ዛሬ ላይ ዓለማችን ዘርፈ ብዙ ችግሮች እየፈተኗት ትገኛለች። አገራችንም የዚህ ችግር ሰለባ ከመሆን የወጣች አይደለችም። በመሆኑም አገራት ከችግሮቻቸው ልቀው ለመገኘት በጥናትና ምርምር ላይ የተደገፉ ችግር ፈቺ የፈጠራና ቴክኖሎጂ ውጤቶችን እንደየአገራቸው ተጨባጭ ሁኔታ በማፍለቅና በመጠቀም ላይ ይገኛሉ።
ኢትዮጵያም ያሉባትን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሌሎችም ዘርፈ ብዙ ችግሮች ከመሻገር አኳያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለጥናትና ምርምር በተለይም ለሳይንሳዊ ፈጠራዎች ትኩረት እየሰጠች ትገኛለች። ለአብነትም በግብርናው፣ በጤናው፣ በአካባቢ ጥበቃና ሌሎችም መስኮች የሚታዩ ችግሮችን ሊፈቱ የሚችሉ የፈጠራ ስራዎች እንዲወጡ እና እንዲደገፉ እየተደረገ ያለውን ስራ መመልከት ይቻላል። ከሰሞኑም በመካሄድ ላይ ባለው “ከቤተ ሙከራ ወደ አዝመራ” በሚል መሪ ሀሳብ በግብርናው ዘርፍ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን የሚያመላክተው አውደ ርዕይም ይሄንን የሚያጠናክሩ የፈጠራና የምርምር ውጤቶችን ያሳየ ሆኗል።
በችግር የደነደነ ትክሻ የሚሰበረው በምርምርና ፈጠራ ነው። ያደጉ የዓለማችን አገራት ለዚህ እድገታቸው የበቁት በእያንዳንዱ ዘርፍ የሚታየውን ጉድለት የሚሞላ የፈጠራ ስራ ስርተው በመፍታታቸውና የችግሩን ስር ነቅለው በመጣላቸው ነው። ለዚህም እኛም አገር የምርምርና ፈጠራ ውጤቶችን ይዞ ወደችግሮቻችን በመቅረብ “ችግር ሆይ ደህና ሁን” የሚል መርዶን ማድረስ ይገባል።
መርዶ ሲባል ችግርን ከዚህ በኋላ በዚህ ሥፍራ ቦታ የለህም የሚያስብል ስራን መስራት ማለት ነው። ምክንያቱም፣ እኛ ሰዎች የመጨረሻው የስንብት መርዷችን ሞት እንደሆነው ሁሉ፤ ለችግርም መርዶው በጥናትና ምርምር የታገዘ ፈጠራ ሊሆን ይገባል ብዬ አምናለሁ።
ችግር ሲነሳ በሰው ልጅ ህይወት የሚያደርሰውን ሰቆቃ ብቻ ማየት ሚዛናዊነት አይደለም። በዓለም ላይ የምናያቸው ድንቅ፣ የማይታሰቡና የማይደረስባቸው የሚመስሉ ከጥቃቅን እስከ ትላልቅ የፈጠራ ስራዎች እንዲወለዱ፣ እንዲያድጉና እንዲሞቱ ያደረገ ትልቅ ሀብት መሆኑም መዘንጋትም የለበትም።
እስከ ቅርብ ግዜ አገራችን በየዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታት ለፈጠራ ስራ ያላት ድጋፍና ትኩረት እዚህ ግባ የሚባል ባይሆንም፤ በአሁኑ ወቅት ግን ችግርን ነቅሰው የሚያዩና ለመፍታት የሚታትሩ ብሩህ የአእምሮ ባለቤቶች ያሏት ስለመሆኑ የሚያመላክቱ የተስፋ ስንቆች ብቅ ብቅ ማለት ጀምረዋል።
