የመነሻ ወግ፤
ለጉልምስናና ለሽበት ወግ የበቁ “ፊደል ቆጠር” ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ስለ የክብር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል አንድም ዝናቸውን በመስማት አልያም መጻሕፍታቸውን በማንበብ እውቀት ሳይቀስሙ እንደማይቀሩ ይገመታል:: ይህ ማለት ግን ዕድሜውን ያደላቸው “አንቱዎቻችንን” በሙሉ ይመለከታል ማለት እንዳልሆነ ልብ ይሏል::
በአካልም ሆነ በመጻሕፍታቸው ለሚያውቋቸው ትዝታቸውን ለመቀስቀስ፣ ለማያውቋቸው ደግሞ ስለ እኚህ ነፍሰ ሔር የአገራችን የሥነ ጽሑፍ ዐምድ በጥቂት ቃላት ዘክረናቸው እንለፍ:: ከበደ ሚካኤል ልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮችን መነሻ በማድረግ ባሳተሟቸው መጻሕፍት ቀዳሚውን ትውልድ በእውቀትና በሥነ ምግባር በማነጽ ረገድ በአክብሮት የሚጠቀሱ መጋቤ እውቀት አርአያ ሰብ ናቸው::
የፋሽስት ኢጣሊያ ሠራዊት በሽንፈት ተዋርዶ በተባረረ ማግሥት (ከ1934 ዓ.ም ጀምሮ) ታሪክና ምሣሌ (1ኛ እና 2ኛ) በሚሉ አርእስት ካሳተሟቸው መጻሕፍት በማስከተል እስከ እለተ ህልፈታቸው ድረስ ከ25 በላይ ድንቅ መጻሕፍትን ለትውልዱ አበርክተዋል::
በግጥምና በዝርው የቀረቡ መሳጭና ጣፋጭ ተረትና ምሣሌዎችንና ቲያትሮችን (የትንቢት ቀጠሮ፣ ሮሜውና ዡልዬት፣ አኒባል፣ በላይነህ፣ አጼ ካሌብ)፣ የታሪክ መጻሕፍትን (ታላላቅ ሰዎች፣ የዓለም ታሪክ፣ ግርማዊነታቸው በአሜሪካ፣ ጃፓን እንደምን ሰለጠነች፣ ትልቁ እስክንድር ወዘተ.)፣ እና ለጠቅላላ እውቀትና ለመንፈሳዊ ህንጸት የሚረዱ በርካታ ሥራዎችን አበርክተውልናል::
ይህንኑ የአገር ባለውለተኛነታቸውን በማስታወስም “መልካም ለሠሩ ሰዎች ሽልማት መስጠት ብቻ ሳይሆን ትምህርትም የሚሰጥ እንደ አንድ ዩኒቨርሲቲ የሚቆጠር ነው” ተብሎ ይደነቅ የነበረውን የመጀመሪያውን የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሽልማት ድርጅት ንጉሣዊ ሽልማት በ1957 ዓ.ም ለማግኘት ከበቁት ታላላቅ የአገሪቱ አንቱዎች መካከል አንዱ ነበሩ:: የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲም በ1990 ዓ.ም የክብር ዶክትሬት በመስጠት አክብሯቸዋል:: የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበርም እንዲሁ በ2002 ዓ.ም የመታሰቢያ ቴምብር ካሳተመላቸው በርካታ የሥነ ጽሑፋችን ፈር ቀዳጆች መካከል አንዱ ከበደ ሚካኤል ነበሩ::
ይህ ዐምደኛም ለአገሩ ሕጻናት ያሳተመውን ስድስት ያህል የግሉን መጻሕፍት አክብሮቱን በመግለጽ ያበረከተው ለእኚሁ “የቀለም ቀንድ አባት” ነበር:: “ደራሲው ዛሬ ለደረሰበት ደረጃ እንዲበቃ በልጅነት ዕድሜው በመጻሕፍታቸው አማካይነት መሠረት ለጣሉለት ለክብር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል … መታሰቢያ ይሁን” በማለት::
