የትናንቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወይም አአድ ፤ የዛሬው የአፍሪካ ሕብረት ወይም አሕ/AU/የተመሠረተበትን 60ኛ አመት”Our Africa Our Future” ወይም “አፍሪካችን ነገ’ችን”በሚል መሪ ቃል በያዝነው ወር በተለያዩ ዝግጅቶች እያከበረ ነው ። ባለፈው አርብ ግንቦት 17 ቀን 2015 ዓም የተመሠረተበትን ዕለት ወይም “የአፍሪካን ቀን” በተለየ ድምቀት አክብሯል ። በዓሉ በ55ቱ አባል አገራት በአጀንዳ 2063 አተገባበር ላይ የተገኙ ውጤቶችን ፣ ያጋጠሙ ችግሮች ፣ የተሻገሩበትን ስልት በመገምገም ዕለቱን ይዘክሩታል ይለናል በሕብረቱ ድረ ገጽ የተቀመጠ መረጃ ። በተለያዩ ብዙኃን መገናኛዎች ስለ ፓን አፍሪካኒዝም እሳቤ ፣ ስለ አፍሪካ ታሪክ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች እየተከናወኑ ከመሆኑ ባሻገር የተዛባውን የአፍሪካ ተረክ ለማረቅና ለማስተካከል የተቀናጀና የተናበበ ጥረት እየተደረገ ነው ። የዚህ አካል የሆነ ሥነ ሥርዓትም የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር በተገኙበት ተካሂዷል ።
የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ አፍሪካ ኅብረት 60ኛ ዓመት ክብረ በዓል በአዲስ አበባ የኅብረቱ ዋና መሥሪያ ቤት በቀድሞ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንትና የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ በተሠየመው መሠብሠቢያ አዳራሽ በተዘጋጀ ሥነ ሥርዓት የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ፤ አፍሪካ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም ምርታማነቷን መጨመርና ራሷን መመገብ መቻል አለባት። መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች ፣ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላትና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በታደሙት በዚህ መድረክ የ32 የአፍሪካ አገራት መሪዎች የዛሬ 60 ዓመት በአዲስ አበባ ተገኝተው የኅብረቱን መመሥረት የሚያበስረውን ቻርተር መፈረማቸውን አስታውሰዋል ።
አሁን ላይ 55 አባል አገራት የያዘው አፍሪካ ኅብረት በዓለም መድረክ ጠንካራና ትልቅ ሥፍራ እየያዘ መምጣቱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመው በዚህም የአህጉሪቱንና የህዝቧን ጥቅም ለማስከበር ቢቃረብም ፤ የአፍሪካ ኅብረት መሥራች አባቶች በኅብረቱ መቋቋሚያ ቻርተር ያሠፈሯቸውን ቃል ኪዳኖችና በአጀንዳ 2063 የተጠቀሱትን ፍላጎቶች ሙሉ በሙሉ በመፈፀም ረገድ ብዙ ይቀራል ብለዋል። አህጉሪቱ አሁንም በድኅነት ውስጥ እየማቀቀች ፣ አሰራሮች በሙስና እየተተበተቡ ፣ ለገጠሙን ችግሮች የሌሎችን እጅ እያየን ነጻ ነን ማለት እንደማይቻል አመልክተዋል።
አፍሪካ ያላትን ሀብት በመጠቀም ይህን ገጽታ መቀየር ፤ በተለይም ደግሞ የአፍሪካ ወጣቶች በግብርና፣ በኢንዱስትሪ ፣ በቴክኖሎጂ ዘርፍ በመሳተፍ አህጉሪቷ መለወጥ እንደሚገባ ጠቁመው በዚህ ረገድ በተለይም አፍሪካ የመበልጸግ አቅም እንዳላት ፤ ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ የምትሰራው ውጤታማ ሥራ አብነት መሆኑን ጠቁመዋል ። በሌላ በኩል አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረክ ተሠሚነቷን ለማጠናከር የሚያስችሉ ዓለም አቀፍ ውክልናዋ መስፋት እንዳለበት ፤ ለዚህም በተመድ የጸጥታው ምክር ቤት እንዲሁም በቡድን 20 እና ቡድን 7 ሀገራት ተሣትፎ እንዲኖራት መስራት ይገባል ብለዋል ። የአፍሪካ አገራትና ዜጎቿም የአፍሪካ ኅብረት መሥራች አባቶች የያዟቸውን የአንድነት አቋም በማስቀጠል በአፍሪካ አገራት መካከል ጠንካራ ኅብረት ለመመሥረት የሚያደርጉትን ጥረት መቀጠል እንደሚገባም አሳስበዋል።
የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ ማኅማት በበኩላቸው ፤ አፍሪካ ኅብረት የተለያዩ ተግዳሮቶችን አልፎ አሁንም አህጉሪቱን የተሻለ ደረጃ ላይ ለማድረስ እየሰራ ያለ አህጉራዊ ተቋም ነው። አፍሪካ ችግሮችን ተቋቁማ የተሻለ ምጣኔ ሀብታዊ እድገት እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ድምጿም የመሰማት እድል ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ቢመጣም፤ አፍሪካ ላይ ውጪያዊ ጫናዎች በመበራከታቸው፤ አፍሪካን እንዲሁም መላውን ዓለም ትኩረት ያደረጉ የባለብዙ ወገን ሥራዎች ለመሥራት አሉታዊ ጫናዎችን እየፈጠሩ ስለሆነ ለመከላከል በጋራ ልንቆም ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ለቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጀት ለአሁኑ አፍሪካ ኅብረት ምሥረታ ያበረከተችውን አስተዋጽዖ አሁንም ለአህጉሩ ትብብር መጎልበት አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት ፤ የመጀመሪያዋ ሴት ሊቀ-መንበር በመሆን የአፍሪካ ኅብረትን እንደ ጎርጎረሳውያን አቆጣጠር ከ2012 እስከ 2017 የመሩት ደቡብ አፍሪካዊቷ የቀድሞ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ዶክተር ድላሚኒ ዙማ አሳስበዋል ። ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ የአፍሪካ ኅብረት በርካታ ፈተናዎችን አልፎ እዚህ ትልቅ ደረጃ ላይ ደርሷል ካሉ በኋላ በመቀጠል ከስኬቶቹ መካከል ድርጅቱ በወቅቱ ሲቋቋም ነጻ የአፍሪካ አገራትን ለመፍጠር ያደረገውን ጥረት ለአብነት አንስተዋል።
የፖለቲካዊ ውህደት ተልዕኮን አንግቦ እንዲንቀሳቀስ ወደ ኅብረት የተሸጋገረበት ጊዜ እንደ ትልቅ እምርታ የሚወሰድ ነው ፤ አኅጉሩ በርካታ የምንኮራበት ስኬቶች ላይ ቢደርስም አሁንም የበዙ ውስጣዊ ችግሮች ፈተና ሆነው መቀጠላቸውን ፤ ለአብነትም በአፍሪካ እርስ በአርስ ግጭት መኖሩና አሁንም የጸጥታ መደፍረስ ችግር መሆኑን ገልጸዋል። ይህ ሁኔታ እንዲቀየር በርትቶ መሥራት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል ። ይህንን ተቋም ይበልጥ በመደገፍና ለቀጣይ ትውልድ አንድነቱ የተጠበቀ ፣ በኢኮኖሚ የተሳሰረ ፣ የበለጸገና ሰላምና ደኅንነቱ የተረጋገጠ አህጉር ማስተላለፍ እንደሚገባ አመልክተዋል። ለዚህም ኅብረቱና አባል አገራት በጋራ መሥራት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል።
የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ትግበራ በመልካም ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ፤ በአፍሪካ ብልጽግና ለማረጋገጥና በርካታ ሰዎችን ከድኅነት ለማውጣት የውሃ ፣ የሃይል ፣ የትራንስፖርትና ሌሎች ወሳኝ መሰረተ ልማቶች ሊሰፋፉ እንደሚገባ ፤ በተለይም አፍሪካ ያላትን ሀብት በመጠቀም ራሷን ልትመግብ እንደሚገባ ዶክተር ድላሚኒ አጽንኦት ሰጥተዋል።
የአፍሪካ ህብረት ታሪካዊ ዳራ በወፍ በረር ሲቃኝ፤
የቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ሕብረት ልክ ባለፈው ሀሙስ ዕለት ከ60 ዓመት በፊት ግንቦት 17 ነበር የተመሰረተው ይለናል የአሻም ቴሌቪዥን ። አፍሪካውያን አህጉራዊ ድርጅት ከመመስረታቸው በፊት በብራዛቪል ፣ በሞኖሮቪያ እና ካዛብላንካ ቡድን በሚል በተለያዩ ፍላጎቶች ለሦስት ተከፋፍለው ነበር ። ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም በአፍሪካዋ መዲና አዲስ አበባ አይረሴው የአፍሪካውያን ታሪክ ተፃፈ ፡፡ ከብዙ ውጣ ውረድና ድካም በኋላ ተሳክቶላቸው በነጻነት አርማቸው አዲስ አበባ የተሰባሰቡት 32ቱ ነፃ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች ከግንቦት 14 እስከ 17 ቀን 1955 ዓም ከመከሩ በኋላ ባለ 33 አንቀጹን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ቻርተር በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይ አፀደቁ ፡፡ በዕለቱም የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አዲስ አበባ ላይ ዕውን ሆነ።
ያች ቀን ለአፍሪካ አህጉር አዲስ የድል ምዕራፍን አበሰረች፡፡ ለአፍሪካውያንም አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም ተከፈተ፡፡ ያኔ አፍሪካውያን መሪዎች የባርነት ቀንበርን በተባበረ ክንዳቸው ከትከሻቸው ሊያወርዱ ቃል ኪዳን ገቡ፡፡ በወቅቱ ከ25 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያን በደስታ ስሜት የሚጠብቁት ፤ የመላው ዓለም ሕዝብ በቅርበት የሚከታተለው ጉባኤ ፤ ከ500 በላይ ከመላው ዓለም የተሰባሰቡ ጋዜጠኞች የሚሽቀዳደሙበት ውሳኔ እና በብዙ ሺህ ሕዝብ ዘንድ በቴሌቪዥን መስኮት የሚጠበቀው የ32ቱ ነጻ የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎች ጉባኤ ግንቦት 14 ቀን 1955 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ ነበር የተጀመረው፡፡
የወቅቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመራጭ ሊቀ መንበር ግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት አፄ ኃይለ ስላሴ የሊቀ መንበርነት ምርጫ በሙሉ ድምፅ ከፀደቀ በኋላ ረዘም ያለና ቀልብን ሰቅዞ የሚይዝ ንግግር አደረጉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሊቀ መንበር ንግግር እንደተጠናቀቀም የላይቤሪያው ፕሬዚዳንት ተብማን እና የሱዳኑ ፕሬዚዳንት አቦድ ተራ በተራ እየተነሱ ንግግራቸውን በአዳራሹ ለተሰባሰበው ጉባኤተኛ ፤ ልዩ መልእክተኛ እና በቴሌቪዥን መስኮት ለሚጠባበቀው የዓለም ሕዝብ አደረሱ፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ ከአሜሪካ እስከ ሩሲያ፣ ከህንድ እስከ ምዕራብ ጀርመን ያሉ ሀገራት መሪዎች የመልካም ምኞት እና የደስታ መልዕክቶች ተስተጋቡ፡፡ በወቅቱ አሜሪካን በፕሬዚዳንትነት በመምራት ላይ የነበሩት ፕሬዚዳንት ጆን ኤፍ ኬኔዲ በላኩት መልዕክታቸው፤” የእኔን እና የአሜሪካን መንግሥት መልካም ምኞት ለእናንተ የአፍሪካ ሕዝብ እንደራሴዎች ለመግለጽ እድል ስለገጠመኝ ከፍ ያለ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ አፍሪካ ያለማቋረጥ ነፃነትን እና አንድነትን ለመጎናፀፍ የምታደርገው እርምጃ ለሰው ልጅ ክብርና ራስን ለማወቅ የሚደረገው ተጋድሎ ዋናው ክፍል ነው። አሜሪካ እና ሕዝቧ ስራችሁን ስትጀምሩ የተቃና ውጤት እንድታገኙ ይመኙላችኋል፤” ብለዋል።
የመሪዎቹን ንግግር ለዓለም ዐይንና ጆሮ እንዲያደርስ አደራ የተባለው የያኔው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የአሁኑ ኢቢሲ የብኩርና ስራውን ለሕዝብ አስተጋባ ፡፡ ለአራት ቀናት በተካሄደው ጉባኤ ማጠናቀቂያ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም ደግሞ በእንግሊዝኛ እና በፈረንሳይኛ ቋንቋዎች በኢትዮጵያውያን የተዘጋጀው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መመስረቻ ረቂቅ ቻርተር ጉባኤተኛው ተወያይቶ እንዲያፀድቀው ቀረበ፡፡