ከሰሞኑም በተለየ የኪነ- ህንፃ ጥበብ በተሰራውና በማራኪው የሳይንስ ሙዚያም ውስጥ እነዚህ ለመቁጠር የሚያታክቱ፣ ሲታዩ የሚደንቁ፣ የማይቻል የሚመስሉ ግን የተቻሉ የፈጠራ ስራዎች ለእይታ በቅተዋል።
በዚህ የሳይንስ ሙዚየም የነገ የአገር ተስፋ ፈንጣቂ የፈጠራ ባለአዕምሮዎች ስራዎቻቸውን ለጎብኝዎች ሲያብራሩ ሲታዩ የአገራችን ዘርፈ ብዙ ችግር በአገር በቀል ሳይንሳዊ እሳቤ ባለቤቶች መፍትሄ ያገኛል የሚለውን ተስፋ ከፍ ያደርጋል።
ጅምራቸው ተስፋ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር በለጋ እድሜያቸው የነቁ የአእምሮ ባለቤት ታዳጊዎች፤ ህልማቸውና ፈጠራቸው ለፍሬ ሳይበቃ እንዳይቀር ምን ያስፈልጋቸዋል? ምንስ መደረግ አለበት? በሳይንስ ሙዚየሙ የሚንኮራኮሩ አውሮፕላኖች፣ የሚንተፋተፉ ማሽኖች በተግባር ሰማዩን ሲሰነጥቁት፣ መሬቱን ሲያርዱት የሚታዩትስ መቼ ይሆን? የሚሉ ስጋት አዘል ጥያቄዎችና ምኞቶች ከግንዛቤ ሊገቡ ያስፈልጋል።
ተስፋውንም ስጋቱንም ለማሳየት የሚያግዘኝን ጥቂት ማስረጃዎች ላቅርብ። የ11ኛ ክፍል ተማሪዋ ሶሊያና አበራ፣ በአገራችን በግብርናው ዘርፍ የሚታየውን በባህላዊ መንገድ እህል ሲዘራ የሚገጥመንን ችግር የሚፈታና የአርሶ አደሩን ጉልበትና ጊዜ የሚቆጥብ ‹‹ሲድ ሶር›› የሚባል ማሽን የፈጠረች እንቁ ታዳጊ ናት።
ተማሪ ሶሊያና ከጨረቃ ድምቀት በላቀ፣ ፈገግታ የፈጠራ ስራዋን ከስያሜና ትርጓሚው በመነሳት ለጎብኝዎች ስታብራራ ሁሉም ግርምት በሚጭር ስሜት ነበር የሚያያት። ‹‹ሲድ ሶር›› ማለት ዘር የሚዘራ ማሽን ማለት ነዉ›› ስትል የበሰለ የፈጠራ አእምሮ ባለቤት መሆኗ ያሳብቅባታል።
የአገራችን አርሶ አደሮች የተለያዩ አዝእርቶችን በእጃቸው ስለሚዘሩ አንዳንድ ቦታ የመብዛት፣ የመሳሳትና ያለመዳረስ ሁኔታ አለ። ይህም ዘሮቹ በአንድ ቦታ በርከት ብለዉ ሲወድቁ የአፈሩን ንጥረ ነገር ይሻማሉ። በዚህም ሰብሎች በመቀጨጭና በመጥፋታቸው አመርቂ ምርት አይገኝም። በዓለም ደረጃም የሚኖራቸዉ ተወዳዳሪነት ዝቅተኛ ይሆናል። ይሄን በመገንዘቧም በሳይንሳዊ መንገድ ችግሩን ለመፍታትና ዘሮችን በእኩል መጠን ለመዝራት የሚያገለግል ማሽን መፍጠሯን ታስረዳለች።
ማሽኑ የተለያዩ ዘሮችን የሚበትኑ ወንፊቶች አሉት፤ ወንፊቶች መኖራቸው አርሶ አደሮች ዘር በሚዘሩበት ወቅት እየቀያየሩ (ለምሳሌ፣ ጤፍ ሲዘሩ የጤፍ ወንፊት፣ ስንዴ ሲዘሩ የስንዴ ወንፊት) መጠቀም የሚያስችል ነው።
