በየትኛውም ማህበረሰብ ውስጥ “አገር ማለት ሰው ነው” የሚል የቆየና የሚቆይ እውነት አለ። ይህ እውነት በብዙ ነገር የተለያየችውን ዓለም አንድ የሚያደርግ የጋራ እውነት ነው። አገር ማለት ሰው ከሆነ የአገር ልዕልና በሰውነት በኩል የሚመጣ ስለመሆኑ መተማመን ላይ ያደርሰናል።
ስለለውጥና ስኬት የሚያጠኑ ዓለም አቀፍ ባለሙያዎች አገራዊ ለውጥ በግለሰባዊ ለውጥ ውስጥ እንዳለ ይናገራሉ። ይሄን እውነት ተመርኩዞ ዓለም አቀፉ የኢኮኖሚስቶች ማህበር ደግሞ የአገርን ለውጥ ከግለሰብ ለውጥ ጋር፣ የትውልድን ለውጥ ደግሞ ከአገር ለውጥ ጋር ያቆራኘዋል። ከእኛ በቀር ሁሉም የዓለም ህዝብ ይህን እውነት ያውቃል።
ወደ እኛ አገር ስንመጣ የለውጥ መሰረት ምን እንደሆነ ገና የገባን አይመስለኝም። ምክንያቱም ከትላንት እስከዛሬ የተራመድንባቸው ጎዳናዎች የለውጥን ህግ የሳቱ መሆናቸው ነው። ዛሬም ድረስ እያደረግነው ያለው ነገር ከለውጥ ህግ ጋር የሚቃረን ነው።
ራሳችንን ሳንቀይር አገር ለመቀየር የቆምን ብዙዎች ነን። በአንድ ሀሳብ ሳንስማማ አገር ለመቀየር የፖለቲካ ፓርቲ አቋቁመን የምረጡኝ ቅስቀሳ የምናደርግ ብዙ ነን። ተነጋግረን ሳንግባባ ደጋፊና ተከታይ አቋቁመን የነገዋ ኢትዮጵያ ተስፋ ስንል ለራሳችን የማይገባ ስም ሰጥተን የምንቀሳቀስ ሞልተናል።
ይህን እኮ ነው የለውጥ ህግ አልገባንም ስል የተነሳሁት። ለውጥ ራስን ከመቀየር፣ አስተሳሰብን ከማዘመን የሚነሳ ነው። እድገትና ስልጣኔ ከእኔ ወደ ሌላው፣ ከሌላው ወደ ሌላው ከዛም ማህበረሰብ ላይ የሚያርፍ ነው። ያን የማህበረሰብ ለውጥ ነው የአገር ለውጥ ብለን የምናወራው።
ራስን መቀየር ስንል አስተሳሰብን፣ ልማድን፣ የኑሮ ዘይቤን በምክንያት በተደገፈ እውቀት መቀየር ማለት ነው። ራስን መቀየር ማለት ተነጋግሮ ለመግባባት፣ ተግባብቶ በአንድ ለመቆም ራስን ማዘጋጀት ማለት ነው። ራስን መቀየር ማለት ከራስ በፊት ለአገርና ህዝብ የሚያስብ ሰውነትን መፍጠር ማለት ነው። እኛ ደግሞ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እነዚህን እውነታዎች ሊያሳቱን በሚያስችሉ ተግዳሮቶች ውስጥ ነን። ዘረኝነትና ራስ ወዳድነት እየተፈታተኑን ነው። ይህንንም ፈታና ለመሻገር እና ቀና ብሎ ለመሄድ ሀሳብና እውቀት ያስፈልገናል።
የእውቀታችንን መጀመሪያ ኢትዮጵያ ስናደርግና ብሄርተኝነትን ስናደርግ አንድ አይደለም። እውቀታቸውን አገር ከሚሏት እውነት የጀመሩ እነሱ በኋለኝነት ተጠርተው አያውቁም። ሁሌም ከፊት ሁሌም በኃይል ውስጥ ናቸው። አባቶቻችን ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው።
