ድህነትና ብልጽግና የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው፡፡ በየትኛውም አገር የቱንም ያህል ብልጽግና ቢኖር በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ድህነት መኖሩ አይቀሬ ነው፡፡ ይህ አደጉ በለጸጉ በሚባሉት ሃያላን አገራትም ያለ እወነታ ነው። ድህነት ደረጃው ቢለያይም ሌላው ቀርቶ የዜግነት በሚከፍሉ አገራትም ያለ እውነታ ነው። ነገር ግን እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ታዳጊ አገሮች የድሆች ቁጥር ብቻ ሳይሆን የድህነት መጠኑም ማለትም መሰረታዊ የሆኑት የምግብ፤ የልብስና የመጠለያ ችግሮች ጎልተው ይታያሉ።
በቀጥታ የአገራችንን ሁኔታ ስንመለከትም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየታየ ካለው የኑሮ ውድነት የድሆች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ አሁን ላይ ያለውን እጅግ ከፍተኛ የኑሮ ውድነት ጫንቃቸው መሸከም ያቃታቸው ዜጎች ለእርዳታ ጠባቂነት እየተዳረጉ መሆኑንም እየተመለከትን ይገኛል፡፡
የድሆች ቁጥር መበራካት ደግሞ በዜጎች ላይ ከሚያደርሰው የእለት ተእለት ተጽእኖ ባለፈ አገራችንንም ለተረጂነት የሚዳርግ መሆኑን በተግባር ስናየው ቆይተናል። በዓለም ላይ አለን ተረፈን ብለው የሚረዱት አገራት ደግሞ ከስንዴ እስከ ቁሳቁስ ድጋፍ ሲያደርጉ እንደሚያወሩት በልበ ንጹህነት ሳይሆን በርካታ ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጠው ነው።
እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎቸ ደግሞ በአንድም ይሁን በሌላ መልኩ የአገርን ሉአላዊነት የሚዳፈሩ የአገርና የህዝብን ጥቅም የሚነኩና እንደ ዜጋ አንገት የሚያስደፉም ናቸው። በመሆኑም ይህንን ለትውልድ የሚተላለፍ የስጋም የህሊናም እዳ ከመቀበል አስፈላጊውን መስዋእትነት ከፍሎ ከተረጂነት ለመላቀቅ ብሎም የራስን ችግር በራስ ለመፍታት መስራት ለነገ የማይባል የመንግስትም የህዝብም ቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል።
ደሃ ለመሆናችን የተለያዩ ምክንያቶችን መደርደር የሚቻል ቢሆንም በእኔ እይታ ቀዳሚዎቹ ሊሆኑ የሚችሉት ሁለት ነገሮች ብቻ ነው። የመጀመሪያው ጠንካራ ሰራተኛ አለመሆናችን ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የውስጥ ሰላማችንን በማስጠበቅ ረገድ የገጠሙን ተግዳሮቶች ናቸው።
ምንም እንኳን አንዳንዶቹ ጉዳዮች ውጤታቸውን ለማየት ዓመታትን የሚፈልጉ ቢሆንም ከቅርብ ግዜያት ወዲህ መንግስት በሁለቱም እንቅፋቶች ላይ ቁርጠኛ አቋም ለመውሰድ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ ተስፋ ሰጪ ጅምሮችን ለማየት በቅተናል። የመጀመሪያው ዘወትር የአውሮፓውያንና አሜሪካውያን ደጅ ጠኚ የሚያደርገንን በምግብ እህል ራስን ለመቻል የሚደረገው ትንቅንቅ ነው።
በዚህ ረገድ አርሶና አርብቶ አደሩ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች እንደተጠበቁ ሆነው በተለይም በስንዴ ምርት ላይ የታየውን አበረታች ለውጥ ለዚህ ጉዳይ መጥቀስ ይቻላል። በዚህ ረገድ ከመንግስት ከፍተኛ አመራሮች ጀምሮ እስከታችኛው ድረስ የተሰጠው ትኩረት አቅማችን ከአገራችን ፍላጎት አልፎ የውጪ ገበያውን ለመንካት የሚያስችል መሆኑን አይተናል።
ስራው ሲጀመር ግን « ስንዴ ለውጪ ገበያ ለማቅረብ» የምትለው እቅድ የብዙዎች መሳለቂያ ሆና ነበር። በአርግጥም ሲቀልዱ የነበሩት ሰዎችም እውነት ነበራቸው። እውነታው ደግሞ ኢትዮጵያ ስንዴ ሲሰፈርላት እንጂ ስትሰፍር ያለመኖሯ ሀቅ ብቻ ሳይሆን ይህንን ታሪክ በጦርነትና በተለያዩ ግጭቶች ውስጥ ሆና ለማሳካት ማቀዷም ነበር።
ግን በድፍረት ብቻ ሳይሆን አቅምንም ከግምት ባስገባ መልኩ ስራው ትኩረት ተሰጥቶት በመሰራቱ የታሰበውን ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል። ይህም ሆኖ ግን እነዚህ ለውጦች ቀጣይነት ኖሯቸው የሚፈለገው ግብ ላይ ለመድረስ በአንድ ዓመት የምርት ብዛት ወይንም የአርሶ አደር ተሳትፎ ብቻ አይወሰንም። በመሆኑም መንግስት በልዩ ትኩረት ያቀመሰንን ድል ለማስቀጠል ሁላችንም ከጎን በመሆን የሚጠበቅብንን ልንወጣ ይገባል።
