ክረምት’፤ ስርወ ቃሉ ከርም፤ ከረመ የሚለው የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ወርኃ ዝናም፣ ወርኃ ነጎድጓድ፣ ዘመነ ባሕር፣ ዘመነ አፍላግ፣ ዘመነ ጠል፣ ዘመነ ደመና፣ ዘመነ መብረቅ ማለት ነው። በትግርኛ ክራማት ይባላል።ሰኔ በልግ የሚወጣበት ክረምቱ ደግሞ የሚብትበት ወር ነው።መደበኛው የክረምት ወቅት ከሰኔ 26 ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም 25 ቀን ድረስ ያለው ጊዜ ነው።
ለዚህ ነው ትምህርት ቤቶች ከሰኔ 30 ጀምሮ እስከ መስከረም መባቻ ዝግ የሚሆኑት።ተማሪዎች የክረምቱ ዝናብ እየመታቸው ትምህርት ቤት ሔደው ኅሊናቸውን ሰብስበው መማር አይችሉም።መምህራንም በዝናቡ ለማስተማር የሚተጉ አይሆኑም።ገጠራማ በሆኑ አካባቢዎች ደግሞ መንገዶች ይጨቀያሉ ብቻ ሳይሆን አላራምድ ይላሉ፤ ጫማ ያስወልቃሉ፡፡
ወንዞችም ይሞላሉ፤ በወንዙ ሙሌት ለመሻገር መቸገር ሊኖር ይችላል።አንዳንዴም ወንዝ እየተሻገሩ ከሌላ ቦታ በዘነበ ዝናብ ፈረሰኛ ወንዝ መጥቶ ሰውን ይወስዳል፤ሕይወት ይጠፋል።ሲከፋም ቀብሮ እርምን ለማውጣት አስከሬን የማይገኝበት አጋጣሚም ይኖራል።ስለዚህ በክረምቱ ትምህርቱ መዘጋቱ ተገቢ ነው።
የዘንድሮው ክረምት ለየት ያለ ይመስላል።ቀኑ ሳይደርስ ገባሁ ገባሁ እያለ፤ አልፎ አልፎ በአዲስ አበባ በግንቦት ወር መጀመሪያዎቹ ሳምንታት ሲዘንብ ዓይተናል።አዘናነቡ ደግሞ እንደ ነሐሴ ወር ዝናብ ከበድ ያለ ነበር።ደግነቱ ከግንቦት አጋማሽ ወዲህ ባሉት ሳምንታት ዝናቡ ረገብ ብሎ ክርር ያለውን የግንቦት ፀሐይ አይተንበታል።
አባቶችና እናቶች በዝናቡ ምክንያት አስቀድሞ ክረምቱ የሚገባ ከሆነ ለገበሬው ዘር ለመዝራት ሰብሉን ለማምረት ያዳግተዋል የሚል ስጋት ተሰምቷቸው ነበር።።ምናልባት ግን በአረንጓዴ አሻራ ባለፉት ክረምታት የተተከሉት ችግኞች በቅለው ርጥበትና ዝናብ ለመሳብ አቅም ስላገኙም ሊሆን እንደሚችል መገመቱ አይከፋም።
ብዙዎቹ በእድሜ ጠና ጠና ያሉት አበውና እመው (እናቶችና አባቶች) ከገጠር ወደ ከተማ የመጡ ስለሆኑ ክረምቱንም የገበሬውንም ሕይወት ያውቁታል።ገበሬው የዘራው ዘር ፍሬ የሚያፈራው ዝናቡ በልኩ ሲዘንብ ነው።በክረምቱ የገበሬው ሕይወት ከተሰናከለ፤ የክረምቱ ዝናብ በአግባቡ ካልዘነበ አልያም ከግንቦት እስከ ነሐሴ እየዘነበ ከዘለቀ ዘር ለመዝራት አያስችልም።የገበሬ ሕይወት መሰናከልና ጣጣው ለከተሜውም ስለሚደርሰው መስጋታቸው ተገቢ ነው፡፡
