የአገራችንን የዲፕሎማሲ ታሪክ ዘወርወር አድርገን ለማቅረብ በማሰብ (እንደ ወረደ ላለማውረድ) “ታሪከ ዲፕሎማሲያችን” አልነው እንጂ በዚህች ጽሑፍ ለማንሳት የፈለግነው በቀጥታ ስለ አገራችን የዲፕሎማሲ ሁኔታ እና ይዞታ ነው።
እንደሚታወቀው የድሮው ዘመን እንደ አሁኑ ዘመን ዲፕሎማሲ አንድና አንድ ብቻ አይደለም። አይነቱም ሆነ ትርጉሙ፤ ይዞታውም ሆነ ይዘቱ . . . የተለያየ ነው። ይህ ተለያይቶው ራሱ እንኳን አንድ አይደለም፤ እንደየአካባቢው ይለያያል። እዚህ አፍሪካ ላይ ሆኖ አውሮፓ ውስጥ ካለ ጓደኛው ጋር ስለ ዲፕሎማሲ የሚያወራ ሰው በዲፕሎማሲ መዝገበ ቃላዊ ትርጓሜው ካልሆነ በስተቀር በምንም ሊግባቡ የሚችሉ አይመስልም።
እዚህ አዲስ አበባ እንኳን ያሉ የውጭ የዲፕሎማሲ ተቋማትን እንኳን ብንመለከት የሁሉም ስማቸው እኩል “ኤምባሲ”፣ “አምባሳደር” . . . ይሁን እንጂ ሥራቸው ሁሉ እንደ ስማቸው አንድና እኩል ነው ማለት አይደለም። በመሆኑም፣ የበረታው ጊዜው የሚፈቅደውን (አንዳንዴም ቀድሞ) የዲፕሎማሲ ተግባር ያከናውናል። እዛው ቁጭ ብሎ ውሃ የሚወቅጠው ደግሞ እዛው ውሃውን እየወቀጠ ነው የሚገኘው። በመሆኑም ዘርፉም ሆነ ተግባሩ ከባድ ነውና ከባድ ሚዛን ዲፕሎማቶችን የግድ ይላል ማለት ነው።
የውጭ ዲፕሎማሲ ረዥም በአገራችን ታሪክ ያለውና ከበርካታ የዓለም አገራት በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው። ቀደም ሲል ለአደባባይ የበቁ ጥራዞችንም ሆነ ሰነዶችን ብናገላብጥ ከድክመታችን ጥንካሬያችን ያይላል። ከስንፍናችን ብርታታችን ነው ሰፊውን ስፍራ ይዞ የሚገኘው።
ተመካሪ ሳንሆን መካሪ፤ ተሸምጋይ ሳንሆን ሸምጋይ ሆነን ስለ መዝለቃችን ነው የብዕር እውቅናን አግኝቶ የምንመለከተው። አንዳንድ አገራት የአገሩን ካርታና ከዓለም መገኛ ቦታዋን እንኳን የማያውቅን ሁሉ “ዲፕሎማት” እያሉ በሚሾሙበት በዚያ ዘመን፣ አትዮጵያ ተፅዕኖ ፈጣሪ ዲፕሎማቶችን ነበር የምትልከውም ይባላል። ዛሬስ?
