ሀገራችን አዲስ ትውልድ የሚመላለስበት አዲስ መንገድ ያስፈልጋታል:: ከአሮጌው አርቆ ወደ አዲሱ የሚወስድ ዘመን የዋጀው የጋራ ዳና ግድ ይላታል:: አዲስ መንገድ በአዲስ ሀሳብ የሚቀደድ፣ በሰላም ስም የሚጸና ግፊያ የሌለበት የወንድማማችነት ሰርጥ ነው::
አለም በሁለት ጥንድ አስተሳሰብ ስር የወደቀች ናት፤ ሀገር በአንድ አይነት ሀሳብ ብቻ የሚገነባ በሚመስላቸው ጽንፈኞች እና የተለያዩ ሀሳቦችን ወደ አንድ በማምጣት ሀገር መገንባት የሚቻል በሚመስላቸው ባለራዕይ ሰዎች:: ሀገር ለማቆም የሚተጉ ልቦች በአስታራቂ እውነት እንደምትገነባ የሚያምኑ ሲሆን በተቃራኒው እንደ እኛ አይነት ከመግባባት ይልቅ በተቃርኖ ሀሳብ ጦር መማዘዝን ባህል ያደረጉ ሀገራት ለምንም ነገር አንድ አይነትነትን የሚያስቀድሙ ሆነው እናገኛቸዋለን::
አለም አንድ አይነት የሆነ ምንም ነገር የላትም:: ከትናንት እስከዛሬ በመለያየትና በተቃርኖ ነገር ግን በአስታራቂ ሀሳብ የቆመች ናት:: ለምንም ነገር አንድ አይነት መሆንን የሚመርጡ ግለሰቦች ገና የዘመናዊውን አለም ሰፊ ምህዳር ያልተረዱ፣ ልዩነትን እንደ መለያ አድርገው የተቀበሉ በአሮጌ እሳቤ የተጠፈነጉ ናቸው ብዬ በግልጽ መናገር እችላለሁ::
በእንዲህ አይነት አስተሳሰብ ስር የወደቁ ሀገራት አይደለም ትውልድ፣ አይደለም ሀገርና ህዝብ ቀርቶ ራሳቸውን እንኳን ከራሳቸው ጋር ማግባባት አይችሉም:: ሀገራችን በእንዲህ አይነቱ ብላሽ የሀሳብ ቀንበር ስር ከወደቀች ሰነባብታለች:: ጫንቃችን ላይ የወደቀውን የድህነትና የኋላ ቀርነት ቀንበር ሳናነሳ ሌላ የብሄርና የጥላቻ ቀንበርን እያመቻቸን እንገኛለን::
ጫንቃችን ላይ የጣልንው የመለያየት ቀንበር ቀና እንዳንል አጉብጦን እንደመጻጉ ከምንናፍቀው የድኅነት ደጅ አላደረሰንም:: ታመናል:: በብሄር ታመናል:: በወገንተኝነት ታመናል:: በሰላም እጦት ታመናል:: ባለመነጋገር ታመናል:: በጥላቻ ታመናል:: እኚህ ሁሉ ህመሞቻችን እንደ ሀገር ፊተኛነትን ነጥቀውን ማንም ባልሄደበት የኋላ ቀርነት ጎዳና ላይ አቁመውናል::
መፍትሄ ካሻን መፍትሄው አንድ ሲሆን፣ እርሱም በሰላም ሀሳብ ወጥተን የምንገባባትን፣ ተነጋግረን የምንግባባባትን፣ ተራርቀን የምንነፋፈቅባትን የጋራ ሀገር መፍጠር አለብን:: መፍትሄ ካሻን ከጦርነት የራቀ የሰላም ሀሳብ፣ የሰላም ምኞት ያለው መሪና ተመሪ ያሻናል:: ሀገር የተለያየ ሀሳብ ነው የሚያስፈልጋት:: የአሁኑ ስልጣኔና ርምጃ የመጣው በተለያዩ ሰዎች የተለያየ ሀሳብ ነው:: ሀሳባችን ሌሎችን እስካልጎዳ ድረስ የተለየ መሆኑ ችግር ይኖዋል ተብሎ አይታሰብም:: በመነጋገርና መወያየት ሁሉንም ወደሚያስማማ እውነት መጠጋት ግን የበለጠ አዋጭ እንደሆነ ይታመናል::