እንደ አዲስ አበባ ባሉ ከተሞች ክረምቱን በከተማ ግብርና ለመጠቀም ከወዲሁ ጥረት ቢደረግ መልካም ነው።በግሌ መቼም የጓሮ አትክልት አምርቱ ለማለት መብቱም የለኝም።በመዲናዋ ጓሮ ያለው ቤት አለ እንዴ? መልሱን ለእናንተ ልተወው።ቢኖርም ብር ያላቸው አፈር መቆፈርን ስለሚንቁ አይተክሉም አያለሙም፤ግን እኮ ሰው ቀጥሮም ማልማት ይቻላል።እግረ መንገዳቸውን እኮ የከተማ ግብርና ለሚያለማው ሠርቶ አዳሪ የተወሰነ ሰጥተው ተጠቃሚ ማድረግ ይችላሉ።
የአዲስ አበባ ትምህርት ቤቶችም፣ በተለይ የመንግሥት ትምህርት ቤቶች፣ ባላቸው ሰፋፊ ግቢ ድንች፣ ስኳር ድንች፣ ሽንኩርት፣ ጎመን ቀይሥር ወዘተ ተክለው በክረምቱ ያለሥራ ተወዝቶ ሙጃና አረም የሚበቅልበትን መሬት ከወዲሁ ሊያለሙ የሚችሉበትን መንገድ ቢያመቻቹ ጥሩ ይመስለኛል። ራሳቸውን ይደጉማሉ፤ከተረፋቸውም ለሰዎች በመጠነኛ ዋጋ ሸጠው ይጠቀማሉ፤ትምህርት ቢሮ እና የግብርና አካላት ትብብር በማድረግ ድርሻቸውን ይወጡ።ትምህርት ቤቶች፣ ጤና ጣቢያዎችና ሌሎች ሰፋፊ ግቢ ያላቸው መሥሪያ ቤቶች መሬቱን አልምተው ይጠቀሙበት።
ክረምት የዝናብ ወቅት ብቻ ሳይሆን ለገበሬ ከባዱና ዋነኛው የሥራ ወቅት ነው።አንዳንድ መጻሕፍትና ሰነዶች ዘመነ ክረምት የሚባለው ከሰኔ 26 እስከ መስከረም 25 ቀን ያለው ወቅት እንደሆነ፣ በውስጡም 7 ክፍሎች ያሉት ሲሆን ከነዚህ መካከል ሁለቱ በዓተ ክረምት (የክረምት መባቻ)፡- (ከሰኔ 26- ሐምሌ 19 ) እና ምልአተ ባሕር (ከሐምሌ 19 – ነሐሴ 10) ይባላሉ።ስያሜያቸው የተለያየ ቢሆንም ዞሮ ዞሮ በክረምት የሚጠቃለሉ ናቸው፡፡
ለምሳሌ ከላይ ከጠቀስናቸው ጊዜያት በዓተ ክረምት የሚባለው ክረምቱ የሚገባበት የክረምቱ መለማመጃ፣ በመጠኑ በመጠኑ እየዘነበ ‹‹እየመጣሁ ነው፣ እየገባሁ ነው›› ብሎ ለሰውም፣ ለእንስሳትም ለእፅዋትም ለነፍሳትም የሚያስተዋውቅበት ጊዜ ነው።ምልአተ ባሕር የሚባለው ክፍለ ጊዜ ደግሞ ከሐምሌ 19 እስከ ነሐሴ 10 ቀን ድረስ ያሉት 21 ዕለታት የሚጠሩበት ነው፡፡
በዚህ ወቅት የክረምት ኃይልና ብርታት የክረምትን ጥግ አድርገው የሚከሰቱ የተፈጥሮ ኃይላት ዑደት ይጸናበታል።መብረቅ፣ ነጎድጓድ፣ ይከሰታል፤ ባሕራትና አፍላጋት (ወንዞች) ይሞላሉ።ጥልቅ የውሃ ቦታዎች መጠናቸው ያድጋል፤ ምንጮች ይመነጫሉ፡፡