ወደ ዛሬው ከመምጣታችን በፊት አሁንም ወደ ኋላ ሄድ ብለን ማየቱ ነው “ታኮ” የሚሆነን። አለበለዚያ “ስትራፕ” ማድረግ ይመጣልና ትርፉ አደጋ ይሆናል። “ስትራፕ ማድረግ” ደግሞ (ባለሙያዎች እንደሚሉት) ለአድራጊውም፤ ከኋላው ላለውም ጥሩ አይደለምና በምንም መንገድ “ስትራፕ ማድረግ” አይመከርም።
ድሮ የነበረው ዲፕሎማሲ ዘመኑን ያገናዘበ ነበር ይባላል። “እንዴት?” ሲባል፣ ኢትዮጵያ አይደለም ለራሷ ለዓለም የሚተርፉ ሀሳቦችን ታፈልቅ የነበረበት ወርቃማ የዲፕሎማሲ ዘመናት ነበሩ ነው የሚባለው። “ማስረጃ?” ሲባልም የማይጠቀስ የዲፕሎማሲ ታሪክ የለም።
ኢትዮጵያ በሊግ ኦፍ ኔሽን (ዓለም መንግሥታት ፊት) ላይ ያደረገችው ምድር አንቀጥቅጥ ንግግር፤ የኢትዮጵያ ልዑክ በአውሮፓና አሜሪካ እየተዘዋወረ ሲያደርጋቸው በነበሩ ጉብኝቶች ይፈጥራቸው የነበሩ አፍሪካዊ ተፅዕኖዎች ወዘተ ከሚቀርቡት ማስረጃና መረጃዎች መካከል ቀዳሚዎቹ ናቸው።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ኅብረት፣ ኤሲኤ እና መሰል ተቋማት እንዲመሠረቱ፤ መቀመጫቸውንም እዚሁ አዲስ አበባችን ውስጥ እንዲያደርጉ ከፍተኛ መስዋዕትነት በመክፈል ወደ ተግባር የተቀየረበት ወርቃማ የዲፕሎማሲ ዘመን እንደ ነበር ነው የነበሩት ሲናገሩም ሆነ፤ የፃፉት ሲነበብ የሚገኘው እውነት።
በዓለም ባንክ፣ የተባበሩት መንግሥታት፣ አይኤምኤፍ . . . ውስጥ የነበራት ከተሳታፊነት እስከ የመሪነት ሚናም እንዲህ በቀላሉ ተነስቶ የሚያልቅ እንዳይደለ ትናንት ብቻም ሳይሆን ዛሬም እየተነገረ ይገኛል። ነገም ስላለመነገሩ ምንም ምክንያት የለም።
ኢትዮጵያ በየሄደችበት የምትፈራ፣ የምትከበር፣ የምትታመን፣ የምትወደድ፣ የምትወከል፣ በሞዴል ነት የምትታይ፣ በፊት መሪነት የምትጠቀስ . . . አገር እንደሆነች ነው የሚያውቁ ሁሉ ሲናገሩ ነው የሚሰማው።
ይህ ሁሉ በአብዛኛው የዲፕሎማሲያችን ጥረትና ስኬት እንደ ነበርም ነው እነዚሁ የቅርብም ሆኑ የቅርብ ተሳታፊዎችና የሩቅ ታዛቢዎች ሁሌም ሲናገሩ የሚሰማው። እነ ሴንጎር፣ እነ ጋርቬይ፣ እነማንዴላ፣ እነጆን ስፔንሰር (እድል ተግዳሮቷን ጨምሮ) . . . ስለ አገራችን የመሰከሩትም ይህንኑ እንጂ ሌላ አይደለም።
እነ ከተማ ይፍሩ የአፍሪካ ኅብረት እዚህ እንዲቋቋም እንዴት የማሳመን ሥራ ሲሠሩ እንደ ነበር (ዕድሜ ለጸሐፍት) ማንም የሚረሳው አይደለም። “ከአክሱም ዘመነ መንግሥት ጀምሮ በንግድም ሆነ በፖለቲካ ሩቅ ምሥራቅን ያቀኑ፣ በመካከለኛው ምሥራቅ የተምነሸነሹ፣ ፋርስን ያደረጁ [የ]ብርቱ”ዎች አገር መሆኗም እንደዚሁ ዛሬም ድረስ እየተመሰከረላት የሚገኝ እድሜ ጠገብ እውነት ነው።
ዛሬ፣ ጥያቄው “ያ ሁሉ የአገራችን የዲፕሎማሲ ሌጋሲ አሁን አለ ወይ?” የሚለው ቢሆንም፤ ከዚህ ጽሑፍ አኳያ የአሁኑን ታኮ ሆኖ ማቆም፤ ስትራፕ እንዳያደርግ ማሳሰብ . . . በመሆኑ አሁን ላይ ማተኮሩ አስፈላጊ አይደለም።
