ቴክኖሎጂው፣ የሕይወት ሩጫው፣ የእርስ በእርስ ፉክክሩ… የበዛበት ዘመናዊው ዓለም ከቅንነት ጋር የሚስማማ ሆኖ አይታይም። ‹‹ቅንነት ሞተ፣ መተዛዘን ጠፋ …›› የሚሉ ድምጾች ደጋግመው ይደመጣሉ። በተለይም የኢትዮጵያውያን መገለጫ ተደርገው ከሚቆጠሩት ባህርያት መካከል አንዱ የሆነው ቅንነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሸረሸረና እየደከመ መሄዱ ያሳሰባቸው ኢትዮጵያውያን በዚሁ ጉዳይ ላይ አተኩሮ የሚሰራ የበጎ አድራጎት ተቋም ለማቋቋም አቅደው ተነሱ። የእነዚህ ኢትዮጵያውያን እቅድ የወለደው ‹‹ቅን ኢትዮጵያ የበጎ አድራጎት ማኅበር›› የተሰኘው ምግባረ ሰናይ ተቋም በ2002 ዓ.ም ተመሰረተ። የሃሳቡ አፍላቂና ባለቤት አንጋፋው የሃይማኖት መምህር ዶክተር ቶሎሳ ጉዲና ናቸው።
የኢትዮጵያ ሕዝቦች የመከባበር፣ የቅን አስተሳሰብና የመደናነቅ ባህል የኑሮ ዘይቤያቸው ሆኖ እንዲሰርፅ የማየት ራዕይ ያለው ማኅበሩ፤ መከባበር፣ ቅን አስተሳሰብና መደናነቅ በኢትዮጵያ ሕዝቦች መካከል በሁሉም ማህበረሰብ ተቀባይነት አግኝተውና ተስፋፍተው ለሀገር ዕድገትና ልማት አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው የማድረግ ተልዕኮም አለው።
የመደናነቅና የመመሰጋገን ባህልን ማዳበር የሚለው የማኅበሩ ዓላማ ‹‹የሀገራችን ኋላ ቀርነትና ድህነት ከምድራችን መካንነት የመነጨ አይደለም፣ የአስተሳሰብ ቅኝታችንም የተጓደለው ትምህርት ከማጣት የተነሳ አይደለም፣ በጉልበትም በስልጣንም አይደለም የደከምነው፤ የእነዚህ ችግሮች ምንጮች አለመተዋወቃችን፣ አለመተማመናችን፣ ተባብረን ለመስራት አለመጣራችን ነው። እርስ በእርሱ መልካም አመለካከት የሌለው ሕዝብ በእርምጃው ውጤታማ ሊሆን እንደማይችል ግልፅ ነው።
ትልቁ የአድናቆት ዓላማ በሰው ድካም ሳይሆን በሰው ብርታት ላይ፣ በሰው ውድቀት ሳይሆን፣ በሰው ስኬት ላይ ማተኮር ነው። ሰውን በአክብሮት እና በትህትና መነጽር፣ በምስጋና እና በአድናቆት መነጽር ማየት መቻል ለሁሉም ወገን ጠቃሚ ሲሆን ለሀገር እድገትም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው። ይህ ሲባል ሂስ አይኖርም ማለት አይደለም። ገንቢ ሀሳብ የበለጠ እንድንበረታታ ያደርገናል እንጂ አይጎዳንም። የሚሰጠው ገንቢ ሀሳብ በቅን አመለካከት ላይ የተመሰረተ መሆን ይኖርበታል። ተቀባዩም ቂም ሳይዝ በቅን ልቦና መቀበል ይኖርበታል። ገንቢ ሐሳብና ጤናማ አስተያየት መስጠትና መቀበል ለግልም ሆነ ለሀገር ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው። አፍራሽና ተስፋ አስቆራጭ ዕይታና አንደበት ግን የጥፋት መሳሪያ ስለሆነ ልናስተናግደው አይገባም›› ከሚለው የዶክተር ቶሎሳ ጉዲና ሃሳብ የመነጨ ነው።
እንደማኅበሩ እምነት፤ ቅንነት ሦስት አምዶች (Pillars) አሉት፡- በጎ አስተሳሰብ፣ መከባበር እና መደናነቅ። ማኅበሩ እነዚህን አምዶች በማጠንከርና በማስፋፋት ቅንነት የኅብረተሰቡ መገለጫና ባህል እንዲሆንና ዜጎች በሀገር ግንባታ ላይ አዎንታዊ ሚና እንዲኖራቸው ለማድረግ ይሰራል። ከዚህ በተጨማሪም ራስንና ሌሎችን የመቀበል እሳቤ ለጠንካራና ጤነኛ ኅብረተሰብ ግንባታ ቀዳሚ እርምጃ መሆን አለበት።
