ቀባሪ አታሳጣኝ የሚለው የአባቶቻችን አባባል አስፈላጊነቱ የታየኝ ከሰሞኑ ነው:: የዚህ ምክንያቱም በማህበራዊ ሚድያ ሲዘዋወር ያየሁት እንደወጡ የቀሩ ሴት እህቶቻችንን መጨረሻ ማየቴ ነው:: በዚህ ተንቀሳቃሽ ምስል ላይ ቦታው በውል በማይለይ የአረብ በረሃ ላይ እራሳቸውን ችለው ለቤተሰብ ሊተርፉ አስበው ጉዞ የጀመሩ እህቶቻችን የበረሃውን ውሃ ጥም፣ የበረሃው ሙቀትና በባዶ እግር መጓዙን መቻል ሲያቅታቸው በየመንገዱ ቀርተው ይታያሉ::
ድጋሜ ላይናገሩ ልሳናቸው ተዘግቶ፤ ላይነቁ አሸልበውም ፊታቸው ላይ ከራስ አልፎ ቤተሰብን የማሳረፍ ጉጉት ይታያል:: እንደሀገራቸው ወግና ልማድ ለቤተሰብ መርዶ ሳይነገር፤ ፍትሃት ሳይፈቱ፤ በለቅሶ ሳይቀበሩ፣ ለቅሶ፣ ህዝን ሰልስት እየተባለ ሳይቆጠር ቀባሪ አሳጥቷቸው ማየት በእጅጉ ያማል:: በርካቶች የሞታቸው መርዶም ቤተሰብ ጋር ሳይደርስ ቤተሰብ ልጄን ምን ዋጠው በሚል ጭንቅ መምጣታቸውን ይናፍቃል፤ ልብንም ይሰብራል::
ከዚህ የተረፉና ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው ዜጎች በህገወጥ አዘዋዋሪ እጅ ወድቀው በግዳጅ ሊያሳልፉላቸው የጓጉ ቤተሰቦች ጋር በመደወል ከሚሞቱ ብር እንዲልኩ ከእጅ ወደአፍ የሆነ ኑሮ የሚኖሩ ቤተሰቦቻቸውን ይማፀናሉ:: ቤተሰብም ልጁ ተሰዶ እንደሚያሳልፍለት በመተማመን የወሰደውን ብድር ሳይመልስ ሌላ ዕዳ ውስጥ ይዘፈቃል:: በርካቶች ለነገ ህይወታቸው ተስፋን ሰንቀው መዳረሻ እና የጉዞ መስመር ባደረጓቸው አገራት ህገወጥ ናችሁ ተብለው ታስረዋል፤ ተርበዋል፤ ታርዘዋል፤ ከባድ ስቃይ አስተናግደዋል::
በዚያው ልክ ይህንን ሁሉ ስቃይ አልፈው በሠላም እነሱ በውል ባያውቁትም ደላሎቹ ካሰቡላቸው መዳረሻ የሚደርሱ ዜጎች ቁጥርም ቀላል አይደለም:: ሆኖም ወደ አረቡ ሀገራት ለሥራ ከሚሄዱ ዜጎቻችን በአብዛኛው ከገጠሪቱ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የሚመጡ ናቸው:: ሆኖም በመዳረሻው ስለሚጠብቃቸው ሁኔታ ከደላሎቹ፣ ከአዘዋዋሪዎቹም ሆነ ከዚህ ቀደም በህጋዊ መንገድ ከሚወስዷቸው ኤጀንሲዎች በቂ መረጃ አያገኙም ነበር::
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያሳየው፤ ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ በሳዑዲ አረቢያ ደረጃቸውን ባልጠበቁ እስር ቤቶች እና ማቆያ ማዕከላት ውስጥ ይገኙ የነበሩ ከ133ሺ በላይ ዜጎች ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዋል:: ከእነዚህ ተመላሾች መካከል የተወሰኑት በደረሰባቸው ፆታዊ ጥቃት የማን እንደሆነ የማያውቁትን ልጅ ይዘው መጥተዋል፤ ቀጣዩም ፈተና ያለረፍት ይቀጥላል::
