ዓለማችን ሶስተኛውን የኢንዱስትሪ አብዮት አገባዳ ወደ አራተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት ማማተር ከጀመረች ሰነባበተች ። ሶስተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት ከ20ኛው መክዘ አጋማሽ ዛሬ ድረስ የቀጠለው ሲሆን ፤ የዲጂታል ቴክኖሎጂ፣ በይነ መረብ ወይም ኢንተርኔት፣ አውቶሜሽን፣ ሮቦቲክስና ሌሎች ቴክኖሎጂዎች የተስፋፉበትና በስፋት ጥቅም ላይ የዋሉበት ነው። ብዙ ሊቃውንት አሁን የምንገኝበትን ጊዜ የአራተኛው የኢንዱስትሪ አብዮት የተጀመረበት፤ የዲጂታል ቴክኖሎጂ የተቀናጀበት፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ወደ ስራ የገባበት፣ በይነ መረብ እያንዳንዱን የህይወት ቅንጣትና የኢኮኖሚ ዘርፍ ማዳረስ የጀመረበት ከመሆኑ ባሻገር በአኗኗራችንና በግንኙነታችን ላይ ዕለት ዕለት እየተገለጠ ያለ ነው። እጃችን የገባን ቴክኖሎጂ ተለማምደነውና ተዋውቀነው ሳናበቃ እጃችን ላይ የሚያረጅበትና በፍጥነት የሚለዋወጥበት ዘመን ነው።
ዓለማችን ዲጂታል እየሆነች ነው። በዲጂታል ቴክኖሎጂና በኮሙኒኬሽን ኔትወርክ እየተሳሰረች በአኗኗራችን፣ በስራችንና በዕለት ተዕለት ግንኙነት ላይ ለውጥ እየመጣ ነው። ከዚህ ጋር የተያያዙ ዲጂታል መሳሪያዎች፣ የሶፍትዌር መተግበሪያዎች፣ እንደ ፌስቡክ ያሉ ማህበራዊ መድረኮች፣ በመረጃ ወይም በዳታ ላይ የተመሠረቱ እንደ መረጃ የማፈላለግና ኮሙኒኬሽን አገልግሎቶች እየተስፋፉ ነው። ፍጥነት፣ ተለዋዋጭነት፣ የማያቋርጥ መሻሻል፣ ወዘተረፈ የዲጂታል ዓለሙ መለያ ነው።
ለፈጠራና ለንግድ አዳዲስ ዕድሎችን ይዞ እንደመጣው ሁሉ የዜጎችን ግለ ህይወት ወይም ፕራይቬሲ፣ ደህንነትና ግንኙነት አደጋ ላይ እየጣለ ነው። የተሳሳተና ሆን ተብሎ የተዛባ መረጃ እንደ እንጉዳይ እየፈላ፤ በይነ መረብ፣ ማህበራዊ ሚዲያ፣ የሞባይል ስልኮች፣ ክላውድ፣ ቢግ ዳታ አናሌቲክስ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎትና ብሎክቼይን የዲጂታል ዓለሙን ወደ አዲስ ምዕራፍ እያሸጋገሩት ይገኛል። እነዚህ የቴክኖሎጂ እምርታዎች መረጃን በቀላሉ እንድናጋራና እንድንለዋወጥ፣ ከሌሎች ጋር እንድንተባበር፣ ሒደቶችን አውቶሜት እንድናደርግ፣ የዲጂታል ምርቶችንና አገልግሎቶችን እንድናስፋፋ በመጋዝ አኗኗራችንና አሰራራችን አቅልለውልናል።
ወደ አኅጉራችን አፍሪካ ስንመጣም በስፋት ጥቅም ላይ እየዋለ እናገኘዋለን። ዲጂታል ቴክኖሎጂዎችና ፈጠራዎች በፍጥነት እያደጉ ነው። የተንቀሳቃሽ ስልክና የበይነ መረብ ተጠቃሚዎች መበራከት ለአፍሪካ ዲጂታል ኢኮኖሚ ማበብ የማይተካ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ዲጂታል አፍሪካ ሰፋ ያለ የዲጂታል ቴክኖሎጂን ማለትም የሞባይል ስልኮችን፣ ማህበራዊ ሚዲያን፣ ኢ-ኮሜርስን፣ የዲጅታል ክፍያን፣ ፊንቴክን፣ ኢ-ጤናን፣ ኢ-ትምህርትን እና ኢ-ግብርናን የሚያካትት ነው።