አባቶቻችን እውቀታቸውን አፍስሰው፣ ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍለው ነጮች ያልቻሏትን አገር ፈጥረዋል። ዛሬም ድረስ በፊተኛነት የምንጠራው እነሱ አፋቸውን በፈቱበት ቀዳማይ ስም፣ ኢትዮጵያ ነው። እኛም በዚህ ስም አፋችንን ፈተን የወደ ፊት እጣ ፈንታችንን የምንወስንበት ጊዜ ላይ ነን።
በጋራ ሀሳብ ኢትዮጵያዊነትን አስቀድመን እጣፈንታችን እስካልወሰንን ድረስ ከዛሬ የተሻለ ነገ ላይ መድረስ አንችልም። የዓለም መልክ የተበላሸው በብሄርተኞች ጽንፍ የረገጠ እሳቤ ነው። ማማር ካለብን፣ ወደ ፊት መራመድ ካሻን ኢትዮጵያዊነትን እናስቀድም። ይሄ እንደ አገር ለመቀጠል ብቸኛው አማራጫችን ነው።
ሁሉም ነገር መጀመሪያ አለው። መጀመሪያችን ከአገር እንዲጀምር ኢትዮጵያዊነትን ያደበዘዙ የብሄር እሳቤዎች፣ የእኔነት እውቀቶች መጽዳት አለባቸው። ብሄርተኛነት ኢትዮጵያዊነትን የሚያደበዝዝ፣ ኢትዮጵያዊነት ግን ብሄርተኛነትን የሚያደምቅ ኃይል አለው። መጀመሪያችን አገር ከሆነ በብሄር ለመድመቅ ይቻለናል። መጀመሪያችን ብሄር ከሆነ ግን በኢትዮጵያዊነት መድመቅ አንችልም።
ሰማኒያና ከዛ በላይ ብሄር ብሄረሰቦች ተብለን የምንጠራው፣ በታሪክ፣ በባህል፣ በወግና በስርዐት ቀዳማይ የተባልነው ኢትዮጵያ ስለቀደመች ነው። ሁሌ ህዳር በመጣ ቁጥር የብሄረሰብ ቀን የምናከብረው ህብረብሄራዊነትን በሰጠን ኢትዮጵያዊነት ነው። ዘረኛነት ይህን የሚያጠይም በሽታ ነው።
የአገር ለውጥ የእኔና የእናንተ ለውጥ ነው። ህልም ባለው ፖለቲካና ፖለቲከኛ የሚፈጠር ነው። ለአገር በሚያስቡ በጎ ልቦች፣ በጎ አእምሮዎች የሚያብብ ነው። ትላንትናዎቻችን ብዙ ትኩሳቶችን ወልደውብናል። ዛሬም በእነዛ ትኩሳቶች የምንሰቃይ ነን። ለውጥ ማለት ለእነዛ ትኩሳቶች መድሃኒት መፈለግ አሊያም ደግሞ በአዲስ መንፈስ ወደ ፊት መሄድ ማለት ነው።
የጥቁሮች መብት ተሟጋቹ ኪንግ ማርቲን ሉተር ለአብዮት ሲነሳ “አይ ሀቭ ኤ ድሪም!!!” (ህልም አለኝ!!!) ብሎ ነው። በዚህ ፍልስፍና ውስጥ ጸንቶ በመቆም ነው ለመላው ጥቁር ህዝብ ድምጽ መሆን የቻለው። እኛም ህልማችን አገር መለወጥ ከሆነ እንደ ማርቲን ሉተር “ህልም አለኝ!!!” ብለን መነሳት ይኖርብናል።