በርካቶች ያለዕረፍት ቤት ተዘግቶባቸው ሲሰሩ በመቆየታቸው ለአዕምሮ ጭንቀት ተዳርገዋል፤ የተወሰኑት ከሰውነት ክፍላቸው ምን እንደጎደለ ባያውቁም ሰውነታቸው ላይ ያለውን ጠባሳ እያዩ ምኔን ይሆን ቀደው ያወጡት የሚል ጭንቀት ላይ ናቸው:: በእነዚህና ሌሎች ምክንያቶች ወደ አረብ አገራት የነበረው የስራ ስምሪት ከተቀባይ ሀገራት ጋር አስፈላጊው ስምምነት ላይ እስኪደረስ ተቋርጦ ቆይቷል::
ያኔም ታዲያ ዜጎች በየመንገዱ ለአውሬ እየተጣሉ መቅረታቸው፤ ጀልባ ሞላ ተብሎ ውቅያኖስ ላይ መዘርገፋቸው፤ በየአገራቱ እንደዕቃ በኮንቴነር ታሽገው ሲጓጓዙ መሞታቸው ለህገወጥ አዘዋዋሪዎቹ እና ደላሎቹ ምናቸውም ነው:: ስለዚህም መንግስት በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን አማራጮች የአረብ ሀገራት የሥራ ሥምሪትን አስፈላጊው ሥምምነት ላይ እስኪደረስ ማገዱን ቢያሳውቅም ደላሎቹ በየገጠር ቀበሌው በመዞር ሚስኪን ዜጎችን ለመሰል ስቃይና ሞት መመልመላቸውን ቀጥለው ነበር::
ኑሮን ለማሸነፍ የሰዎች ከቦታ ቦታ መፍለስ ያለ የነበረ፤ ወደፊትም የሚኖር ነው:: ችግሩ ፍልሰቱ በምን ዓይነት መንገድ ተካሂደ የሚለው ነው:: ‹ሻወርና ሂስ ከራስ ሲጀምር መልካም ነው› የሚል አባባል በተደጋጋሚ የታክሲዎች ማድመቂያ ጥቅስ ሆኖ ይታያል:: እውነትም ሂስን ከራስ መጀመር መልካም ስለሆነ ወደ አረብ ሀገራት የሚሰማሩ ዜጎቻችን ምን ዓይነት ነበሩ የሚለውን መለስ ብለን እንቃኝ::
አብዛኞቹ ህገወጥ የሰው አዘዋዋሪ ደላሎች በብዛት የሚንቀሳቀሱባቸው የአገሪቷ አካባቢዎች ገጠሪቷ የአገራችን አካባቢዎች ናቸው:: እነዚህ አካባቢዎች ደግሞ የጤና ሚኒስቴር የጉድጓድ ሽንት ቤትን ጠቀሜታና ከመጸዳጃ ቤት መልስ እጅን የመታጠብ ጠቀሜታን በመተንተን ሰዎች ሽንት ቤት እንዲቆፍሩና የግልና የአካባቢ ንጽህናቸውን እንዲጠብቁ ምክር የሚሰጥባቸው ናቸው::
ይህ ማለት ከዚህ አካባቢ የሚነሱ ሰዎች እጅግ የዘመነ አኗኗር ለሚከተሉት ሀገራት እራሳቸውን ሳያላምዱ በእነዛ ሀገራት የሚኖሩ ዜጎችን ኑሮ ለማቅለል ይጓዛሉ:: በዚህ ሂደት ቀጣሪዎቻቸው የመጓጓዣን ጨምሮ ለአገናኝ ኤጀንሲዎቹ ከፍተኛ ክፍያ ይከፍላሉ:: በርካታ ወጪ አውጥተው ያመጧቸውን ሰራተኞች ከቤት ጽዳት እስከ ዘመናዊ ምግብ አሰራር በዘመናዊ መሳሪያ ለታገዘው የአረቡ ዓለም ኑሮ ዝግጁ እንደሆኑ ቀጣሪዎቻቸው ይጠብቃሉ::
ቀደም ብሎ ሲሆን የቆየው ግን የተገላቢጦሽ ነበር:: መጸዳጃ ቤቱን መግባባት ይቸግራቸዋል፤ ወንዝ ወርደው ልብስ ሲያጥቡ የነበሩ ታዳጊ ልጃገረዶች የአሰሪዎቻቸውን ውድና ቅንጡ ልብሶች በዘመናዊ የልብስ ማጠቢያ ማሽኖች እንዲያጥቡ ብሎም እንዲተኩሱ ይጠበቅባቸዋል:: ያሰቡትን ብሎም የከፈሉትን ያላገኙት ቀጣሪዎች ለማሰልጠን ቢሞክሩም በቋንቋ መግባባት የማይታሰብ ነው:: ይሄ አሰሪዎቻቸውን የሚያናድድ ነው፤ ኑሮን ለማሸነፍ የተሰደዱትን ዜጎቻችንም ለሌላ የሥነ ልቦና ጫና የሚዳርግ ነው:: በዚህም አብረዋቸው ከሚሰሩ የሌላ አገራት ዜጎች ያነሰ ክፍያ ከመከፈልም አልፎ እንደሚያንሱ እንዲያስቡ ሲደረጉ ቆይቷል::