የ‹‹ቅን ኢትዮጵያ›› የበጎ አድራጎት ማኅበር ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተፈራ ሥዩም እንደሚናገሩት፣ ማኅበሩ በሀገሪቱ ያሉትን የአስተሳሰብ ክፍተቶች፣ በተለይም የቅንነት ጉድለቶችን፣ ለመሙላት ታስቦ የተመሰረተ ነው። የማኅበሩ ምስረታ በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተዳከመ የመጣውን የቅንነት ባህርይ ለማነቃቃት የተወሰዱ የመፍትሄ እርምጃዎች አካል ነው።
አቶ ተፈራ ስለማኅበሩ አመሰራረትና የመጀ መሪያ የሥራ እንቅስቃሴዎች ሲያስታውሱ ‹‹ቅንነት እንዲፈጠር አጋዥ የሚሆነው የመደናነቅ ባህል በኢትዮጵያ ያልተለመደ በመሆኑ ይህን ባህል እንዴት ማስፋፋት እንደሚቻል ለማመልከት አንድ ጥናት ማድረግ አስፈላጊ ነበር። ጥናቱን ሰባት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን እንዲያካሂዱት ከተደረገ በኋላ የተለያዩ የሃይማኖት ተቋማት እና የአፍሪካ ኅብረትን ጨምሮ የልዩ ልዩ ድርጅቶች ተወካዮች፣ የመንግሥት ባለስልጣናት እንዲሁም ታዋቂ ግለሰቦች በተገኙበት ጥናቱ ቀረበ። በጥናቱ ግኝቶች ላይ በመመርኮዝ የመደናነቅ ባህሉን ወደ ቅንነት ማሸጋገር አስፈላጊ እንደሆነ ታምኖበት ቅንነትን የመስበክና የማስተማር ጥረቶች ቀጠለ›› ሲሉ ያብራራሉ።
በኢትዮጵያ የመደናነቅ፣ የመተባበርና የበጎ አሳቢነት ባህል እንዲዳብር በማሰብ የተመሰረተው ‹‹ቅን ኢትዮጵያ›› የበጎ አድራጎት ማኅበር፣ ይህን ዓላማውን ከግብ ለማድረስ የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን ዋና ስራ አስኪያጁ አቶ ሥዩም ይገልፃሉ። ማህበሩ ኅብረተሰቡ ስለቅንነት፣ መደናነቅና መመሰጋገን የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖረው የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን አዘጋጅቷል።
በእነዚህ መድረኮች ላይ ታዋቂ ሰዎችና ከጉዳዩ ጋር ተዛማጅ የሆኑ አካላትን በማሳተፍ ስለቅንነት፣ አድናቆትና ምስጋና መልዕክቶች እንዲተላለፉ ያደርጋል። በየዓመቱ የግንቦት ወር የመጀመሪያው ማክሰኞ ሀገር አቀፍ የወላጆች፣ የመምህራንና የተማሪዎች የመከባበር ቀን ሆኖ እንዲከበር ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሞ ይኸው ኹነት በየዓመቱ እየተከናወነ ይገኛል። በትምህርት ቤቶች ውስጥ የምስጋናና አድናቆት መድረኮችን በማዘጋጀት ተማሪዎች፣ ወላጆችና መምህራን እርስበርስ እንዲሞጋገሱና እንዲመሰጋገኑ ያደርጋል።
ኢትዮጵያ ሁሉም ሀብት ቢኖራትም በቅንነት ጉድለት ምክንያት ለብዙ ችግሮች ተዳርጋለች ብሎ የሚያምነው ማኅበሩ፣ ልጆች በቅንነት በተቃኘ አስተሳሰብ እንዲያድጉ ለወላጆችና ለልጆች የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን ያዘጋጃል። ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በጅማ፣ በሀዋሳ፣ በድሬዳዋ፣ በአዳማና በሌሎች ከተሞች መሰል መድረኮችን የማዘጋጀት እቅድ አለው።
