኖክ ገለጻ የመካነ ህይወት ተክለ ሃይማኖት ገዳም ነው። ገዳሙ አሁን አሁን እንጂ ከዚህ ቀደም ብዙም አይታወቅም ነበር፡፡ ገዳሙ በታኅሣሥ 30 ቀን 1979 ዓ.ም. በወቅቱ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በነበሩት አቡነ ሰላማ ተባርኮ ተመሥርቷል። ለገዳሙ መመስረት ዋናው ምክንያት የጠበል መገኘት ሲሆን የገዳሙ መልክአ ምድራዊ ገፅታው ተራራማ፣ ሸለቋማ፣ በጣም በሚያምር ደን የተሸፈነ፣ ምንጭ ያለውና ለጎብኝዎች እጅግ ማራኪ በሆነ ቦታ ነው።
በውስጡ የፅድ፣ የወይራ እና የባህር ዛፍ ዝርያዎች ሲገኙ ደኑን ተከትሎ የተለያዩ አእዋፍ፣ አንበሳ፣ነብር፣ጦጣና ጅብ ይገኙበታል፡፡ የገዳሙ የቱሪስት መዳረሻም ነው። በየዕለቱ ምዕመናንና የሀገር ውስጥ ጎብኝዎች ይስተናገዳሉ። በአብዛኛው ግን ለጠበል የሚመጣ ሰው የሚበዛ ሲሆን ከ15 እስከ 30 ቀናት ይቆያሉ፤ ጠበልተኞቹ በሚቆዩባቸው ጊዜያት አትክልት በመንከባከብ፣ ችግኝ በመትከል፣ በግንባታ ሥራ እንደአቅማቸውና እንደየችሎታቸው ተሳትፎ ያደርጋሉ።
ዶክተር ሄኖክ አሉ፤ «በጥቂቱ ስለባሌ ልላችሁ የምችለው ይህንን ነው፤ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ግን ቢያንስ አንድ ጊዜ ሊጎበኘው የሚገባ እኔ ልገልጸው ከምችለው በላይ በተፈጥሮ መስህቦች የበለጸገች ከተማ ናት።» እኛም የዶክተር ሄኖክን ምክረ ሃሳብ ሰምተናል፤ አገራችንን ማወቅ ይገባናልና። ሰላም!
አዲስ ዘመን ግንቦት 18/2011
አብርሃም ተወልደ