በአጋጣሚ ደግሞ የዘንድሮው ክረምት በገበሬዎች ዘንድ ብቻ የሚናፈቅ የሚጠበቅ አይደለም፤ ሕዝብና መንግሥት የዘንድሮውን ክረምት በጉጉት ይጠብቁታል፤የታላቁ የሕዳሴ ግድብ አራተኛው ዙር ውሃ ሙሌት በያዝነው ክረምት ወር የሚካሄድበት ነው።ስለሆነም የዘንድሮን ክረምት ገበሬው ብቻ ሳይሆን ከተሞችም ዲያስራፖዎችም ጭምር መጣልን ብለው የሚጠብቁት ነው።ምናልባት የግድቡን ውሃ ሙሌት በመሳቀቅ እነግብጽ ዝናቡን ‹‹መጣብን›› ብለው በስጋት ሊታወኩ ይችላሉ።የዘንድሮው ክረምት እናት ኢትዮጵያ ከልጆችዋ ጋር በደስታ የምትስቅበት፣ የምትደሰትበት ጊዜ ነው።
ገበሬው (እረኛውም ጭምር) የክረምቱ ዝናብ ከነቤተሰቦቹ እየወረደበትና እየተፈራረቀበት አፈር ለብሶ አፈር መስሎ አርሶ ዘርቶ ጸደይና በጋን ጌታ መስሎ ይኖረዋል።እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ ሀገራት ከእጅ ወደ አፍ የሚሆን የግብርና ምርት በበሬዎች ጠምዶ ሞፈርና ቀንበር አስተሳስሮ ለከተሜዎችም ይተርፋል።በኋላ ቀር አስተራረስ እያረሰ እየተንገዳገደም የሀገሪቱን ምጣኔ ሀብት እየደገፈ ያለው ገበሬው ነው።
ገበሬውን ለማዘመን የሚደረገው ጥረት አሁን ሊፋፋም ይገባል።በያዝነው ዓመት በመጠኑ የመስኖ እርሻዎችን እና ውጤቶቻቸውን ዓይተናል።ለቀጣዩ ዓመት ደግሞ የበለጠ በመስኖ አምርተው ለራሳቸውም፤ ለዜጋውም ለሀገሪቱም እንዲተርፉ የሚደረገው ጥረት ይቀጥል።ገበሬው በክረምቱ በአግባቡ ከዘነበ እህሉን ዘርቶ፣ ሲደርስ አጭዶ ወቅቶ እህሉን ከምሮት ክረምትን የሚያመሰግንበት ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹በለቅሶ የሚዘሩ በደስታ ያጭዳሉ›› እንደሚለው ሁሉ፤ለገበሬው ክረምቱ የለቅሶ የመከራ ወቅት ነው፤ የክረምቱን ለቅሶ ሳይሳቀቅ ቀኑን ሙሉ ዝናቡ እየወረደበት እህሉን ዘርቶ የእፎይታ፣ የእርካታ ኑሮ የሚኖረው ዝናቡን ታግሶ መሬቱን አርሶ እህሉን ዘርቶ ሲጠቀምበት ነው።በሦስት ወራት ክረምት በዘራው ዘር እህሉን የሚከምርበት፣ ዘጠኙን ወራት በእርጋታ በእርካታ የሚከርምበት ወቅት ነው።የሚከርምበት ስል ክረምቱን አሳልፎ እስከ ቀጣዩ ክረምት በደስታ የሚዘልቅበት ማለቴ ነው፡፡