የግሪክ፣ የሮማዊያን፣ የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ፣ የጀርመን፣ የሩሲያና የጣሊያንን በርካታ መጻሕፍት በመመርመር “የቅኔ አዝመራ” እና “የቅኔ ውበት”ን ለትውልዱ ሲመግቡ የኖሩት እኚህ አንጋፋ ታላቅ ደራሲ ከመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊነታቸው ጎን ለጎን መጻሕፍትን ለምን ማዘጋጀት እንደፈለጉ የገለጹት እንዲህ በሚል ግጥም ነበር::
“የፊደል ባላገር የቀለም ገበሬ፣
ከመቼውም ይልቅ ባሁን ዘመን ዛሬ፤
በብርድ በንዳድ ሳይገባው ስንፍና፣
መዳከር መዋተት ይገባዋልን፤
እነሆ አቀረበ ዋታቹ ሰብሳቢ፣
በልቶ እንዲጠግብለት የራበው አንባቢ::
ከደራሲው አጫጭር ግጥሞች መካከል በዚህ ጽሑፍ ለማስተላለፍ ለተፈለገው “አውራ መልእክት” ማጎልበቻ እንዲሆን የተመረጠውን አንድ በግጥም የቀረበ ተረት ወደ ዝርው ጽሑፍ ለውጠን እንደሚከተለው እናስታውሳለን:: “አንዲት ዝንጀሮ ጥቅጥቅ ባለ ቆንጥር በሞላበት ጫካ ውስጥ ስትጓዝ ሰውነቷ ሁሉ በእሾህ ይወረራል:: በመላ አካላቷ ላይ የተሰካው እሾህ ለመቆምም ሆነ ለመቀመጥ ሕመሙ ፋታ ሊሰጣት ስላልቻለ አየተጨነቀችና እያቃሰተች ባለችበት ሁኔታ አንድ መንገደኛ በድንገት በዚያ ጫካ ውስጥ ሲያልፍ ያያታል::”
“ስቃዩዋንና የደሟን መንዠቅዠቅ ያስተዋለው ርሁሩህ መንገደኛ በግዴለሽነት አይቶ እንዳላየ ለማለፍ አልወደደም:: ቀረብ ብሎ በሀዘኔታ እንዲህ ሲል ጠቀየቃት “በመጀመሪያ የቱን ልንቀልልሽ?” ዝንጀሮዋም እያቃሰተች በአራራይ ዜማ አጅባ እንዲህ በማለት በግጥም መለሰችለት” ይሉናል ከበደ ሚካኤል – ዝንጀሮዋን እንደ ሰብዓዊ ፍጡር እያናገሩ::
“ከነቀልክልኝስ አለችው ጌታዬ፣
መጀመሪያ ይውጣ የመቀመጫዬ::
ቂጤ መሬት አርፎ ትንፋሼን ካገኘሁ፣
የቀረውን ሁሉ እኔ እነቅለዋለሁ::
በማለት ዝንጀሮ ተናግራ አረፈች፣
ሁሉን በየተራ እያወጣች ጣለች::
የደራሲውን አገራዊ ደማቅ አተዋጽኦና ሥራዎቻቸውን ማስተዋወቁን እዚህ ላይ ገታ በማድረግ ወደ ዋናው የመነሻ ጉዳያችን እናቅና::
“ኢትዮጵያ ሆይ! ‹እሾህ ወጋሽ?› ክፉሽን ይውጋ”፤
የዛሬይቱን አገሬን በእሾህ የሚመሰሉ በርካታ ችግሮችና ፈተናዎች ትንፋሽ አሳጥተው የሚያስቃትቷት ይመስለኛል:: ልክ “እንደ ዝንጀሮዋ ሁሉ” ተረጋግታ ለመራመድና ለማረፍ እንዳትችል የውጥር የያዟት ተግዳሮቶች በዓይነትም ሆነ በባህርይ እጅግ የተወሳሰቡ እንደሆኑ እያስተዋልን ነው:: ጠንከር ሲልም ሙሾ አሙሺው ባለ አገር ወገኔ በመቃተት፤
“ለእኔ እናት ምን በጃት፣
ያም አፈር፣ ያም ድንጋይ
ያም ኮረት ጫነባት”
በማለት እንባውን እያዘራ አንጎራጎረ እንዲል ሥነ ቃላችን፤ በእናት ዓለም ላይ ከእለት ወደ እለት የሚበረቱባትን ክፉ የመውጊያ እሾሆች ባሰብኩ ቁጥር ሆድ እንደ ባሰው ጨቅላ የማነባው በሥጋ ዐይኔ ቁልቁል በጉንጮቼ ላይ በሚወርደውና በለሆሳስ ወደ ውስጥ በሚፈሰው እምባዬ ብቻ ሳይሆን እንዲህ እንደ ዛሬው ብዕሬም እንዲያላቅሰኝ በመማጠን ጭምር ነው::