ህልም በሌለው የፖለቲካ ሽኩቻ ውስጥ አገር ለመለወጥ መነሳታችን ነው ጥፋት እያደረሰ ያለው። ራሳችንን ምርጥ ለማድረግ እንጂ አገር ምርጥ ለማድረግ ስንወዳደር አንታይም። የትም፣ መቼም ከአገራችን በፊት የእኛ ስም እንዲነሳ የምንፈልግ ነን። እነዚህ ልማዶች ህልም በሌለው ፖለቲካ ውስጥ የተለማመድናቸው ልማዶች ናቸው።
እንደ አገር ብሄራዊ ምክክር ብለን የተነሳነው ህልም ባለው ንግግር ህልም ያለው ትውልድ ለመፍጠር ነው። እንደ አገር ብሄራዊ ተግባቦት ብለን የተነሳነው ህልም ባለው ፖለቲካ ህልም ያላትን አገር ለመፍጠር ነው። ሰላሟን በጦርነት ውስጥ የምትፈልግ አገር ህልም የላትም። ጀግንነቱን በኃይል የዋጀ ፖለቲከኛ ለአገር የሚሆን የሰላም ሀሳብ አይኖረውም።
ከምክክሩ ጎን ለጎን የሽግግር ፍትህ እሳቤን ተግባራዊ ልናደርግ ዝግጅት ላይ ነን። ይህ እሳቤ ህልመ-ቢሶችን ከህልመኞች የምንለይበት ሂደት ነው። ወደ ትክክለኛው አገር የመፍጠር እሳቤ ለመድረስ ህልም አልባ በሆነ አስተሳሰብ ኢትዮጵያን የጎዱና ያስጎዱ የሚቀጡበት የፍትህ ስርአት ያስፈልገናል። ትላንታችን በጎሸና ለማንም ባልበጀ የፉክክር መንፈስ ውስጥ ኢትዮጵያን በዘርና በብሄር የከፋፈለ ነበር። ይሄ አስተሳሰብ ዛሬ ላይ ፊተኛነትን በሰላም ሳይሆን በጦርነት፣ በመነጋገር ሳይሆን በኃይል እንድናምን አድርጎናል።
ህልም ያለው ፖለቲከኛ የብሄሩን ሰንደቅ ከፍ ለማድረግ ሳይሆን የአገሩን ሰንደቅ ከፍ ለማድረግ የሚለፋ ነው። በጋራ ህልም በጋራ እስካልተራመድን ድረስ የአንድነታችንን ሰንደቅ ላይ አንደርስበትም። ሁላችንም የየራሳችንን የብሄር ሰንደቅ ከፍ አድርገን ለብቻ በመጓዝ ኢትዮጵያዊነትን ከማደብዘዝ ባለፈ ትርጉም አይኖረንም።
አገራችን የሚያስፈልጋት ህልም ያለው ፖለቲካና ፖለቲከኞች ነው። ምንም ከሌላት አገራችን ላይ የየድርሻችንን ለማንሳት ከመሞከራችን በፊት ምንም ለሌላት አገራችን የየድርሻችንን ልናደርግላት መጣር ነው ጀግና የሚያስብለን። እስካሁን ባለው ታሪካችንን በየትኛውም አቅጣጫ ብናየው አገራችንን በየዘመኑ ፈተና ውስጥ እየከተትናት ያለነው እኛው ነን።
የሚረባ ታሪክ፣ የሚረባ ትውልድ፣ የሚረባ ተፈጥሮ፣ የሚረባ ማንነት ይዘን በብሄር እሳቤ ተመርዘን ለራሳችን እንዳንሆን ያሰጋል። የተለጠጠ የብሄር እሳቤ የሰውን ልጅ ኃይሉንና ሚዛናዊነቱን ነጥቆ ሰብአዊ ዋጋውን የሚያሳንስ በሽታ ነው ።
በፍልስፍናው ዓለም “ሰው አሳቢ እንስሳ ነው” የሚል እውቀት አለ። ይህ እውቀት መልኩን ቀይሮ ከማሰብ ወደ አለማሰብ፤ ከማገናዘብ ወደ አለማገናዘብ፤ ከሰውነት ወደ አውሬት የሚሸጋገረው ጽንፍ በረገጠ የብሄር እሳቤ ሲወሰድ ነው ።