የትኛውም ሀገርና ህዝብ በተመሳሳይ ባህልና ስርዐት፣ ወግና ልማድ፣ አስተሳሰብና ርዕዮተአለም አልቆመም:: ሀገራችን ኢትዮጵያ የብሄር ብሄረሰብ ጉራማይሌ መልክ ናት:: ከእነዚህ በርካታ ብሄረሰቦች መካከል የሚወጣው የሀሳብ መልክ ደግሞ የተለያየ ነው:: እነዚህ የተለያዩ ሀሳቦች ለኢትጵያ ተጨማሪ ውበት እንጂ ተጨማሪ ስቃይ እንዲሆኑ መፍቀድ የለብንም:: እኛ ከተግባባን፣ ፖለቲከኞቻችን ለመስማማት ከተዘጋጀን ወደ ጦርነት የሚወስድ ሀሳብ አይኖረንም:: በእያንዳንዱ ብሄር ጓዳ ውስጥ ያለው የሰላምና የእርቅ ሀሳብ ነው:: ባህሎቻችን እንድንፋቀር እንጂ እንድንቀያየም አድርገውን አያውቁም::
ልዩነታችንን በማስፋት ለቅያሜአችን መንገድ የከፈትነው እኛ ነን:: ለቅያሜአችን መንገድ እስካልዘጋንና የአብሮነትን መንገድ እስካልከፈትን ድረስ ከድጡ መውጣት አይቻለንም:: ሁሉም ሀሳቦች ምንም ያክል ቢጎረብጡም በንግግር የሚታረቁ ናቸው:: ለአመታት እኔ ብቻ ነኝ ልክ በሚል አጉል አመለካከት ተተብትበን ሀገራችንን ላልተገባ ስቃይ ስንዳርጋት ኖረናል። አሁን ጊዜው ለዚህ የሚሆን አይደለም፤ በመነጋገር መስማማት ይኖርብናል::
ብዙዎች በመነጋገር ከኋላችን ተነስተው ጥለውን እየሄዱ ነው:: ብዙ ሀገራት በእኛ መፈጠር ተፈጥረው እኛን ለማሸማገል መሀላችን ሲገቡ እያየን ነው:: ይሄ ለታላቋ ኢትዮጵያ አይገባም:: በእርቅና በመግባባት የጥንቱን ታላቅነታችንን መመለስ ይኖርብናል:: ከአፍሪካ አልፋ ለአለም ሀገራት ለሰላም ግንባታ ሰራዊቶቿን እየላከች ሰላም ስታሰፍን የቆየች ሀገር ዛሬ ሰላም ርቋት ስትታይ ክፍተቱ የቱ ጋ እንደሆነ ማጤን ያሻል:: ችግሮቻችንን በሀሳብ የበላይነት በማሸነፍ ስማችንን ማደስ ከሁላችንም የሚጠበቅ ጉዳይ ነው:: ልዩነታችን ውበታችን እንጂ የቅያሜአችን ምንጭ ሊሆን አይገባም::
በአለም አቀፍ ደረጃ በብዙ ቋንቋና በብዙ የብሄር ስብጥር የሚታወቁ ሀገራት ጥቂቶች አይደሉም:: ሁሉም ግን ልዩነታቸውን ለስልጣኔና ለፊት መሪነት የተጠቀሙ ናቸው:: ለአብነት ያክል ህንድን ማንሳት እንችላለን:: ህንድ በህዝብ ብዛት ከአለም ሁለተኛ ናት:: በውስጧም ከሁለት ሺህ በላይ ቋንቋዎች ይነገሩባታል:: የሚገርመው ደግሞ ይህን ሁሉ የቋንቋና የብሄረሰብ ስብጥር ይዛ ላለፉት እጅግ በርካታ አመታት ምንም አይነት ጦርነት ተስተናግዶባት አለማወቁ ነው::
