አገራችን በርካታ የግጭት አፈታት ሥርዓቶች ባለቤት ናት። ከነዚህ የግጭት አፈታት ሥርዓቶች መካከል ‹‹ማጋ ራጋ›› የሚባለው የሊቢዶ/ ማረቆ ብሔረሰብ የግጭት አፈታት ዘዴ አንዱ ነው። ብሔረሰቡ በብሔረሰቡ ውስጥ የሚፈጠሩ ግጭቶችንም ሆነ ከሌሎች የአካባቢው ሕዝቦች ጋር የሚፈጠሩ ግጭቶችን ማጋ ራጋ የግጭት አፈታትን በመጠቀም ሲፈታ ኖሯል፤ ዛሬም እየፈታ ይገኛል።
የሊቢዶ/ማረቆ ብሔረሰብ ድምጻዊ እና በብሔረሰቡ ባህል እና ትውፊት ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን በማካሄድ የሚታወቀው አርቲስት ነጋሳ ሲጃ እንደሚለው፤ በብሔረሰቡ ግጭቶች በተለያዩ ደረጃዎች ይፈታሉ። በቤተሰብ ውስጥ የሚፈቱ ግጭቶች፣ በጎረቤት ደረጃ የሚፈቱ፣ በጎሳ ደረጃ እንዲሁም በብሔረሰብ ደረጃ የሚፈቱ ግጭቶች አሉ።
በታችኛው ደረጃ ሊፈታ ያልቻለ ግጭት ጉዳይ ወደ ቀጣይ ደረጃ ይሄዳል። አንድ ግጭት በቅድሚያ በቤተሰብ ደረጃ ሳይታይ ወደ ቀጣይ ደረጃ አይሄድም፤ ቤተሰብ ያላየውን ጉዳይ የጎሳ ሽማግሌዎች ወይም የብሔረሰቡ ሽማግሌዎች አይወያዩበትም፤ በቤተሰብ እንዲታይ ይመልሳሉ። በቅድሚያ የአካባቢው ሽማግሌዎች ችግሩን ለመፍታት ጥረት ማድረግ አለማድረጋቸውን ያጣራሉ።
አንድ ጉዳይ በታችኛው እርከን ካልተፈታ በቀጣይ እርከን ላይ ያሉ ሽማግሌዎች ጉዳዩን ይይዙና ይመረምራሉ። በታችኛው የዳኝነት እርከን የተላለፈው ውሳኔ ተገቢ ነው ብለው ካመኑበት አቤቱታውን ያቀረበው ሰው የቤተሰቡን ውሳኔ እንዲቀበል ጫና ያደርጋሉ። የቤተሰቡን ውሳኔ መቀበል እንዳለበት ጫና ያደርጋሉ። ምርመራውን አድርገው የቤተሰብ ሽማግሌ ስህተት ሠርቶ ከሆነ እንዲያስተካክል ይደረጋል።
‹‹ማጋ ራጋ›› የብሔረሰቡ የግጭት አፈታት ዘዴ ከሁለት ቃላት የተገኘ ሲሆን፣ ‹‹ማጋ›› የመጀመሪያ ዳኝነት ደረጃ ሲሆን፣ ራጋ ደግሞ የመጨረሻው ግጭት መፍቻ የዳኝነት ቦታ ነው። ለምሳሌ አንድ ሰው አደጋ (የመኪና ወይም ሌላ አደጋ) ቢያደርስ መሰል አደጋዎች ሲፈጠሩ የመጀመሪያ ዳኝነት የሚያየው ‹‹ማጋ›› ነው። ማጋ በቅድሚያ አደጋ/ ጉዳት የደረሰበት አካል ከጉዳቱ የሚያገግምበትን ሁኔታ ያፈላልጋል። ጉዳት የደረሰበት አካል ከጉዳቱ ሲያገግም ችግሩ እንዴት ተፈጠረ የሚለውን እንዲመረምር እና የመጨረሻ መፍትሄ እንዲሰጥ ወደ ‹‹ራጋ›› ይልካል። ‹‹ራጋ›› የመጨረሻ መፍትሄ ሰጪ አካል ነው። ‹‹ራጋ›› ያሳለፈው ውሳኔ በማረቆ ብሔረሰብ የመጨረሻው ውሳኔ ነው፤ በይግባኝ እንኳ የማይታይ ነው። በ‹‹ማጋ›› ውሳኔ ላይ ግን ቅሬታ ማቅረብ ይቻላል፤ ቅሬታውም የሚቀርበው ለ‹‹ራጋ›› ነው።
ማጋ በጊዜ የተፈጠረውን ችግር የሚፈታ ሲሆን፣ ራጋ ግን ወደ ኋላ ሄዶ ብዙ ነገሮችን ከግምት አስገብቶ ውሳኔዎችን ያስተላልፋል። የገዳይ የኋላ ታሪክ ምን እንደሆነ፣ ክስተቱ እንዴት እንደ ተፈጠረ ምንም ዓይነት ችግር እንዳይኖር በጥንቃቄ የሚደረግ የግጭት አፈታት ነው።