እንደ ስንዴ የመሳሰሉት እህሎች በክረምት እርሻው ከታረሰ በኋላ ዘር ሲዘሩ፤ የተዘራው ዘር የገበሬው ቤተሰቦች በቦይ ቦይ መሀከል ቆመው አንድ ክንድ በሚያክል ስፋት እግራቸውን ከፈት አርገው ራሳቸውን አጎንብሰው ከወገባቸው ዝቅ ብለው ቦይ ይዝቃሉ፤ አንድ ገበሬ እንዳጫወቱኝ ቦይ መዛቅ የተዘራውን ስንዴ በአፈር የመሸፈን ዘዴ ነው።ስንዴው ሲዘራ የገበሬው ቤተሰቦች ቦይ የሚዝቁት ዘሩን እንዲበቅል እና በወፎች እንዳይለቀም ለመከላከል በአፈር የመሸፈን ሂደት ነው፡፡
ጤፍ በብዛት የሚዘራው በነሐሴ ወራት መሬቱ በዝናብ በውሃ ሲረሰርስና ውሃ ሲቋጥር ነው ፤እርሻው ታርሶ ጤፍ ከተዘራ በኋላ የታረሰውንና የተዘራውን ቦታ የገበሬው ቤተሰቦች ህፃን ልጅን ጨምሮ እና የጋማ ከብቶችና የቀንድ ከብቶች በዕለቱ የታረሰውንና የተዘራበትን መሬት እየተመላለሱ ይረግጡታል፤ይህም ጤፉን ወደ መሬት የመቅበር ሂደት ሲሆን ሰዎችና ከብቶች ጤፍ የተዘራበትን ቦታ በዕለቱ እየተመላለሱ ካልረገጡት በነሐሴ ወር የሚዘንበው ዝናብ የተዘራውን የጤፍ ዘር ጎርፍ ሆኖ ጥርግ አድርጎት እንዳይሄድ ይከላከላል። ይህም የተዘራው ዘር በተዘራበት እንዲበቅል ያስችላል።
በክረምት ወንዞች ይሞላሉ፣ በገጠር መንገዶች ጭቃ በጭቃ ይሆናሉ ፤ በተለይ ደግሞ ዘመድ ለዘመድ ለመጠያየቅ ገበያ ሄዶ ለመገበያየት ራቅ ወዳለ ቦታ ሄዶ እህል ለማስፈጨት ይቸግራል። አንዱ ችግር አንዳንዴ በክረምቱ ቀኑን ሙሉ እኝኝ የሚለው ዝናብ ሲሆን በተጨማሪም በተለይ ወንዝ ተሻግረው የሚሄዱ ሰዎች ወፍጮ ለማስፈጨት፣ ለህክምናም ሆነ ለደስታም ለሀዘን ከወንዝ ማዶ ተሻግረው ለመሄድ የሚቸገሩበት ሁኔታ አለ።
ክረምት የመብረቅ የነጎድጓድን ድምፅ የዝናቡ ሁኔታ ወንዞችንና ሌሎች የውሃ አካላት እንዲሞሉ ያደርጋቸዋል።በአንዳንድ የገጠር አካባቢዎች በክረምት መሻገሪያ ድልድይ የሌላቸው ወንዞች ወንዙ ሲሞላ አቋርጠው ለማለፍ ይቸገራሉ።አንዳንዴም ወንዙን እያቋረጡ ፈረሰኛ ወንዝ መጥቶ (ሌላ አካባቢ የዘነበ ዝናብ ደንገት መጥቶ ሲሻገሩ ሊወስዳቸው ስለሚችል) ወንዝ መሻገር ፈርተውም ቤት ለምነው የሚያድሩ ሰዎችም ይኖራሉ፡፡
ከላይ እንደጠቀስኩት የዘንድሮው ዝናብ ግን ለእኛ እስራኤላውያን መና ከደመና ሲጠብቁ እንደነበሩት ዓይነት ነው።ሰው የዘንድሮውን ዝናብ የሕዳሴ ግድቡን ሞልቶል አንዳች መና ያመጣልና፤ታሪክ ይቀየራል ብሎ ይጠብቀዋል።ኢትዮጵያ ከበይ ተመልካችነት ወደ ተመጋቢነት ትሸጋገራለች፤ መብራት እናበራለን፣ መረጃ እንከታተላለን እንዝናናለን፣ ጠላታችን ድህነትን በህዳሴ ገንጥለን እንጥላለን ብለን የምንጠብቀው ዝናብ ነው የዘንድሮው ክረምት።