ናይጀሪያን ብናይ ተመሳሳይ ታሪክ ነው የምናገኘው:: በህዝብ ብዛት ከአፍሪካ ቀዳሚ ከአለም ደግሞ ተከታይ ናት:: በውስጧም ከአምስት መቶ በላይ የተለያዩ ጎሳዎች ይኖራሉ:: የህዝብ ብዛቷና የጎሳዋ መብዛት ግን ችግር አልፈጠረባትም:: መነጋገርን ያስቀደመ ማህበረሰብ ልዩነቶቹ ምንም ያክል ቢጎሉም ኢምንት ናቸው:: ነገሮች በእኛ አስተሳሰብ ስር ናቸው:: አስተሳሰባችንን መቆጣጠርና መግራት ስንችል ብቻ ነው ሀገር መፍጠር የምንችለው:: ይህን ማድረግ ካልቻልን ግን ልዩነቶቻችንን እንደ እንከን በመቁጠር ውበት አልባ ሀገር ነው የምንፈጥረው:: ስንበዛ መልከኞች ነን:: የተለያየን ስንሆን ውበታም ነን:: ውበትና መልክ ደግሞ ሀገርን የሚያደምቅ የኩራትና የልዕልና ምንጭ እንጂ የጥላቻ አውድ አይደለም::
በሀሳባቸው ተፅዕኖ ስር የወደቁ ሰዎች ተነጋግሮ መግባባት አይቻላቸውም:: አይደለም ከሌላው ጋር ከራሳቸው ጋርም መግባባት አይቻላቸውም:: የሀገራችን አብዛኛው ችግር ይህ ነው:: ለሀሳቦቻችን ቅድሚያ የሰጠን ነን:: ምንም ያክል አዋጪና በላጭ አስተያየት ብንሰማ እንኳን እኔ ያልኩት ካልሆነ የምንል አይነት ነን:: እነዚህ አስተሳሰቦች ናቸው ዛሬ ላይ ዋጋ እያስከፈሉን የሚገኙት:: ሀገራችን በላጭ ሀሳብ ያስፈልጋታል:: በበላጭ ሀሳብ ሀገራችንን መምራት ልምድ ማድረግ ይኖርብናል:: በላጭ ሀሳብ በሌለበትና ተነጋግሮ መግባባት በማይችል ሀገርና ህዝብ ውስጥ ነውጥ እንጂ ለውጥ የለም:: መገፋፋት እንጂ መተቃቀፍ አይታሰብም::
ዘመናዊነትን መዝገበ ቃላት ላይ ብንፈልገው ተነጋግሮ መግባባት የሚል መልስ ነው የሚሰጠን:: ዘመናዊነት ተነጋግሮ መግባባት ከሆነ የእኛ በሀሳብ ልዩነት እሰጥ-አገባ ውስጥ መግባት ምን የሚሉት ስልጠኔ ነው? እንደ መንግስትም ሆነ እንደ ማህበረሰብ ዘመናዊነታችንን ተነጋግሮ በመግባባት ውስጥ ልንፈልገው ይገባል:: እንደ ሀገር ዘመናዊነታችንን በውይይት መጀመር ይኖርብናል:: ባለመነጋገር ከዘመናዊነት ርቀን የሰነበትንባቸው እነዛ በርካታ አመታት አስተምረውናል ብዬ አምናለው:: ባለመነጋገር ሰላማችንን፣ አንድነታችንን ነጥቀውን አለያይተውን ነበር:: አሁን ግን መከራ ይበቃናል:: በጠብመንጃ ሳይሆን በውይይት፣ በመለያየት ሳይሆን በመቀራረብ ሰላም ማምጣት መልመድ ይኖርብናል::