በአኅጉሩ ለዲጂታል ፈጠራ መስፋፋትና መጎልበት የአንበሳውን ድርሻ እየተጫወተ ያለው ደግሞ የሞባይል ስልክ ሲሆን ለበይነመረብ ተደራሽነትና ለዲጂታል አገልግሎት መስፋፋትም የማይተካ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ሞባይል መኒ በአፍሪካ እያደገ ለመጣው የፋይናንስ አካታችነት እንዲሁ የላቀ አስተዋጾ እያበረከተ ነው።
በሚቀጥሉት ዓመታት የዲጂታል ኢኮኖሚ ተጽዕኖ በአፍሪካ አሁን ከሚገኝበት ይልቅ እያደገና እንደ ዋርካ እየሰፋ እንደሚሄድ አገራችን ጥሩ ማሳያ ናት። የዲጂታል መሰረተ ልማት መስፋፋት ለዲጂታል ኢኮኖሚው ጥሩ መደላድል እየፈጠረ ነው። ሆኖም ተግዳሮቶች የሉበትም ማለት አይደለም።
የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተደራሽነት በእኩል ደረጃ አለመገኘት ወይም ዲጂታል ዲቫይድ ቀዳሚው ችግር ነው። ዜጋው ስማርት ስልኮችን፣ ታብሌቶችን፣ ላፕቶፖችንና በይነ መረብን በቀላሉ አለማግኘቱ የመረጃ ተደራሽነቱን ኢፍትሐዊ አድርጎታል። የዲጂታል ክህሎት እጥረትና የዲጂታል ኢንቨስትመንቱ ውስን መሆን ሌላው የዘርፉ ማነቆ ነው። ለመሆኑ በአገራችንስ ዲጂታል ኢኮኖሚው በምን ሁኔታ ነው የሚገኘው።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ የተቋማቸውን የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረቡበት ወቅት የተናገሩት ከሞላ ጎደል የዲጂታል ኢትዮጵያን ምስል ቅንብብ አድርጎ ያሳያል ብዬ አስባለሁ። የመንግሥት ኤሌክትሮኒክስ ክፍያ ድርሻን ለማሳደግና ቀልጣፋ ለማድረግ እስካሁን የ159 ባለ በጀት መሥሪያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ክፍያ ዘዴ እንዲተገብሩ መደረጉን ያስታወቁት ሚንስትሩ፤ ለአብነትም በተያዘው ዓመት የዘጠኝ ወራት 79.2 ቢሊዮን ብር ክፍያ በኤሌክትሮኒክስ ዘዴ መከፈሉን፤ ኢትዮ ቴሌኮም የመንግሥት የኤክትሮኒክስ ክፍያ ድርሻ ለመወጣት እንዲያስችለው የሪፎርም ሥራዎችን እየሠራ ይገኛል።
ለአብነትም የታክስ ክፍያ አሰባሰብ ሥርዓቱ በቴሌ ብር እንዲከፈል የሚያስችል ሥርዓት መዘርጋቱን፤ በባንኮች በኩል ተከፋይ የሚሆነውን የመንግሥት ሠራተኞች ደመወዝ በቀጣይ በቴሌ ብር እንደሚሆን መገለጹን ተከትሎ ኩባንያው የሚጠብቀው ቅድመ ዝግጅትና ያለው ዓቅም ምን ይመስላል? በሚለው ዙሪያ የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ ኮሙዩኒኬሽን ኦፊሰር አቶ መሳይ ውብሸት ለሪፖርተር እንዳስረዱት ፣ በመንግሥት የተያዙት ጉዳዮች ወቅቱን ጠብቀው ቢገለጹ እንደሚሻል ተናግረው፣ ነገር ግን ኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎቱን ለማቅረብ የሚያስችል በቂ ዝግጅትና አቅም እንዳለው አስታውቀዋል ።