ነጋሳ እንደሚለው፤ የተፈጠረው ግጭት ከባድ ከሆነ ማጋ እና ራጋ በየደረጃው የየራሳቸውን ሚና ይወጣሉ። ለአብነት ያህል ሰው ከሰው ጋር ተጣልቶ የሰው ሕይወት የጠፋ ከሆነ የገዳዩ ቤተሰብ በቀጥታ ሄዶ የተፈጠረውን ነገር ለሽማግሌዎች ያሳውቃል። ለሽማግሌዎቹ ራሱን ያስተዋውቅና የቤተሰቡ አባል የሰው ሕይወት እንዳጠፋ ካሳወቀ በኋላ ሽማግሌዎቹ ጉዳዩን በሽምግልና እንዲይዙ ይጠይቃል።
ማጋዎች (ሽማግሌዎች) ወደ ገዳዩ ቤተሰብ ይሄዱና ገዳዩን ቤተሰቡ እንዲያቀርብ ይጠይቃሉ። የገዳይ ቤተሰብም ገዳዩ ካለበት ቦታ አምጥተው ለማጋ ያስረክባሉ። ገዳዩ በሽማግሌዎች እጅ እንደገባ ገዳዩ ጸጉሩ እና ቅንድቡ ይላጫል፤ ጥፍሩም ይቆረጣል። ይህም የሚደረገው ገዳዩ በፈጸመው ወንጀል ማዘኑን ለማሳየት ነው።
ጸጉር እና ቅንድብ ከተላጨ እና ጥፍሩ ከተቆረጠ በኋላ የገዳይ ቤተሰብ ቤቱን ለቆ እንዲሄድ ይደረጋል። የገዳይ ቤተሰብ ደጃፍም በእሾህ ይዘጋል የሚለው ነጋሳ፤ የቤቱ በር በእሾህ የሚዘጋበት ጊዜ አደጋው እንደተፈጸመበት ሁኔታ ይለያያል። የግድያ ወንጀሉ ሆን ተብሎ ታስቦበት የተፈጸመ ከሆነ ለረጅም ጊዜ የቤቱ ደጃፍ በእሾህ ሊዘጋ እና ቤተሰቡ ከአካባቢው ርቆ ሊቆይ ይችላል። ግድያው በድንገት የተፈጸመ ከሆነ ደግሞ ለአጭር ጊዜ ይሆናል። ይህም የሚደረገው የሟች ቤተሰብ በስሜታ ዊነት ከገዳይ ቤተሰብ ጋር ተጨማሪ ግጭት ውስጥ እንዳይገባ እና የሟች ቤተሰቦች ስሜት እስኪበርድ ነው።
ቤታቸውን ለቀው ከመሄዳቸው ባሻገር የሟች ቤተሰቦች ከወንዝ ውሃ በሚቀዱበት ቦታ ውሃ እንዳይቀዱ፣ ከብቶቻቸውንም የሟች ቤተሰብ ውሃ በሚያጠጣበት ቦታ እንዳያ ጠጡ በማጋ ማስጠንቀቂያ ይሰጣቸ ዋል። ከዚህ በተጨማሪም የሟች ቤተሰቦች በሚገበያዩበት ገበያ እንዳይገበዩ እንዲሁም የሟች ቤተሰቦች በሚያዘወትሩበት መን ገድ እንዳይንቀሳቀሱም እግድ ይጣልባቸዋል። የሟች ቤተሰ ቦችም ይህንን የማጋ ትዕዛዝ በሙሉ ልባቸው ይቀበላሉ። የሟች ቤተሰቦች ለሽማግሌዎች ታዛዥ ስለሆኑ የገዳይ ቤተሰቦችም ያሉበት ቦታ በመሄድ ለመተናኮል እንደማይሞክሩ ያስረዳል።
እንደ ነጋሳ ማብራሪያ፤ ማጋ (ሽማግሌዎች) ገዳዩን ከያዙና የገዳይ ቤተሰብን ወንዝ እንዲሻገሩ ካደረጉ በኋላ ወደ ሟች ቤተሰብ በመሄድ ሽምግልና ለመያዝ ፍላጎት እንዳላቸው ያስረዳሉ። የሟች ቤተሰብም የሟቹን አስከሬን ከቀበረ በኋላ የቀብር ዕለት ከቀብሩ ቦታ ትንሽ እንደተሄደ ለቀብር የሄደው ሰው ሁሉ እንዲቀመጥ ይደረጋል። ከዚያ በኋላም የሟች ቅርብ ቤተሰብ የሆኑ ሰዎች ተነስተው እንዲቆሙ ይደረጋል። የቆሙት የሟች ቤተሰብ አባላት ይመረቃሉ። መሰል አደጋ እንዳይደርስባቸው ፈጣሪ እንዲጠብቃቸው ይለመናል። ከዚያ በኋላ ማጋዎች ወደ ሟች እና ገዳይ ቤተሰብ በመመላለስ ያለውን ነገር በቅርበት እየተከታተሉ ለቅሶ እስኪወጣ ይጠባበቃሉ።