የአለም ስልጣኔ በመነጋገር ውስጥ የቆመ ነው:: ወደ አፍሪካ ስንመጣ ግን ይሄ እውነት ጎልቶ አይታይም:: በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በማህበራዊ ህይወታችን ባጠቃላይ በእያንዳንዱ የህይወት እንቅስቃሴአችን ላይ የሰለጠነ ውይይት አይስተዋልም:: ለብዙ ነገር ሰልተን ለመነጋገር ሲሆን ግን የከሸፍን ነን:: አፍሪካን ዋጋ እያስከፈላት ካለው ነገር ውስጥ አንዱና ዋነኛው ደግሞ ይሄ የአልሸነፍ ባይነት ልክፍት ነው:: ወደ እኛ ሀገር ስንመጣ ደግሞ የከፋ ሆኖ እናገኘዋለን:: ያለፉት ሀምሳ አመታት ካለመነጋገር ጦርና ጎራዴ የተማዘዝንባቸው ሆነው ያለፉ ነበሩ:: በቀላል ነገር ብዙ ነገሮችን ያጣንባቸው እንደነበሩ ማውጋት ይቻላል::
አሁን በህይወት የሌለች አንድ ጥበበኛ አያት ነበረችኝ:: ምድር ላይ ዘጠና ስድስት አመት ስትኖር ሁሌ የምትለው አንድ ነገር ነበር ‹መተው ነገሬን ከተተው›› እንደ አያቴ የመተውን ጥበብ ያስተማረኝ ማንም የለም:: በአያቴ ነፍስ ውስጥ፣ በአያቴ ሴትነት ውስጥ፣ በእርጅናዋ ውስጥ ሳይቀር አፍርቶና ጎምርቶ ያገኘሁት አንድ ታላቅ ጥበብ ቢኖር የመተው ጥበብ ነው:: የአያቴ እውነት ይህ ብቻ አይደለም፤ እውነተኛ አሸናፊነት የት እንዳለ የምታውቅ ሴት ነበረች:: እውነተኛ አሸናፊነት በመተውና በመቻል ውስጥ ነው ያለው ትለኝ ነበር:: በትዕግስትና በይቅርታ ውስጥ ነው ያለው ብላ ነግራኝ ታውቃለች:: ይህንንም እውነት ስታስረግጥልኝ ‹መቻል ምን ይከፋል፣ ሆድ ከሀገር ይሰፋል…› ስትል አውግታኛለች::
እኔና እናንተ ይህን እውነት አናውቀውም:: አያቴ ይህችን ምድር እስከተሰናበተችበት ጊዜ ድረስ በመተው ጥበቧ ለዘጠና ስድስት አመታት ከሰው ልጅ ሁሉ ጋር በመስማማት ኖራለች:: የአያቴ እውነትና እምነት ያስደንቀኛል:: የዛሬዋን ኢትዮጵያ በእሷ ነፍስ ውስጥ፣ በእሷ ሴትነት ውስጥ አያታለሁ:: የአያቴ እውነት አሁን ላለነው ለእኛ መልካም እውቀት ሆኖ ስላገኘሁት አካፈልኳችሁ::
አሁን ላለችው ኢትዮጵያ የአያቴ ጥበብ ያስፈልጋታል:: ለእኛ፣ አሁን ያለው ትውል አባላት የአያቴ እውነት ያስፈልገናል:: አያቴ በመተው ውስጥ ከዘጠኝ አስርት አመታት በላይ በኩራትና በልዕልና ተራምዳለች:: ሁላችንም ወደ መተው እንመለስ:: ወደ ሆደ ሰፊነት፣ ወደ ሰምቶ መቻል እንመለስ:: በትዕግስት፣ በይቅርታ ወደ ማሸነፍ እንሸጋገር:: በውይይት ወደ መርታት እንምጣ:: ሳንግባባ የምንሄድባቸው መንገዶች ሩቅ አያደርሱንም:: ሳንስማማ በልዩነት የምንራመድባቸው ጎዳናዎች አይባርኩንም::
ካልተግባባን የምንመኛትን ኢትዮጵያ አንደርስባትም:: ልንፈጥረው የምናስበውን ትውልድ አንታደገውም:: ብንሄድ፣ ብንሄድ ወደ ረፍታችን አንደርስም:: የትንሳኤያችንን ጥጉን አናገኘውም:: ላሰብናቸው ሀገራዊ በጎ ሀሳቦች ሰላም ያስፈልገናል:: ሀገራዊ መግባባት ግድ ይለናል:: ሀሳቦቻችንን ካልገታናቸው ወይም ደግሞ በሌላ አስታራቂ እውነት ካልቀየርናቸው አደገኛ ነው የሚሆኑብን:: ብዙ ሀገራት የፈረሱት፣ ብዙ ትውልዶች የመከኑት በሀሳብ ነው:: እንደዚሁም፣ በጋራና በመተማመን ሀሳብ ያተረፉ በርካታ ሀገራት አሉ:: ለእኛም የሚያስፈልገን በጋራ ሀሳብ ወደ ፊት መሄድ ነው::