ተቋሙ በሞባይል ገንዘብ ዝውውር አገልግሎቱ እስካሁን ከ32 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን አገልግሎት እየሰጠ እንደመገኘቱ መጠን የዘረጋው ሲስተም አገልግሎቱን በቀላሉ ለመስጠት ያስችለዋል ። የትኛውም ውሳኔ ከሚመለከተው አካል ከመጣ መሥራት እንደሚቻል፤ ደመወዝ በቴሌ ብር መከፈሉ የተቋማትን ቅልጥፍና በመጨመር የሚያደርገውን አስተዋጽኦ በመግለጽ፤ በዕረፍትና በበዓላት ወቅት የሚውል የደመወዝ ክፍያ ቀንና ተዛማጅ ጉዳዮች ለደመወዝ ከፋዩም ሆነ ተከፋዩ በሚያመች ለመክፈል እንደሚያስችል አቶ መሳይ ይናገራሉ ።
እስካሁን ባለው አገልግሎቱ እንደ ደመወዝ ዓይነት የጅምላ ክፍያ በሚከፈልበት ወቅት ሠራተኞች የደመወዛቸውን እስከ 35 በመቶ ያለምንም ዋስትና መበደር እንደሚችሉ፤ ኩባንያው በቀጣይ ሌሎች ተጨማሪ አማራጮች እንደሚያቀርብና እስካሁን ድረስ ግን ከሚመለከተው አካል የመጣ አቅጣጫ አለመኖሩን አቶ መሳይ አጽንኦት ሰጥተዋል ።
ኢትዮ ቴሌኮም የቴሌ ብር የሞባይል ገንዘብ ዝውውርን ይፋ ካደረገበት ግንቦት 3፣ 2013 ዓ.ም ጊዜ አንስቶ እስከ ግንቦት 2015 ዓ.ም ድረስ 32.2 ሚሊዮን ደንበኞች እንዳፈራ፤ በአገልግሎቱም እስካሁን ከ375.2 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው ግብይቶች (ትራንዛክሽንስ) እንደተፈጸመ አስታውቋል ። እንዲሁም የነዳጅ ክፍያ በአስገዳጅነት በቴሌ ብር እንዲፈጸም ከተደረገበት ከሚያዝያ 16 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ 2.7 ቢሊዮን ብር ግብይት መፈጸሙ ታውቋል ። ስለ ዲጂታል ክፍያ ወቅታዊ ሁኔታ ካነሳሳሁ ላይቀር፤ የዲጂታል ኢትዮጵያን ታሪካዊ ዳራ መለስ ብለን እንቃኝ ።
ወደ አገራችን ስንመጣ ኢትዮጵያ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን ቀርፃ እና አፅድቃ ወደ ስራ ከገባች ዓመት ሆኗታል ። ዲጂታል ኢትዮጵያ የዲጂታል ዕድሎችን በመጠቀም ፈጠራ የታከለበትና በእውቀት ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያስችል በኢትዮጵያ መንግስት የሚመራ ተነሳሽነት ነው ። ከአገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ እና የ10 ዓመት የልማት ዕቅድን ከመሳሰሉ ቁልፍ አገራዊ ስትራቴጂዎች ጋር እንዲሁም እንደ አፍሪካ ህብረት አህጉራዊ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂ ካሉ ዓለም አቀፍ ስትራቴጂዎች ጋር የተሳሰረ ነው ።