ወደ ፊት የሚወስድ፣ በአንድነት የሚያቆም የጋራ ህልም ያስፈልገናል። ከጦርነት የሚያወጣ፣ በወንድማማችነት የሚያቆም የመከባበር እውቀት አዲሱ ማንነታችን ሆኖ ወደ ፖለቲካችንና ፖለቲከኞቻችን እስካልመጣ ድረስ አዲስ ነገን አናይም። እንዲህ ሲሆን ብቻ ነው በታደሰ ማንነት ውስጥ አገራችንን ተስፈኛ ልናደርጋት የምንችለው።
ግለሰብ ሳይሰለጥን አገር አትሰለጥንም። መጀመሪያ እኛ እንለወጥ። መጀመሪያ አስተሳሰባችንን እንግራ። በእውቀት፣ በአንድነት መንፈስ መተባበርን ልማድ እናድርግ። ከዚህ እውነት ቀጥሎ ነው የአገር ለውጥ የሚመጣው። ራሳችንን በጥላቻ፣ በመለያየት እያኖርን ብልጽግና መጠበቅ ሞኝነት ነው። ራሳችንን ከአንድነት፣ ከወንድማማችነት አርቀን ስልጡን አገርና ህዝብ መጠበቅ የማይታሰብ ነው።
ግለሰባዊ ለውጥ የለውጥ ሁሉ መሰረት ነው። ሰው ራሱን ካልለወጠ አገሩን መቀየር አይችልም። አገር የግለሰቦች አስተሳሰብ ናት። አገር በግለሰቦች ሀሳብና ድርጊት የተሰፋች ናት። ራሳችንን እናድስ። አሁን ላይ አገራችን የሚያስፈልጋት የታደሰ ማንነት ነው።
ባልታደሰ ማንነት በአዲስ ዛሬ ላይ ተመሳሳይ ስህተቶችን ስንሰራ ኖረናል። ራስን ማደስ በእውቀትና በምክንያታዊነት መቆም ነው። ራስን ማደስ ከሁሉ የሚበልጥን እውነት መከተል ነው። እየሄድንበት ያለነውን ጎዳና ቆም ብሎ ማየት ነው።
ከዚህ እውነት በመነሳት ከሁሉም የሚበልጠው እውነታችን አንድነታችን ነው። ሌላው የልዕልና ጌጥ በአንድነታችን በኩል የምናገኘው ነው። አብዛኞቹ ችግሮቻችን እኛው የፈጠርናቸው ናቸው። ችግሮቻችንን በገዛ እጃችን ስንፈጥር ለፈጠርናቸው ችግሮች የሚሆን መፍትሄ ግን የለንም።
ለተፈጠሩ ችግሮች የመፍትሄ ሀሳብ ማምጣት እንደአገር ጥሩ መገለጫችን ነው የሚሆነው። ከየትኛውም ቃል በላይ ይህ እውነት ይገልጸናል ብዬ አምናለሁ። ችግር እየፈጠርን የሰላምና የእርቅ ሀሳብ ማምጣት ማለት አገራችንን ከፊት አላስቀደምናትም ማለት ነው። እንዲህ አይነት አገራዊ ቀውስ የሚፈጠረው ራስ ወዳድነትን ከፊት ባደረገ አእምሮና ልብ ነው።
አገር ታማኝና ለለውጥ የበረታ ዜጋ ከሌላት ዋጋ የላትም። አገር ለእርቅ ልቡን፣ ለድርድር በሩን የከፈተ መንግስትና ህዝብ ከሌላት ተስፋ የላትም። በአንድ አገር ላይ ሁሉም እድሎች፣ ሁሉም ስኬቶች በግለሰብ ለውጥ የተፈጠሩ ናቸው። አገራችንን ለተሻለ ነገር የምናበቃት እኛ ነን። ህይወት የምትሰምረው ዝም ብሎ በመኖር ሳይሆን እንዴት መኖር እንዳለብን ስንረዳ ነው።