ሀገራችን በአሁኑ ሰዐት በሰላም እርምጃ ላይ ናት:: ርምጃዋ ይፈጥን ዘንድ ሁሉን አቀፍ ምክክር ያስፈልጋታል:: ርምጃዋ ይፈጥን ዘንድ የሀሳብ የበላይነትን መሰረት ያደረገ የንግግር መድረክ ያስፈልጋታል:: ትላንት ላይ ለጦርነት ምክንያት የሆኑ የመለያየት ሀሳቦች በውይይት መፈታት ለሀገራችን የሰላም ርምጃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው:: የውስጥና የውጪ ፖለቲካዊም ሆኑ ማህበራዊ ችግሮቻችን በጋራ ውይይት የሰላም ፀሀይ ቢወጣባቸው በብዙ እናተርፋለን ባይ ነኝ:: እኛ እየኖርን ያለነው በድሮ ባህል ነው:: ትናንትና ለጦርነት መንስኤ የሆኑ ችግሮቻችንን ዛሬም ለጦርነት እየተጠቀምንባቸው እንገኛለን:: ተወያይቶ ከመስማማት ይልቅ ጎራ ወደ መፍጠር መሄድ ይቀናናል:: ትላንትናዎቻችን በዚህ ደረጃ ዋጋ ያስከፈሉን ነበሩ::
ልማዶቻችን መቀየር አለባቸው:: ጀግናን በጦር ሜዳ ሳይሆን በጠረጴዛ ዙሪያ እንዴት መፍጠር እንደሚቻል ማወቅ ሀገራችንን የሚታደጋት የለውጥ እሳቤ ነው:: ኢትዮጵያ በለውጥ ጎዳና ላይ ናት ብለን ስንናገር በምክንያት መሆን አለበት:: ለውጥ ብዙ ገጾች አሉት:: የሁሉም ገጾች ማረፊያ ግን የሀሳብ የበላይነት ነው:: የሀሳብ የበላይነት ደግሞ ተነጋግሮ በመስማማት የሚመጣ የስልጣኔ ከፍታ ነው:: ለውጥ በሀሳብ የበላይነት ካልመጣ ጥያቄ ውስጥ ይወድቃል::
ስለሀገር ሰላም ጥቂት ሰዎች ብቻ ነደው የሚፈጥሩት እሳት የለም:: በእሳቱ ለመሞቅ ሁላችንም ነዳጅ መሆን አለብን:: እሳቱ ለውጥ ነው:: ለውጥ ደግሞ በጋራ የሚመጣ የአብሮነት ሀይል ነው:: የለውጥ መጀመሪያ መነጋገር ነው:: የመነጋገር መጀመሪያ ደግሞ በሀሳብ የበላይነት ማመን ይሆናል::
ሲወቅስና ሲተች፣ ሲረግምና ሲያንቋሽሽ የኖረ አእምሯችንን ለአዲስ ለውጥ ማዘጋጀት ይኖርበታል:: በጥላቻና በመገፋፋት የቆመ ሰውነታችን አብሮነትን መልመድ ግድ ይለዋል:: ሌሎችን ባለማዳመጥ ዘመናትን የተሻገረው ብኩርናችን ሌሎችን በማድመጥ የአብሮነትን ሀሁ መማር ግድ ይለዋል:: በራሱ ፍቅር የወደቀ እኛነታችንን ሌሎችን ማፍቀር እንዲለምድ በማድረግ ለውጣችንን ከራስ እንጀምር::
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 21 ቀን 2015 ዓ.ም