ነገር ግን የጉባኤው መድረክ መሪ እና የወቅቱ የጊኒ ፕሬዚዳንት ሴኩ ቱሬ አዲስ ሃሳብ አቀረቡ፤ “የራሷ ቋንቋና ፊደል ያላት አፍሪካዊት ሀገር እያለችን ከቅኝ ገዥዎቻችን ቋንቋ ተውሰን ቻርተሩን መፈረም የለብንም” የሚል ፡፡ ሃሳቡም ተቀባይነትን አገኘና በጸሃፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ መሪነት ዶክተር ምናሴ ለማ ፣ አቶ ማሞ ታደሰ ፣ ክቡር አቶ ታደሰ ያዕቆብ ፣ ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩና በሌሎች ሚኒስትሮች ርብርብ በአንድ ሌሊት ወደ አማርኛ ቋንቋ ተተረጎመ ፡፡
የወቅቱ የግብፅ መሪ የነበሩት ጋማል አብደል ናስር አረብኛ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት የሚናገሩት ቋንቋ በመሆኑ ለምን በአረብኛም አይዘጋጅም በሚል ያቀረቡት ሃሳብ ብዙ ቢያከራክርም በመጨረሻ ይሁንታን አግኝቶ በአራት ቋንቋዎች የተተየበው እና በ33 አንቀፆች የተዋቀረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ቻርተር በሙሉ ድምጽ ፀደቀ ። በ36ኛው የመሪዎች ጉባዔ ላይ በአፍሪካ ኅብረት ማቋቋሚያ ሰነድ እስኪተካ ድረስም አገልግሎት ላይ ቆዬ ፡፡ ኢትዮጵያም ከሕዝቦቿ እስከ መሪዎቿ ፤ ከቋንቋዋ እስከ ሰንደቋ ከአፍሪካ አንድነት ድርጅት እስከ አፍሪካ ህብረት ምስረታ ለአፍሪካውያን መዲናና ተምሳሌት እንደሆነች ቀጥላለች፡፡
በ1963 ዓ.ም 32 ነፃ መንግሥታት የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን በማቋቋም ስራውን የጀመረው አአድ ኋላም በጎርጎረሳውያን አቆጣጠር በ2002 ዓ.ም የአፍሪካ ህብረት ከተቋቋመ በኋላ የአባላቱ ቁጥር አድጎ አሁን ላይ 55 የአፍሪካ ሀገራት የድርጅቱ አባል ናቸው ። የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ራዕይ የነበረው ባለፈው ግማሽ ምዕተ ዓመት አህጉሪቱ እየገጠሟት የነበሩትን ተግዳሮቶች እንዲሁም የቅኝ ግዛት እና የዘር መድልዎ መወገድን በተመለከተ ነበር። በ1990 ዎቹ መገባደጃ ላይ መሪዎች በተለወጠው ዓለም አዳዲስ ተግዳሮቶችን ለመወጣት የድርጅቱን ራዕይ ማስተካከል አስፈላጊ መሆኑን ተወያይተዋል።
በ2002 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ደርባን ጉባዔ ላይ የአፍሪካ ህብረት መሪዎች እና መንግሥታት የመጀመሪያ ጉባዔውን ሲያደርግ ፋውንዴሽን አቋቁሞ ፤ አህጉሪቱ በፖለቲካ ፣ በኢኮኖሚ ፣ በባህል እና በማህበረሰቡ ውስጥ ግቦቹን ለማሳካት እንደ ዓላማ በመያዝ ጥረቱን ቀጥሏል። በ2014 ዓ.ም ይፋ በተደረገው የ2063 አጀንዳ አህጉራዊ አንድነት ለመመስረት የሚያስችሉ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን መርሀግብሮች ለይቶ አስቀምጧል። በዚህም መሰረት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ሕብረት የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት አስመልክቶ የአፍሪካ ቀንን አክብሯል ። በየዓመቱ የአፍሪካ ቀን መከበር የጀመረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት-አፍሪካ ህብረት ግንቦት 25 1963 ዓ.ም መመስረቱን ተከትሎ ነው። “የአፍሪካ ቀን” የአፍሪካውያንን መራራ የነፃነት ትግልና ብሩህ ተስፋ በማሰብ የሚከበር ሲሆን ፤ አፍሪካውያን ባህላቸውን ፣ ትውፊታቸውን እና ስልጣኔያቸውን ለመላው ዓለም የሚያስተዋውቁበት በዓል እንደሆነም ይነገራል።
ሻሎም አፍሪካ ! ሻሎም ኢትዮጵያ ! አሜን ።
አዲስ ዘመን ግንቦት 20 ቀን 2015 ዓ.ም