ለቅሶ ከወጣ በኋላ ራጋዎች የሟችን ቤተሰቦች ይዘው ወደ ገዳይ ቤተሰብ ያቀናሉ። የበዳይ እና የተበዳይ ወገኖች ግራና ቀኝ እንዲቀመጡ ይደረጋል። ገዳዩ እና የገዳይ ቤተሰብ በቡልኮ ወይም በጋቢ ተሸፍኖ ነው ወደ እርቅ ሥርዓቱ የሚሄደው። ገዳዩ እና የገዳይ ቤተሰብ በቡልኮ እንደተሸፋፈኑ ይቀመጣሉ። በተመሳሳይ የሟች ቤተሰብ አባላትም በቡልኮ ይሸፋፈናሉ። ገዳዩ በቡልኮ እንደተሸፋፈነ የእርቅ ሥርዓቱን ለመፈጸም በመጡ ሽማግሌዎች ፊት ወጥቶ አንገቱን አቀርቅሮ ብቻውን እንዲቀመጥ ይደረጋል። ይህም የሚደረግበት ምክንያት የሰው ነፍስ ያጠፋ ሰው እንደመሆኑ የእርቅ ሥርዓቱ ሳይፈጸም ሰውን ቀና ብሎ ማየት እንደማይችል ለማሳየት ነው ሲል ነጋሳ ትርጉሙን ያብራራል።
ገዳዩ ወጥቶ ከተቀመጠ በኋላ የሟች የቅርብ ቤተሰብ (ወንድም፣ ልጅ) እንዲሁ በሽማግሌዎች ፊት ይወጣል። የእርቅ ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ በዳይና ተበዳይ በአንድ ላይ ሆነው በባልዲ ሙሉ የቀረበ ማር እንዲቀምሱ ይደረጋል። ካንድ ባልዲ እንዲቀምሱ የሚደረግበት ምክንያት የገዳይ እና የሟች ቤተሰቦች አንድ መሆናቸውን ለማሳየት ነው። ሁለቱ በጋራ ማሩን በሚቀምሱበት ወቅት ሽማግሌዎች በምርቃት ያጅባሉ። ያለፈው አልፏል፣ ከአሁን በኋላ ሰላም ይሁን፣ ፍቅር ይሁን፣ አብሮነት ይሁን፣ እርቅ ይውረድ እያሉ ይመርቃሉ። የእርቅ ሥርዓቱ ከተካሄደ በኋላ ፍጹም ወንድማዊነት ይሰፍናል ይላል።
እንደ ነጋሳ ማብራሪያ፤ የእርቅ ሥርዓቱ ከተካሄደ በኋላ የሟችም የገዳይ ቤተሰብ አባላት ክንብንባቸውን ከራሳቸው ላይ እንዲያነሱ በሽማግሌዎቹ ይነገራል። ክንብንባቸውን ካነሱ በኋላ ሁለቱ ቤተሰቦች ማዕድ በጋራ ይቋደሳሉ። በእርቅ ሥርዓቱ የታደሙ የሟች እና የገዳይ ቤተሰብ አባላት እንዲሁም ራጋዎች የሟች ቤተሰብ እና ገዳይ በጋራ የቀመሱትን የማር ጠጅ ይጠጣሉ። የማር ጠጁ በቅድሚያ የሚሰጠው ለሟች የቅርብ ቤተሰብ ይሆናል። በተለይም የሟች ወንድም ካለ ለሟች ወንድም ይሰጣል። በመቀጠልም ለገዳይ ይሰጣል። ከዚያም ሥርዓቱን ለሚፈጽሙ ሽማግሌዎች ይሰጣል። በመጨረሻም ጥቁር ፍየል ይታረድና የእርቅ ሥርዓቱ ይቋጫል። ጥቁሩን ፍየል የሚያቀርበው የገዳይ ወገን ነው። የሚያርደውም የገዳይ ወገን ነው።
የብሔረሰቡ ባህልና ትውፊት ተመራማሪው አርቲስት ነጋሳ እንደሚለው፤ በጥቁር ፍየል የተቋጨ የእርቅ ሥርዓት አይፈርስም ተብሎ ይታመናል። ይህም ከአያት ቅድመ አያት ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ነው።