ዲጂታል ኢትዮጵያ የመንግሥትን፣ የግሉን ዘርፍና የልማት ኤጄንሲ ተዋንያንን በአንድ ላይ በማሰባሰብ፣ መሰረታዊ የዘርፍ ተነሳሽነትን በመለየት የአገሪቱን ዲጂታል ኢኮኖሚ ጉዞን ለማሳለጥ እንዲሁም የኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን በግንባር ቀደምትነት ለመምራት የሚችሉና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ሊጠቀሙ የሚችሉ አራት ስትራቴጂያዊ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ዘርፎችን ለይቷል ። ግብርና፣ የማምረቻ ዘርፍ፣ የመረጃ ቴክኖሎጂና ቱሪዝም ቅድሚያ የተሰጣቸው ዘርፎች ናቸው።
ግብርና፡-
በግብርና ውስጥ የበይነ መረብ ቁሶች አርሶ አደሮች ምርታቸውን እንዲቆጣጠሩ ማስቻል፣ ጥብቅ ሰንሰለት ደግሞ ፍትሃዊ የንግድ ውድድር፣ ደህንነቱ የተጠበቀና የተሻሉ (ርካሽ) የክፍያ አማራጮችን ተግባራዊ ለማድረግ እንዲያስችላቸው ማድረግ ነው ። ኢትዮጵያን በዚህ ዘርፍ ውጤታማ ለማድረግ ሁለት ምቹ እድሎች ተለይተዋል። አንደኛው የዲጂታል ግብርና መድረክ መገንባት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቴክኖሎጂ መር የሆኑ የግብርና ኢንተርፕራይዞችን (ቴክ-ግብርና) መደገፍና ማበረታታት ናቸው ።
ማምረቻው ዘርፍ ፡-
በዓለም አቀፍ ገበያዎች ተደራሽነትን ለማስፋት በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ አዳዲስ የግንኙነት ቴክኖሎጂዎችን መቀበል እና መፍጠር ማስቻል እና ኤክስፖርትን ለማሳደግ በዲጂታል የተደገፉ የሎጂስቲክስ አያያዝ አካሄዶችን ማጎልበት ናቸው።
የመረጃ ቴክኖሎጂ፡-
በመረጃ ቴክኖሎጂ አስቻይ የሆነባቸው አገልግሎቶች መገንባትን ይመለከታል።
ከዚህ አማራጭ አንጻር ኢትዮጵያ ሁለት መልካም አጋጣሚዎች ተለይተዋል።
የመጀመሪያው ለባለ ከፍተኛ አቅም እና ተሰጥዖ ማዕከላት መሰረተ ልማት ማቅረብ ሲሆን÷ ሁለተኛው ደግሞ መሪ የንግድ ሥራ ሂደት አቅርቦትን ሊስቡ የሚችሉና ተሰጥኦ ማሳደጊያ የመረጃ ቴክኖሎጂ ፓርክን ዳግም በማዋቀር በሙሉ አቅሙ ወደ ስራ ማስገባት ናቸው።
ቱሪዝም፡-
ቱሪዝምን ተወዳዳሪ ለማድረግ የዲጂታል አሰራር መዝርጋት ያስፈልጋል። ይህንን ለማድረግ ሶስት መልካም አጋጣሚዎች ተለይተዋል።
የመጀመሪያው የቱሪዝም ዲጂታላይዜሽን ግብረ ኃይል በማቋቋም የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ዲጂታላይዝ ማድረግ ሲሆን÷ ሁለተኛው ደግሞ የዲጂታል የገበያ ስርዓትን በማበጀት የቱሪስት ፍሰትን እና የቆይታ እና ተሳትፎ መጠኑን ማሻሻል ነው ። ሶስተኛው ደግሞ በቱሪዝም ዘርፍ የተሰማሩ አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችን የዲጂታል አገልግሎት እንዲሰጡ አቅም መገንባት ነው ።
ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምንድነው?
ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን÷ በአካል ከሚደረጉ ግንኙነቶች ወጥቶ የዲጂታል አሰራሮችን በመተግበር ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ ለመድረስ ባለ ሂደት ውስጥ ያለ “ጉዞ” ነው። የዲጂታል የሽግግር ጉዞ በመንግስት፣ በንግድ ድርጅቶች እና በማህበረሰቡ መካከል ግንኙነት በአካል ይካሄድ ከነበረበት አናሎግ ህብረተሰብ ወጥቶ ግንኙነትና ልውውጦች በበይነ መረብ በጣም ፈጣን፣ ርካሽ፣ እና ደህንነቱ አስተማማኝ የሆነን ቴክኖሎጂን በመጠቀም ወደ ሚካሄዱበት የተቀናጀና አካታች ዲጂታል ኢኮኖሚ የሚደረግ ጉዞ ነው።
ዲጂታል ኢኮኖሚ የሚያመለክተው የተሻሻለ የኔትወርክ ግንኙነቶችን እና እርስበርስ ተያያዥነት ያላቸውን የዲጂታል መድረኮችን በመጠቀም የሚደረግ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን ነው።
የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ከአናሎግ ኢኮኖሚ ይጀምራል። በአናሎግ ኢኮኖሚ ውስጥ በዜጎች በመንግስትና በንግድ ድርጅቶች መካከል ያለው ግንኙነት የዲጂታል ቴክኖሎጂን የማይጠቀም እና በአካል የሚደረግ ነው።
ከአናሎግ ኢኮኖሚ ቀጥሎ የሚገኘው ደግሞ ዝቅተኛ የዲጂታል ተደራሽነት ነው። በዚህ ውስጥ ውስን የዲጂታል መሰረተ ልማት ይኖራል፤ የተወሰኑ የዲጂታል ማሳያዎች ብቅ ብቅ ማለት ይጀምራሉ።
የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞው ይቀጥልና አናሎግ ግን የዲጂታል አሰራር እያደገ ይሄዳል። በዚህ ውስጥ አብዛኞቹ አገልግሎቶች አናሎግ የሆኑበት፣ ግልፅ የሆነ የዲጂታል ራዕይ ካልተቀናጁ አገልግሎቶች ጋር ያሉበት እና የሚተገበርበት ነው።
ይህ አናሎግ እና ያልተቀናጀ የዲጂታል አገልግሎት ደግሞ የተቀናጀ የዲጂታል ስርዓትን ይወልዳል።
በዚህ ውስጥ የላቀ፣ የተቀናጀ የዲጂታላይዜሽን አገልግሎትና ጠንካራ አስቻይ ስነ ምህዳሮች ይኖራሉ ። የዲጂታል ኢኮኖሚም ይገነባል።
የዲጂታል ኢኮኖሚ የተሟላ የዲጂታል ኢኮኖሚ የተተገበረበት፣ ከመንግስትና የንግድ ተቋማት ጋር ለመገናኘት የዲጂታል አገልግሎትን የሚጠቀም ነው ። የንግድ ተቋማት ፈጠራ የታከለበት አገልግሎት ያቀርባሉ። የመንግስት ስራዎችና አገልግሎቶች ዲጂታል ይሆናሉ።
አብዛኞቹ የንግድ መነሻዎች ዲጂታል ይሆናሉ ።
ጎረቤት አገር ኬንያ ከ14 ዓመታት በፊት የጀመረችው ‘ኤምፔሳ’ የተሰኘውን የሞባይል ገንዘብ ስርዓት አሁን ላይ 72 በመቶ የሚሆነው የአገሪቱ ነዋሪ እየተጠቀመው ይገኛል ይላል ቮክስ ከተባል ድህረ ገጽ የተገኘ መረጃ ። በሰባት አገራት የሚሰራው ኤምፔሳ 42 ሚሊዮን ንቁ ደንበኞችና 400 ሺህ ወኪሎች አሉት ። 50 በመቶ የሚሆነው የኬንያ ዓመታዊ ጥቅል ምርት/GDP/በዚሁ ስርዓት በኩል ይንቀሳቀሳል ። በኡጋንዳ ከጠቅላላ ህዝቡ የባንክ አካውንት ያለው 11 በመቶ ሲሆን ኤምፔሳን የሚጠቀመው ሰው ግን 42 በመቶ ተሸጋግሯል ። እናም እነዚህ አገራት ከግብይት በኋላ ቁጥር ህ/ሽን ንገረኝ ማለት የተለመደ ነው ይለናል ቢቢሲ ።
ሻሎም ለኢትዮጵያ ! አሜን ×፫ ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 24 ቀን 2015 ዓ.ም