ማኅበሩ ከትራንስፖርት ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሞ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ፣ አሽከርካሪዎች በቅንነት እንዲያሽከርክሩ፣ እውቀታቸውንና ችሎታ ቸውን በቅንነት እንዲጠቀሙ ያስተምራል። ቅንነትን የተላበሰ ዜጋ በማፍራት ሰላሟ የተጠበቀች ሀገር ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በትብብር ይሰራል።
አቶ ተፈራ እንደሚሉት፣ ‹‹ቅን ኢትዮጵያ›› እስካሁን ድረስ ባከናወናቸው ተግባራት የቅንነት ባህል መሻሻል እያሳየ ይገኛል። ‹‹የዜግነት ግዴታችንን ለመወጣት ባደረግነው ጥረት ብዙ ግለሰቦችና ቡድኖች ሃሳባችንን መደገፋቸው፤ በየደረጃው ያሉ የመንግሥት አካላት ሃሳቡን እንዲረዱት ማድረጋችን እንዲሁም የቅንነት፣ የመመሰጋገንና የመደናነቅ ባህል የብዙ ሰዎች የሕይወት መገለጫ ባህርይ ሆኖ መመልከታችን በዋጋ እንደማይተመን ትልቅ ሽልማትና እውቅና እንቆጥረዋለን። የሰዎች ባህርይ በመልካምነት ተለውጦ ቅንነትን መገለጫው ያደረገ ማኅበረሰብ እውን ማድረግ ትልቅ ስኬት ነው›› በማለት የማኅበሩ ተግባራት ለውጥ ማስመዝገባቸውን ይገልፃሉ።
ማኅበሩ እንዲመሰረት ምክንያት የሆኑት አንጋፋው የሃይማኖት መምህር ዶክተር ቶሎሳ ጉዲና ሦስተኛው ሀገራዊ የማመስገንና የመደናነቅ ቀን ሲከበር ባስተላለፉት መልዕክት፤ ‹‹መመሰጋገን፣ መከባበርና መተባበር አንድነታችንን ይበልጥ ያጠናክራል፤ ቅንነትን ያዳብራል›› ሲሉ ገልጸዋል።
ሕፃናት የነገ አገር ተረካቢ ዜጎች በመሆናቸው ወላጆች፣ መምህራንና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እነዚህ ሕጻናት ከመለያየትና ዘረኝነት ርቀው የአመስጋኝነት፣ የመደናነቅና የቅንነት መልካም እሴቶችን ተላብሰው እንዲያድጉ መተባበር እንዳለባቸው ተናግረዋል። ልጆችን በፍቅርና በስርዓት በማሳደግ ቅን ዜጎች እንዲሆኑ ማድረግ እንደሚገባ ጠቁመው፣ ልጆች የአሉታዊ አመለካከት መሳሪያ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባም መክረዋል።
‹‹የአንድን ሀገር ዕይታ ለመቀየር የሕዝቡን አስተሳሰብ መቀየር አስፈላጊ ነው። የሕዝብን አስተሳሰብ ለመቀየር ደግሞ ቅን አመለካከት፣ ቅን አገላለጽ፣ በጎ ሕሊናና፣ ጤናማ መንፈስ ማስፈለጉ ጥያቄ የለውም። ቅንነት የአንድ ግለሰብ እና ኅብረተሰብ ጤናማ መግለጫ ነው። የመደናነቅ ባህል በሰፊው ባልታወቀበት ምድር ዘለቄታዊ ትምህርት መስጠት የሚያመጣው የአስተሳሰብ ለውጥ የሚያስከትለው ይቅርታ፣ ዕርቅ፣ መከባበርና መተማመን በቀላሉ የሚገመት አይደለም።
ሁሉንም ከፍና ዝቅ ሳናደርግ የሰው ልጅን በመልካም ቃልና በሞራል ብናበረታታ የእድገታችን ምዕራፍ ቀዳሚ ይሆናል። በቤተሰብ ደረጃ ያለውን የመከባበር፣ የመደናነቅና መልካም የማሰብ ባህል ወደ ጎረቤት፣ በጎረቤት ያለውን በከተማ፣ በከተማ ያለውን በሀገር ደረጃ እናሳድግ፤ ይህም ዘላቂነት እንዲኖረው መልዕክቱን በትምህርት ቤትና በመገናኛ ብዙኃን አማካኝነት እናሰራጭ። በአጠቃላይ የመደናነቅ፣ የመከባበርና የቀና አስተሳሰብ ባህልን በመላው ኢትዮጵያ በተቀናጀ መልኩ በስራ እንተርጉም›› ብለዋል።