ፍየሉ ከመታረዱ በፊት ገዳዩ ግድያውን እንዴት እንደፈጸመ፣ የግድያው ዋና መንስኤ ምን እንደነበር በተሰበሰበው ሕዝብ ፊት እንዲናገር ይደረጋል። አንዳች ነገር ሳይደብቅ የተፈጠረውን ነገር ያስረዳል። ከዚያ በመቀጠል ፍየሉ ይታረዳል። ፍየሉን የሚያርደው የገዳይ ወገንን የሚወክል ሽማግሌ ነው።
በመቀጠል ደግሞ የሟች ወገንን የሚወክል ሽማግሌ የፍየሉን ትንሹን አንጀት ያወጣል። በፍየሉ አንጀት ገዳይ እና የሟች ወንድም የእግር አውራ ጣቶች በጋራ በአንድ ይታሰራሉ። በተጨማሪም የሟችና የገዳይ አጎቶች ጣትም እንዲሁ በአንድ ላይ ይታሰራል። ከዚያ በመቀጠል የሟች ወገን ተወካይ ሽማግሌ እና የገዳይ ወገን ተወካይ ሽማግሌ ጣትም በአንድ ላይ ይታሰራል። ይህም የሚካሄደው ሁለቱ ወገኖች የተሳሰሩ እና አንድ መሆናቸውን እንዲሁም ከዚህ በኋላ ምንም ዓይነት ቂምና በቀል በውስጣቸው እንደማይኖር ለማሳየት ነው። በመጨረሻም በሁለቱ ወገኖች ጣት ላይ የታሰረው አንጀት በቢላዋ ይቆረጣል። የታረደው ፍየል እና አንጀት የተቆረጠበት ቢላዋ በሁለቱ ወገኖች ተወካይ ዳኞች ይቀበራል። ይህም ጥላቻና ቂም ተቀብሯል ማለት ነው ሲል ነጋሳ ያብራራል።
በመጨረሻም ራጋው የወሰነው የጉማ ብር ለሟች ቤተሰብ ይሰጣል። ገዳይ ምንም ያህል ሀብታም ቢሆን የጉማ ብሩን ከኪሱ አውጥቶ አይከፍልም። የገዳይ የአባት ቤተሰቦች እና እናት ቤተሰቦች አዋጥተው ሰብስበው ነው የሚሰጡት። ብሩ ለሟች ወገን ሽማግሌ ከተሰጠ በኋላ የተሰጠውን ብር ሙሉ በሙሉ መውሰድ እንደሌለባቸው እና የተወሰነ ብር ለገዳይ ወገን እንዲመልሱ ይጠየቃሉ። የሟች ቤተሰብ በፈቃዱ የተወሰነ ብር ይመልሳል። በመጨረሻም የአገር ሽማግሌዎች መርቀው የእርቁ ሥርዓት ይፈጸማል።
እንደ ነጋሳ ማብራሪያ፤ አንዳንድ ጊዜ ራጋ የሟች ቤተሰብ ከገዳይ ቤተሰብ ብር እንዳይቀበል ሊወስን ይችላል። ትልቅ ሰው ሞቶ አንድ ጋቢ ብቻ እንዲሰጥ ሊወስን ይችላል። ምክንያቱም ራጋ ለሟች እና ለገዳይ ለወደፊት የሚበጀው ነገር ይታየዋል ተብሎ ይታመናል። የተደበቀ ነገር አለ ብሎ ካሰበ ምንም ዓይነት ካሳ እንዳይወስዱ ሊወስን ይችላል።
እርቁ ከተፈጸመ በኋላ የገዳይ እና የሟች ቤተሰቦች እንደ አንድ ቤተሰብ ነው የሚታዩት። ገዳዩ የሟች ቤተሰብ አባል ተደርጎ ይታያል። ሁለቱ ቤተሰቦች የቅርብ ዘመድ ተደርገው ስለሚቆጠሩ በሁለቱ ቤተሰቦች መካከል ጋብቻ አይፈቀድም።
የማጋ ራጋ ሥርዓት እንክብካቤ ሊደረግለት እና ሊደገፍ እንዲሁም ተጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ መተላለፍ ያለበት ድንቅ የግጭት አፈታት ዘዴ ነው። በተለይም ባህላዊ ይዘቱን እያጣ እንዳይሄድ የሚመለከተው አካል ጥንቃቄ ሊያደርግለት ይገባል። ከምንም በላይ እርቁ ከወረደ በኋላ የበዳይ እና የተበዳይ ወገን በቂምና በቀል እንዳይፈላለጉ በር የሚዘጋ መሆኑ ከዘመናዊ የግጭት መፍቻ ዘዴዎች እጅግ የሚልቅ ፋይዳ አለው።
መላኩ ኤሮሴ
አዲስ ዘመን ግንቦት 18/2015