በትእግስትና በመከባበር፣ በመነጋገርና በመደማመጥ፣ በመተማመንና በመቀባበል ለኢትዮጵያ እረፍትና እድገት ተባብረንና እጅ ለእጅ ተያይዘን ከመሥራት ይልቅ ምስኪን አገሬ በፖለቲካውም ሆነ በኢኮኖሚው፣ በአገር ልጆችም ሆነ በዲያስፖራው የሴራ ጡጫና እርግጫ ስለምን በግላጭና በስውር በእሾህ ጅራፍ እንደምትጠበጠብ ማሰቡ በራሱ ናላ ያዞራል:: ይህ መከራዋ ለቅን ልጆቿ ግራ ሲያጋባ፤ ለመሠሪዎቹ “የእንግዴ ልጆቿ” ደግሞ “ደሟና ስቃዩዋ” የደስታና የግቢ ምንጭ ሆኗቸዋል::
በነጋ በጠባ እንደምናስተውላቸው እንደ ዛሬዎቹ ችግሮቻችን ትናንትናና ከትናንት ወዲያ በአባቶቻችን ዘመን ተመሳሳይ ፈተናዎችና ችግሮች ገጥመዋት ነበርን? ብለን ጠይቀን መልስ የሚሰጠን ሁነኛ አረጋጊ እስካሁን ፈልገን ለማግኘት አልታደልንም:: ፈልጎም ሊያጽናናን የሚችል በጎ ፈቃደኛ ለማግኘት ብርቅ ሆኖብናል:: ስለምን የቤት ልጅ ጠላትና የውጭ ባእድ ደመኛ በአገሬ ላይ እንደሚረባረቡ ገምተን ገምተን ስላልተሳካልን እነሆ ዛሬም እንደ ትናንቱ “እህህ” እያሉ ከመቆዘም ልንገላገል አልቻልንም:: ከጎበጥንበትም ቀና ለማለት አቅም አላገኘንም::
አንዱ አገራዊ የችግር እሾህ ተነቀለ ሲባል ሌላ ክፉ እሾህ እየተወረወረ ያስለቅሰናል፣ ስለምንና እንዴት መሽቶ በነጋ ቁጥር አገሬ በእሾህ ቆንጥር እንድትወረር እንደሚፈለግ ለማወቅ እንቆቅልሹ ውስብስብ ሆኖብናል:: ደግሞስ የልጅ ወጉ ከአገር ገላ ላይ እሾኋን በመንቀል እፎይታ መስጠት እንጂ እንደምን በእሾህ እንድትገረፍ ይፈረድባታል?
በውስጥም ሆነ በውጭ ካሉ ደመኞቿ ጣፋጩ ማር እንዲመርና መራራው ሬት እንዲጣፍጥ መሰበኩና መተግበሩ ለማን ምን ጥቅም እንዲያስገኝ ታስቦ እንደሆነ ምሥጢሩ በሚገባ አልተገለጸልንም:: ግምታችንን እንሰንዝር ካልን ምናልባትም ከእለት ጉርስ የሚያልፍ አገርን በመሸጥ የሚገኘው ጥቅም እያማለላቸው ይሆንን ብለን መገመታችን አልቀረም:: በግሌ ከላይም ሆነ ከጎን ያሉትን የአገሬ ወፈ ሰማይ ፖለቲከኞች የምመስላቸው በኮንትሮባንድ የተሰበሰበን ልባሽ ጨርቅ እንደሚሸጡ ሱቅ በደረቴዎች ነው::
ሱቅ በደረቴዎች ለሽያጭ ይዘው የሚዞሩት ልባሽ ጨርቆች የተሰበሰቡት አንድም “ነፍስ ይማር!” የሚል ቅጽል ከተሰጣቸው የሙታን ገላ ላይ ተገፈውና የመጡ ናቸው:: ያልባሳቱ የመጀመሪያ ባለቤቶች ሥጋቸው በአገራቸው የተቀበረ ቢሆንም ባሕር ተሻግረው ከእኛ ዘንድ ደርሰው የምንለብሳቸውና የምንጫማቸው ድህነታችን፣ መናቆራችንና ስንፍናችን በሩን ወለል አድርጎ ስለከፈተላቸው ነው:: “ልመና የለመደ እጅ አይታጠፍም” የሚለው ብሂል ቢጠቀስ ቦታው ይመስለናል::
ከፊል ልባሽ ጨርቆች ደግሞ በአገር ጓሮ ተሹለክልከው የገቡት አንድም በእርዳታ ስም፣ አንድም ለነፍሳቸው ጽድቅን ከፈለጉ ባለጠጎች ተመጽውተው፣ አለያም ቁምሣጥን ከሚያጣብቡ ተብለው ተወርውረው ከተሰባሰቡ ውራጆች ሊሆን ይችላል:: ከዚህ ያለፈ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ታስቦ ነው ብሎ መደምደሙ የመንፈስ ራቁትነትን ከማመልከቱ ውጭ ምንም ማለት አይቻልም::