ቅንነት እየተዳከመ ባለበት ወቅት ቅንነትን ለማጎልበት የሚከናወኑ ተግባራት ብዙ መሰናክሎች እንደሚያጋጥሟቸው መገመት ከባድ አይሆንም። ‹‹ቅን ኢትዮጵያ›› ስላጋጠሙት ችግሮች አቶ ተፈራ እንዲህ በማለት ያብራራሉ፡- ‹‹ሁላችንም እንደምንረዳው በአሁኑ ወቅት ትልቅ የቅንነት ችግር አለ። ‹ቅን ኢትዮጵያ› በ2002 ዓ.ም ቢመሰረትም ለ10 ዓመታት ያህል ይዟቸው የተነሳቸውን ዓላማዎች ለማሳካት የሚያስችሉትን ስራዎች እንዳይሰራ ብዙ መሰናክሎች ተፈጥረውበት ቆይቷል።
የማኅበሩ ፈቃድ እንዳይታደስ እንዲሁም ‹ለመሆኑ ‹ቅን ኢትዮጵያ› ማለት ምን ማለት ነው?› እየተባለ አላስፈላጊ ለሆኑ ትርጓሜዎች እንዲጋለጥ ሲደረግም ነበር። ይህ ሁሉ የሚያመለክተው በየደረጃው ያለውን የቅንነት ማጣት ችግር ነው።›› ይላሉ። ከዚህ አስቸጋሪና አላስፈላጊ ሁኔታ ውስጥ ለመውጣት በመገናኛ ብዙኃንና በኪነ-ጥበባዊ መሰናዶዎች በኩል ለሕዝቡ ተደራሽ መሆን አስፈላጊ እንደሆነ ይመክራሉ። መከባበር፣ መደናነቅና መልካም አስተሳሰብ በሰዎች ልብ ውስጥ ካሉ፤ የጠፉ ነገሮችንም መልሶ ማምጣትና ማዳበር እንደሚቻልም ይገልፃሉ።
‹‹በሀገራችን በሁሉም ዘርፎች ጎልቶ የሚታየው የቅንነት ማጣት ችግር እንደ ኢትዮጵያዊ ቁጭ ብለን ተነጋግረንና ተደማምጠን ለሀገራችን የሚበጀውን በጋራ ለማድረግ እንድንችል ያስገድደናል። አንዱ ተናግሮ እስከሚጨርስ ድረስ እንኳ አንጠብቅም። ብዙ አለመግባባቶች የሚፈጠሩት ባለመደማመጥ ምክንያት ነው። ይህ አለመደማመጥ ደግሞ ከቅንነት ማነስ የመነጨ ሊሆን ይችላል። ይህ ዓይነቱ ባህርይ የኅብረተሰባችን ባህል ሆኖ እንዳይቀጥል ስለቅንነት መነጋገርና በቅንነት መጓዝ ይገባል›› ይላሉ።
‹‹በአሁኑ ወቅት በብዙ ትምህርት ቤቶች የጀመርናቸው ስራዎች አሉ። በየትምህርት ቤቶቹ የቅንነት ክበባትን በማቋቋም ተማሪዎች ቅንነትን ባህል አድርገው እንዲያድጉ እየሰራን ነው። ይህ ስራ በተወሰኑ ትምህርት ቤቶች ተጀምሯል። በቀጣይም አቅም በፈቀደ መጠን ይህን ተግባር በሌሎች ትምህርት ቤቶች ለማስፋት ጥረት ይደረጋል። የስነ ምግባርና የግብረ ገብነት ትምህርት በስርዓተ ትምህርት ውስጥ ተካትቶ እንዲሰጥ ማኅበሩ የራሱን አስተዋጽኦ ያበረክታል። የተማሪዎች የመመሰጋገንና የመደናነቅ ቀን ሲከበር ቆይቷል። በቀጣይ ጊዜ ይህ በመምህራንና በተማሪዎች ብቻ ተወስኖ የሚገኘው ኹነት በሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል እንዲተገበር ‹‹ሀገር አቀፍ የመመሰጋገንና የመደናነቅ ቀን›› በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት እንዲታወጅ ጥረት ያደርጋል። የመልካም አስተሳሰብ፣ የመደናነቅና የመመሰጋገን ባህሎች በሁሉም ተቋማትና የኅብረተሰብ ክፍሎች እንዲለመዱ በግንዛቤ ማስጨበጫና በሌሎች ዘዴዎች አማካኝነት የተጀመሩ ጥረቶችን አጠናክሮ ያስቀጥላል›› በማለት ስለማኅበሩ ቀጣይ እቅዶች ገልጸዋል።
አንተነህ ቸሬ
አዲስ ዘመን ሰኔ 9/2015