ባስ ሲልም ክፍያን እስከመከልከል፤ ያለዕረፍት አድካሚ ስራን እንዲሰሩና አለፍ ሲልም ምግብ እስከመከልከል የደረሰ በደል አስተናግደዋል:: ይህም ቢሆን በርካታ ዜጎቻችን የሄዱት በህገወጥ መንገድ ስለሆነ ከኤምባሲዮቻችን ጋር መገናኛና አቤት ማያ መንገዱን አያውቁትም:: የላኳቸው ደላሎች የእነሱ ነገር የሚጨንቃቸው ብር እስኪቀበሉ ድረስ ብቻ ስለሆነ ለመብታቸው መከበር ተገቢውን ክትትል አያደርጉም:: ቢከፋቸው፣ ቢርባቸው ጭንቀታቸውን የሚያካፍሉት አይዟችሁ ባይ ወገን አለማግኘታቸው ከጉዳቱ በላይ ሌላ ጉዳት ሆኖ ቆይቷል::
ሆኖም ‹ለሁሉም ጊዜ አለው› እንደሚል መጽሐፉ፤ የህገወጦች መፈንጫ፤ የዜጎች መሰቃያ የነበረው የአረብ ሀገራት የሥራ ስምሪት በተገቢው መንገድ የመጀመሩ ብስራት ተሰምቷል:: አዲስ በተቋቋመው የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ዓማካኝነት በውጭ አገራት የሚደረገው የሥራ ዕድል ፈጠራ የዜጎችን ተጠቃሚነትና ደህንነት በሚያረጋግጥ መንገድ ለማድረግ አዲስ ጉዞ ተጀም ሯል::
በአረብ ሀገራት የተጀመረው የሥራ ስምሪት ዜጎች ተፈላጊ በሆነ የሥራ ዘርፎች አስፈላጊውን ሥልጠና ያገኙና የበቁ ዜጎችን የማሰማራት መልካም ጅምር ነው:: በዚህም ዜጎች ከየት እንደተነሱ የሚታወቅበት ምን ብቃት እንዳላቸው በምዘና የሚረጋገጥበት የሥራ ስምሪት ተፈጥሯል:: እንደ ሥራና ክህሎት ሚንስትር መረጃ፤ እስካሁን ከ12ሺ በላይ ዜጎች አስፈላጊውን ሥልጠና ወስደው የሥራ ስምሪት ተካሂዷል:: ከ67ሺ በላይ ዜጎች ለአረብ አገራት የሥራ ስምሪት ብቁ ያደረጋቸውን ሥልጠና ወስደዋል:: የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ስልጠና የሚሰጥባቸው 77 ማዕከላት ተዘጋጅቷል::
ኑሮዬን እለውጣለሁ ብሎ የጓጓ ኢትዮጵያዊ ዜጋ በህጋዊ መንገድ ከመነሻው እስከመድረሻው ታውቆ ጉዞ ያደርጋል:: በሚሄድበት አገር ስለሚጠብቀው ሁኔታና ስለሥራ ድርሻው መረጃውም ሆነ አስፈላጊው ክህሎት ኖሮት ይጓዛል:: በዚህ ዓይነት መንገድ የሚጓዙት ዜጎች አይበለውና ደብዛቸው ቢጠፋ ምን ገጠማቸው? ብሎ ለመፈለግ ቀላል ነው:: መልካም ጅምሩን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ይህን አማራጭ ትተው ዜጎቻችንን አሁንም በበረሃ በዱር በገደል ለማሰማራት የሚፈልጉ ህገ ወጦችን ሀይ የማለቱ ሥራም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት::
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ከትዝታ ማስታወሻ
አዲስ ዘመን ሰኞ ግንቦት 21 ቀን 2015 ዓ.ም