የአገሬ ፖለቲከኞችን በኢምፖርት ልባሽ ጨርቆች ለምን እንደመሰልኳቸው ብዙ ትንታኔ መስጠቱ አስፈላጊ መስሎ አልታየኝም:: “የጀመርከውን ሃሳብ ሳትቋጭ አንዳታልፍ?” በማለት የሚሞግትና ግድ የሚል ካለም በግብራቸው ሳይሆን በስማቸው ብቻ “የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም” እየተሰኙ የሚያበጣብጡንን አቋሞች መፈተሽ ብቻ በቂና ከበቂ በላይ ይሆናል:: “የልባሽ ፖለቲካ” አራማጆቹ ሰብእናና ግብ ምን ሊሆን እንደሚችል ከግብራቸውና ከውሏቸው መረዳቱ አይከብድም:: ዕድሜ ደጉ ብዙ አሳይቶናል፤ ዘንድሮም ከማየት አልቦዘንንም::
ለመሆኑ አገራዊ በረከቶቻችንን እየቆጠርንና የጎደለውን እያሟላን ለተሻለ ነገ ከመሥራት ይልቅ የተጣለው መሠረት እንዲፈርስና የሕዝብ ሮሮ አየራችንን እንዲበክል በማድረግ የት መድረስ ይቻላል? ድፍርስ ውሃ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ እንደሚጣራ ሁሉ የጠቆረው የአገራችን ደመናም ያጋተው የብሶት ጩኸትና እዬዬ የሚጣራበት ልዩ ጥበብ ቢኖር ያለ ምንም ጥርጥር የክብደቱን ልክና የዓይነቱን አበዛዝ ለመገመት የምንቸገር ይመስለናል::
ዘመናዊ ቴክኖሎጂው ተመራምሬ ደርሼበታለሁ ብሎ እንዳረጋገጠው ከሆነ ከሰው ልጆችም ሆነ ከእንስሳትና ከቁሳቁሶች የሚወጣው ድምጽ በአየር ላይ በኖ የሚጠፋ ሳይሆን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከደመና በላይ እየተንሳፈፈ እንደሚኖር ጥናቶች አስነብበዋል:: ስለ ግኝቱ በቂ እውቀት ያላቸው ዝርዝሩን ቢያሳውቁን እንማርበታለን::
የተንደረደርነው በክብር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል ሥራዎች ስለሆነ መደምደሚያችንን የምናደርገውም ከእርሳቸው የግጥም ሥራዎች መካከል ለማጠቃለያ የሚሆን ሃሳብ በመዋስ ይሆናል::
የታሪክን ጉዞ ያልተገነዘበ፣
ሁሉንም ያደንቃል እያጨበጨበ::
ለመጭው ሳያስብ ላላፊው ሳያዝን፣
በልማድ ይኖራል ጅል ሳያመዛዝን::
ብልኅ ያስተውላል አይደናበርም፣
መሄድ መመለሱን አይጠራጠርም::
ጊዜ እየለወጠው የልማድን አዋጅ፣
ጠላት የነበሩ ይሆናሉ ወዳጅ::
እንዲሁም ቢመስለን ግራ መስሎ ለእኛ፣
ፍየል ከነብር ጋር ይሆናል ጓደኛ::
ልበ ተላላ ሰው ዘላለም ይሞኛል፣
እስኪ ረግቶ ያለ ምን ነገር ይገኛል::
ማሳረጊያችን፡- ማርን አይጣፍጥም ብለን ሙግት እንግጠም ብንል እከሌ የሚባል ተከራካሪ አለሁ ብሎ ላይሞግተን ይችላል:: ምክንያቱም የማርን ጥፍጥና የሚመሰክረው ባህርይው እንጂ “ጉንጭ አልፋ” ክርክራችን አይደለም:: የሬትን መራርነት ክደን የማርን ተፈጥሮ በማላበስ እሶሶ እያልን እናዳንቅ ብንልም የምናገኘው ግብረ መልስ አበጃችሁ የሚሰኝ ሳይሆን “ወፍፈዋል” አሰኝቶ ከንፈር የሚያስመጥጥ ሊሆን ይችላል::
ለምን? ቢሉ ማርም ጣፋጭ፤ ሬትም መራራነቱ የታወቀ ነውና:: ስለዚህም በጎ በጎውን አገራዊ ስኬት እያደነቅን፣ የሚታረመው እንዲታረም እንበርታ እንጂ በትንሽ በትልቁ አገርን በእሾህ ጅራፍ እየገረፍን ማስለቀሱ ዞሮ ዞሮ ጦሱ የጋራ፣ መከራውም የጀማው በሙሉ እንደሚሆን ልንዘነጋ አይገባም:: ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ::
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ግንቦት 23/2015