‹‹ሲድ ሶር›› ተግባሩ ዘር መዝራት ብቻም አይደለም፤ ዘር ከዘራ በኋላ ዘሩን አፈር በማልበስና ዉሃ በማጠጣት የአርሶ አደሩን ፈርጀ ብዙ ችግር ይቀርፋል። በርካታ ሰብሎች ወድቀዉ የአፈሩን ንጥረ ነገር የሚሻሙበት ሁኔታ እንዳይፈጠር በማድረግ ምርትና ምርታማነትን ያሳድጋል።
እድሉን ያገኙ አርሶ አደሮችም የእጅ ስልካቸውን ማሽኑ ላይ ካለው የመቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂ ጋር በማገናኘት አንድ ቦታ ላይ ሆነው አዝርት እንዲዘራ፣ አፈር እንዲያለብስ ማዘዝ መቻላቸው ድካማቸውን ይቀንሳል። ከተለያዩ ነገሮች ጋር እንዳይጋጭ የሚቆጣጥር ማሽን ስለተገጠመለትም ያለምንም ስጋት መጠቀም እንዲቻል ተደርጎ የተሰራ ነው።
ሌላው የቡድን የፈጠራ ሥራን ይዞ የቀረበው ተማሪ እዮሲያስ ሰለሞን፣ ‹‹ካርበን ካፕቸሪንግ ማሽን›› የተባለ ካርበን ወደ ኦዞን እንዳይሄድ በማድረግ የአየር ንብረት እንዳይዛባ የሚያደርግና እየጨመረ የመጣውን ሙቀት እንዲቀንስ የሚያደርግ ማሽን መስራታቸውን ይናገራል።
ማሽኑ ላይ ካርበንን የሚይዝ እና ሴንስ ሚያደርግ መሳሪያ የተገጠመለት ሲሆን፤ ይህም የተገጠመለትና የካርበን ልቀትን ደረጃ አመላካች ያለው፤ ልቀቱ ከፍ ሲልም ካርቦንዳይ ኦክሳይድን አብዞርብ ማድረግ የሚችልም ነው። በዚህም ከተለያዩ ፋብሪካዎች፣ መኪናዎች የሚለቀቀዉን ካርበን በመቆጣጠር ካርበን ኦዞን ደርሶ የአየር ብክለት እንዳያደርስ የሚቆጣጠር የወቅቱን የዓለም ችግር የዋጀ ነው።
ዓለም ያደገችው ችግር በወለደው የፈጠራ ስራ መሆኑ የማይዘነጋ ነው። እንደ አገርም የማይፈታ የሚመስል ችግር እንደ ሀምሌ ጉም የተጋረደብን ቢመስለንም፤ ይሄንን ችግር ሊያሻግር የሚችል ባለ ብሩህ አእምሮና ለመፍትሄ የሚጥሩ ወጣቶች እንደ ፀሐይ ጮራ እየፈነጠቁ ነው።
ሆኖም እነዚህ የተስፋ ፍንጣቂዎች እንዳይደበዝዙ፣ እንደ ጤዛ ታይተው እንዳይጠፉ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ ተገቢ ነው። እነዚህ ባለ አእምሮዎች ችግርን በፈጠራ ስራ ልፈታህ ነው ሲሉት መርዶው ስለሆነ ፈተናዎች አያጧቸውም። እናም የፈጠራ ስራን መስክ ማበልፀግና ማሳደግ ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ ሊሆን ይገባል። የፈጠራ ስራ በመስራት ችግርን ለመፍታት፣ ሸክምን ለማቃለል፣ የሚታትሩ እንቁ አእምሮችን ያብዛልን እያልን ተሰናበትናችሁ። ሰላም!
ዓመለወርቅ ከበደ
አዲስ ዘመን ግንቦት 22/2015