በብዙ መንገድ የድሮው ዲፕሎማሲ ከዛሬው ዲፕሎማሲ የተለየ ነው። በበርካታ ምክንያቶች የአሁኑ የዲፕሎማሲ ተግባር ከድሮው ይከብዳል። በበርካታ ዘመናዊ ምክንያቶች የዛሬው ዲፕሎማሲ ውስብስብ ነው።
የዲፕሎማሲው ተግባር የቀድሞውን እርሾ ይዞ በብዙ መልኩ ፍሬያማ ሆኖ ቀጥሏል። ለማሳያም ያህል ኢትዮጵያን ለማዳከምና ከተሳካም ለማፈራረስ በርካታ የተወጠኑ በርካታ የውጪ እቅዶች የከሸፉት አንድም በዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ነው።
የድሮው ዲፕሎማሲ በግርድፍ መልኩ በአንድ መለያና መጠሪያነት ይታወቅ እንጂ ሥራው ግን ረቂቅና ሁሉንም ዳሳሽ ነበር። ዛሬ በዚሁ በዲፕሎማሲ ቋንቋ “ዘላቂ ወዳጅና ጠላት የለም”፤ “ብሔራዊ ጥቅም”፤ “የሉዓላዊነት ክብር”፤ “ሠጥቶ መቀበል” እና ሌሎችም የሚባሉበት ዘመን ነው።
የውሃ ዲፕሎማሲ፣ የቲዩተር/ፌስቡክ ዲፕሎማሲ፣ የሕዝብ ለሕዝብ (ፐብሊክ) ዲፕሎማሲ፤ “ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ”፤ “የኢኮኖሚ/ቢዝነስ ዲፕሎማሲ”፤ “የዕርዳታ ዲፕሎማሲ”፤ “የጦርነት ዲፕሎማሲ” . . . ወዘተርፈ በሚባልበት ወቅት ላይ ነን ።
በዚህ ዘመን በዲፕሎማቲክ ዘርፍ እየተሠራ ካለው ድሮ፣ የተሠራው የተሻለ ነበር ባዮች ጥቂት አይደሉም። የድሮው በእርሾነት ባይኖር ኖሮ የዛሬው . . . የሚሉም ብዛታቸው “እንደ ሰማይ ከዋክብት …” ባይባልም ጥቂቶች አይደለም።
ለማጠቃለል፣ ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው ዘርፍ ከድሮው ዘመን (የዲፕሎማሲያችን የማዕዘን ድንጋይ ከነበረው) ጀምሮ እስከ ዘንድሮው የዓባይ ግድብና የሉዓላዊነት ትግል ዘመን ዲፕሎማሲ ድረስ በርካታ ዲፕሎማሲ ሥራዎችን ሠርታ እጅግ አኩሪ ድሎችን አስመዝግባለች።
የተሰሚነቷ እርሾውም ስኬቱም አሁንም አለ። ተምሳሌትነቷም በታሪክ ተደግፎም ቢሆን አሁንም አለ፤ ጀግንነቱም አሁንም በእጇ ነው። ስለ ሥልጣኔዋም ገና ምንም አልተነገረላትም።
አሁንም ኢትዮጵያ በየዓለም አቀፉ መድረክ ተከራክረው የሚያሰንፉላትና እውነቷን የሚያስረዱ የቁርጥ ቀን ዲፕሎማቶች አሏት፡፡ እነዚህን መሰል የዲፕሎማሲያችን ስኬቶች አጠናክሮ ማስቀጠል አስፈላጊ ሲሆን፤ በተለይም ከዓለም አቀፍ ፍላጎት አንፃርና ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራን ልንሠራ ይገባል፤ ይህም የጋራ ትኩረትን ይሻል!
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው። በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ግንቦት 19/2015