የዘንድሮው ክረምት ለሕዳሴ ግድብ አራተኛ ዙር ሙሌት ስለሚሆን የግድቡ አቅሙ እየጨመረ ይሄዳል።ለኬንያ፣ ለጅቡቲ ለደቡብ ሱዳን ከወዲሁ ኤሌክትሪክ እየተሸጠ በዶላር ገቢ እየተገኘ ነው።እናም ከወዲሁ የግድቡ አቅም ሲጠናከር የኤሌክትሪክ ኃይሉም ዓቅም የበለጠ እየጨመረ ይሄዳል።የሀገሪቱ ገቢም ይጨምራል።ኢትዮጵያውያንን እርስ በርስ ለማተራመስ የሚተጉት ደግሞ ተስፋ ይቆርጣሉ፤እርማቸውን ያወጣሉ።ዝናቡ ገበሬው ብቻ ሳይሆን ሕዝብና መንግሥትም በጉጉት የሚጠብቀው ነው።
በከተሞች ለሚኖሩ ጎዳና ተዳዳሪዎች ክረምት የመከራ ወቅት ነው ማለት ይቻላል፤ዝናቡ ንፋሱ መብረቁ ነጎድጓዱ በረዶው ብርዱ ጎርፉ ሁሉ ይፈራረቅባቸዋል። በተለይ በበጋ በየጥጋ ጥጉ አስፋልት ዳርና አጥር ሥር አንዳንድ ጊዜም በባቡር ሀዲድ ድልድይ ሥር እንዲሁም በቱቦ ውስጥ መኝታ አድርገው የሚኖሩ ይቸገራሉ።መሬቱ ይቀዘቅዛል፤ይረጥባል። የዝናቡ ወጨፎም በረንዳ ሥር ያረሰርሳቸዋል፤በበጋ ፍሳሽ በሌለው ቱቦ ተሸለኩልከው ገብተው የሚያድሩ በክረምት ጎርፎች ሞልተው የሚፈሱበት ትቦ ገብተው ለማደር አይሞክሩትም፤ዝናቡ ‹መጣብን› ቢሉ አይገርምም።
በአዲስ አበባ ከተማ በክረምቱ መግቢያ ዋዜማ የሚታዩ የመንገድ ቁፋሮዎች አሉ።መሥሪያ ቤቶች ሁሉ ዓመቱን ተኝተው ክረምቱ ሲደርስ አስፋልትና የእግረኛ መንገድ እየቆፈሩ አካባቢን በክረምት ያጨቀያሉ።በብዛት አስፋልት ዳር የእግረኛ መንገዶች ሲቆፈሩ ይታያሉ።ለአሽከርካሪም ለእግረኛም ጠንቅ የሚሆን ሥራ ነው።
መንገዶቹ መቆፈራቸውን መቃወም አይቻልም።ነገር ግን ቀጣዩ ጊዜ ክረምት በመሆኑ አፈሩ እላያቸው ላይ ተከምሮ አስፋልቱንም እግረኛ መንገዱንም ሲያጨቀዩ ከወዲሁ በሚዘንበው ዝናብ እናያለን፤ ለአብነት ያህል ይህ ችግር ከአውቶቡስ ተራ መሳለሚያ ባለው የእግረኛ መንገድ እና አራት ኪሎ አካባቢ ባሉ መንገዶች ይታያሉ።ለወደፊቱ እንደጠቀስነው ዓይነት ዝርክር ሥራ እንዳይደገም የሚመለከታቸው አካላት ይመልከቱት ስል አመለክታለሁ።
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሰኞ ሰኔ 19 ቀን 2015 ዓ.ም