በዚህ መረዳት ውስጥ ነው አሸናፊነት የሚኖረው። በዚህ መረዳት ውስጥ ነው አንደኝነት የሚፈጠረው። በዚህ መረዳት ውስጥ ነው ሙሴን ሆነን አገራችንን የምናሻግረው። እንደ ዜጋ በህይወት ሩጫ ውስጥ አሸናፊ ሆኖ ለመገኘት ባለ ራዕይ መሆን ያስፈልጋል። እንደ አገር የተሻለ ኢኮኖሚን ለመገንባት ደግሞ ከትላንት የተሻለ፣ ዘመኑን የዋጀ አስተሳሰብ ግድ ይለናል።
አሸናፊ ለመሆን ከፍላጎት በላይ ጽናት ያስፈልጋል። ነገሮችን በተለየ መልኩ ማየት ግድ ይላል። ብዙዎቻችን አንደኝነትን የምንፈልግ ነን፤ አንደኛ ለመሆን ግን ስንሮጥ አንታይም። ብዙዎቻችን አገራችንን ለመለወጥ የምንፈልግ ነን፤ ግን በአገር ጉዳይ ላይ ስንግባባና አንድ ስንሆን አንታይም።
ለምንም ነገር ራስን ማደስ ያስፈልጋል። በምንፈልገው፣ በማንኛውም ነገር ላይ ለውጥ ለማምጣት ለውጥ በሚያመጣ ሀሳብ ራሳችንን መክበብ ያስፈልገናል። የማያግባቡንን በእርቅ እየፈታን በሚያግባቡን ነገሮች ላይ አንድ ብንሆን ዛሬ አገራችን ከኢኮኖሚ ባለፈ በሌሎች ዘርፎች ላይም የበላይነቷን ባሳየች ነበር። ግን እኛ ስላልተለወጥን አገራችን አልተለወጠችም። ግን ተነጋግረን ስላልተግባባን ተነጋግሮ የሚግባባ ትውልድ አላፈራንም።
ካንቀላፋንበት እንንቃ። ዓለም ርቆን እየሄደ ነው። ራሳችንን እያደስን ወደ ፊት መሄድን እንማር። ራስን ማደስ ለአዲስ ህይወት አዲስ ምዕራፍ ነው። ራስን ማደስ ለምንም ነገር ሌላ እርምጃ ነው። እንደ ትላንት መኖር ይብቃን። እርቅና ይቅርባይነት በሌለው ህይወት ውስጥ መኖር ይብቃን። ራስን ማደስ ራስን ከትላንት መለየት ነው። ከስህተትና ከውድቀታችን እየተማርን ለአዲስና ለሌላ ድል መዘጋጀት ነው። ባልታደሰ እና ባልተለወጠ ጭንቅላት ውስጥ ለውጥ የለም። ለውጣችን ያለው በመታደሳችን ውስጥ ነው።
ትውልድ ንቃ። መንግስት እወቅ። የዓለም ስልጣኔ የአንድነት ስልጣኔ ነው። የዓለም ስልጣኔ ራስን የመለወጥ ስልጣኔ ነው። እኛ ግን ዛሬም ድረስ አምና እና ካቻምና ውስጥ ነን። እንደ አገርም እንደ ህዝብም ከትላንትነት ውስጥ አልወጣንም። ለአንደኛነት ባላበቃን ትላንት ውስጥ ምን እናደርጋለን? ሰላምና ፍቅርን ባልሰጠን ድሮ ውስጥ ምን እንሰራለን? ለውጥ . . . ለውጥ . . . ከራስ የሚጀምር ለውጥ!!!
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ግንቦት 22/2015