በተጨማሪ አሁን ላይ በአገራችን ይሄን ከውጭ ድጋፍ ነፃ የመሆን ጥረታችንን እያጠናከሩ ያሉ ብዙ እንቅስቃሴዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እንደ አገርም በተለይ በመዲናችን አዲስ አበባ ከከተማዋ አልፎ ኢትዮጵያችን ወደ ብልጽግና ማማ ላይ እየወጣች ለመሆኑ የሚያመላክቱ ብዙ እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡
ለአብነት በከተማችን በከፍተኛ በጀት እየተገነቡ የሚገኙ ሜጋ ፕሮጀክቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እነዚህ ሕዝቧም አገሪቷም ወደ ብልጽግና እየገሰገሱ መሆናቸውን የሚያሳዩ ናቸው፡፡ የህዳሴው ግድብ ኃይል ማመንጨትን ጨምሮ በመንግስት እየተሰሩ ያሉ ስራዎች ለውጦች በዘመኑ የተደረሰበትን ብልጽግና አመላካች አሻራ ከመሆን አልፈው ከውጭ ድጋፍ ነፃ የመሆን ብርቱ አገራዊ ጥረታችንንም ሆነ የጋራ ትጋታችንን የሚያሳዩ ናቸው፡፡
ሌላው ለድህነታችንና ለተረጂነት እየዳረገን ያለው ባለፉት ዓመታት ተፈጥሮ የነበረው ግጭት ነው። ለችግሩ መፈጠር መነሻ ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን ወደ ግጭት እንዲያመራ የዳደረገው ግን በሰለጠነ መንገድ የሀሳብ ልዩነቶችን በውይይት ለመፍታት የነበረን ጥረት የተቀዛቀዘ መሆን ነው። ችግሮቻችንን በራሳችን አቅም ነገሮች ከመባባሳቸው በፊት መቆጣጠር ባለመቻላችን እንደ አገር ብዙ አስከፍሎናል።
ይህ ክስተት ዛሬም ትኩሳቱ ያለቀቀ የቅርብ ግዜ ጠባሳችንም ትዝታችንም ነው። የችግሩ መከሰት ደግሞ ምንም እንኳን መንግስት ረጅም ርቀት በመጓዝ ነገሮችን መቆጣጠር የቻለ ቢሆንም፤ እኛን ከጎዳን ባልተናነሰ በከፍተኛ ደረጃ ለውጪ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት በር የከፈተም ነበር።
በወቅቱ እርዳታ እናደርጋለን ብለው የመጡ አካላት የአገር ሉአላዊነትን የሚገዳደሩ ጥያቄዎችንም አቅርበው ነበር። አንዳንዶቹ እኛ ያልናችሁን ካላደረጋችሁ እንደ አገር የመቀጠል እድላችሁም የተመናመነ ነው ሲሉ ተደምጠዋል። የሚገርመው ይህንን ሀሳብ በመደገፍ መንግስት የአገርን ሉአላዊነት ለሚገዳደረው ለረጂዎች ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ እንዲሰጥ የፈለጉም ኢትዮጵያውያንም ነበሩ።
በተመሳሳይ በዚህ አሳሳቢ ወቅትም መንግስት ነገሮችን በሆደ ሰፊነት በመያዝ የራሳችንን ችግር በራሳችን ለመፍታት የሄደበት ርቀት ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካውያን አስተማሪም ሆኗል። የሰላሙ መስፈን ደግሞ ቢያንስ በሰው ሰራሽ ምክንያቶች ለተለያዩ ችግሮች እየተጋለጡ ለምጽዋት እጃቸውን ለሚዘረጉ ወገኖቻችን እረፍት የሚሰጥ ነው። ከሁሉም በላይ ደግሞ ምን አልባትም ድጋፍ አድራጊ አገራትና ተቋማት ከእርዳታ ጀርባ ስለሚያቀርቡት ጥያቄ ደግመው ደጋግመው እንዲያስቡ የሚያደርግም ይሆናል።
ወደድንም ጠላንም፤ አመንም አላመንም ብልጽግናችን ይሄንኑ ከውጭ እርዳታ ነፃ የመሆን ጽኑ ፍላጎታችንን የሚያመላክት የትጋታችን ደማቅ አሻራ ነው፡፡ የእስከ አሁኑን የእርዳታ ጠባቂነት ወይም የተረጅነት ዘመን ታሪካችንንም ይቀይርልናል ተብሎ ይታመናል፡፡ የእርዳታ ታሪካችንን መቀየር ብቻ ሳይሆን ረጅዎቹ ለእኛ ያላቸውን አመለካከትም እንደሚያስተካክለው መገመት አያዳግትም፡፡
በእርዳታ ሰበብ እጃችሁን ጠምዝዤ የፈለኩትን አደርጋለሁ፤ በአገራችሁ የውስጥ ጉዳይ ገብቼ እፈተፍታለሁ ማለት በእኛ በኩል ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ለዚህ ደግሞ በልማቱም በሰላሙም የተጀመሩ አበረታች ስራዎች አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደ ዜጋ የሚፈለግብንን መወጣት ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ይሆናል።
ሰላማዊት ውቤ
አዲስ ዘመን ግንቦት 23/2015